torsdag 26. november 2015

አቶ አብርሃም ጌጡ ይግባኝ ተጠየቀበት

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
በአቶ ማሙሸት አማረ ካቢኔ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የውጭ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አብርሃም ጌጡ ህዳር 14/2008 ዓ.ም አራዳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት (ሰባራ ባቡር) ቀርቦ ይግባኝ ተጠይቆበታል፡፡ የአራዳ ምድብ ችሎት ለህዳር 11/2008 ዓ.ም ቀጥሮበት የነበር ቢሆንም ህዳር 7/2008 ዓ.ም ፍርድ ቤቱ በነፃ እንዲለቀቅ መወሰኑ ይታወቃል፡፡
አቶ አብርሃም ጌጡ ሰኔ 12/2008 ዓ.ም ቤቱ ተበርብሮ ከታሰረ በኋላ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ ቆይቷል፡፡ ወደ ሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ተዛውሮ ከቆየ በኋላ ከሀምሌ 12/2008 ዓ.ም ጀምሮ ማዕከላዊ ታስሮ ይገኛል፡፡ አቶ አብርሃም ጌጡ ‹‹በሽብር ወንጀል›› ለ6ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት የቀረበ ሲሆን ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ መዝገቦችና በተለያዩ ፍርድ ቤቶች ለ11ኛ ጊዜ መቅረቡን ጠበቃው ገልፀዋል፡፡
አቶ አብርሃም ጌጡ ወደ ማዕከላዊ ተዛውሮ ለሶስት ወራት በማዕከላዊ የቆየው ‹‹በሽብር ወንጀል›› ነው ተብሎ የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ የተከሰሰው በሽብር ሳይሆን በሀሰት ወሬ በማውራት በመሆኑ፣ ይህም ዋስትና እንደማያስከለክል፣ ለዚህ ክስም በቂ ዋስትና አስይዞ እንዲለቀቅ ወስኖ ነበር፡፡ ይሁንና አቶ አብርሃም ጌጡ ከእስር እንዲለቀቅ ፍርድ ቤቱ ከወሰነ በኋላም በማዕከላዊ እስር ቤት ታስሮ እንዲቆይ ተደርጎ ከሰባት ቀናት በኋላ ህዳር 14/2008 ዓ.ም ይግባኝ ተጠይቆበታል፡፡ ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ህዳር 16/2008 ዓ.ም ድረስ ‹‹የሀሰት ወሬ በማውራት›› በሚል ክስ ቀርቦበት እንዲፈታ የተወሰነለት አቶ አብርሃም ጌጡ በማዕከላዊ ታስሮ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

onsdag 25. november 2015

መራዊ ላይ የታሰሩት ወጣቶች ከፍተኛ ድብደባ ተፈፀመባቸው • ሁለቱ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ናቸው

ህዳር 4/2008 ዓ.ም በምዕራብ ጎጃም ዞን መራዊ ከተማ የታሰሩት 8 ወጣቶች ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ምንጮች ለነገረ ኢትዮጵያ ገለፁ፡፡ ህዳር 4/2008 ዓ.ም በሌሊት ቤታቸውን ተበርብሮ ከታሰሩት መካከል በተለይም የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ መኳንንት ፀጋዬ እና አቶ እያዩ መጣ ከፍተኛ ድብደባ እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡ ህዳር 4/2008 ዓ.ም ጣቢያ ዘጠኝ ተብሎ ወደሚታወቀው እስር ቤት ተወስደው እንደተደበደቡ የገለፁት ምንጮቹ ህዳር 9/2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርበው ወደ ማረሚያ ቤት እንዲዛወሩ ትዕዛዝ ቢሰጥም ፖሊስ ባህርዳር ከተማ በሚገኘው ጣቢያ ዘጠኝ የተባለ እስር ቤት በመውሰድ እስከ ህዳር 14/2008 ዓ.ም ከፍተኛ ድብደባ ፈፅሞባቸዋል፡፡
ፖሊስ እስረኞቹን ወደ ማረሚያ ቤት እንዲያዛውር ትዕዛዝ ተሰጥቶት የነበር ቢሆንም እስረኞቹ ፍርድ ቤት ቀርበው ጣቢያ ዘጠኝ በተባለው እስር ቤት ከፍተኛ ድብደባ እንደደረሰባቸው በመግለፃቸው ‹‹ለፍርድ ቤቱ ለምን ተደበደብን ብላችሁ ተናገራችሁ?›› በሚል ለተጨማሪ 5 ቀናት ድብደባው እንደተፈፀመባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ እስረኞቹ ድብደባው የሚፈፀምባቸው ‹‹ለምን የተቃውሞ እንቅስቃሴያችሁን አታቆሙም? ከተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ጋር ያላችሁን ግንኙነት ለምን አታቆሙም?›› እየተባሉ መሆኑንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡
ህዳር 4/2008 ዓ.ም ታስረው ድብደባ የተፈፀመባቸው እስረኞች፡-
1. መኳንንት ፀጋዬ
2. እያዩ መጣ
3. መምህር ሀምታሙ ጥላሁን
4. ስማቸው ማዘንጊያ
5. ቄስ ዘላለም ሞትባይኖር
6. አረጋዊ መጣ
7. ሽባባው የኔዓለም እና
8. አብርሃም ተስፋ ሲሆኑ አብርሃም ተስፋ የኢህአዴግ አባል እንደሆነ ታውቋል፡፡

tirsdag 24. november 2015

በአዛዙ የአፈና መዋቅር የኢትዮጵያ ህዝብ የነፃነትና የእኩልነት ትግል አይቀለበስም!

ህወሓት/ኢህአዴግ በህገ መንግስቱና በሌሎች ራሱ ባወጣቸው ህጎች በርካታ መብቶችን ለይስሙላ ቢደነግግብ ቅሉ፤ በተግባር ግን እነዚህን መብቶች ሆነ ብሎ ባደራጀው የአፈና መዋቅሩ እየደፈቃቸው ይገኛል፡፡ ምንም እንኳን አገዛዙ የመደራጀት መብትን በወረቀት ቢያሰፍርም ‹‹እግር እስኪያወጡ እንጠብቃለን፤ እግር ሲያወጡ ግን እንቆርጣለን›› በሚል መርህ ፓርቲዎችን በዚሁ የአፈና መዋቅሩ በገሃድ እያፈረሰ ቀጥሏል፡፡ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትን ፈቅጃለሁ ቢልም ጋዜጠኞችን በማሰር፣ በማሳደድና ሚዲያዎችን በመዝጋት አማራጭ ሀሳብ እንዳይራመድ አድርጓል፡፡ የመሰብሰብና ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብትን ወረቀት ላይ ቢደነግግም በአስተዳደራዊ መዋቅሩ መሰረት ክርችም አድርጎ ዘግቶታል፡፡ የዜጎችን የመዘዋወር መብት ቢደነግግም ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ፓስፖርት በመንጠቅ ጉዟቸውን በማተጓጎል ላይ ይገኛል፡፡ የመንግስት አሰራር ግልፅና ተጠያቂነት አለበት ተብሎ ተደንግጓል፤ ነገር ግን በየ መስርያ ቤቱ ያለ እጅ-መንሻ ዜጎች አገልግሎት ማግኘት አይቻልም፡፡ ይህ ሁሉ አፈና ሆነ ተብሎ ታስቦበት፣ የአገዛዙን ስልጣን ለማራዘም የሚደረግ መዋቅራዊ ጫና መሆኑን ፓርቲያችን በጽኑ ያምናል፡፡

ዛሬ በሀገራችን ከፍተኛ ርሃብ፣ ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ ስራ አጥነት፤ ስደት እና ሌሎችም ፖለቲካዊና ማህበራዊ ቀውሶች በሰፊው ተንሰራፍተው ይገኛሉ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ እነዚህን ወቅታዊ ጉዳዮች ከህዝብ ጋር ተወያይቶ አቋም ለመውሰድና የመፍትሄ አቅጣጫዎችን ለመሰንዘር ህዳር 18 ቀን 2008 ዓ.ም ህዝባዊ ስብሰባ እንደሚያደርግ ለአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት የእውቅና ደብዳቤ ለማስገባት በተደጋጋሚ ጥረት ያደረግን ቢሆንም የአፈና መዋቅሩ የእውቅና ደብዳቤውን መቀበል ባለ መፈለጉ ለ5 ጊዜ ተጉላልተን በ6ኛው በሪኮመንዴ(በፖስታ) ለመላክ ተገደናል፡፡
የእውቅና ደብዳቤው በሪኮመንዴ የደረሰው አስተዳደሩ ህዳር 6 ቀን 2008 ዓ.ም ላይ ሆኖ ‹‹ህዳር 18/2008 ዓ.ም አልፏል›› በሚል ለተጨማሪ ጊዜ ደብዳቤውን ሳያስተናግድ ቀርቷል፡፡ ህዳር 18 ያላለፈ መሆኑን ካስረዳን በኋላ ለሶስት ቀናት በተደጋጋሚ ብንመላለስም ‹‹ከደህንነትና ፖሊስ ጋር ካልተመካከርኩ እውቅና አልሰጥም›› ሲል እምቢታውን ገልጾአል፡፡ በዚህም ምክንያት ከአባላትና ደጋፊዎቻችን ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ልናደርገው የነበረው ውይይት ሊደናቀፍ ችሏል፡፡
ከዓለም የነጻነት የትግል ታሪክ እንደምንገነዘበው በአገዛዝ አፈና የተገታ የህዝብ ጥያቄ ኖሮ አያውቅም፡፡ አፈናው የነጻነትን ጊዜ ቢያዘገይ እንጅ ፈጽሞ ሊያስቀርም አይችልም፡፡ ስለሆነም ጭቆናው ወደ ነፃነት የሚያስኬደውን ጉዞ እልህ አስጨራሽ ከማድረግ በቀር ዘላቂነት ኖሯቸው የነጻነት ጥያቄውን ፈጽሞ ማዳፈን እንደማይችሉ አገዛዙ ሊረዳ ይገባል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ህዝብ ለማይቀረው የነፃነት ትግል ቆርጦ እንዲነሳና ከሰማያዊ ፓርቲ ጎን እንዲቆም ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
ህዳር 14 ቀን 2008 ዓ.ም
አዲስ አበባ

onsdag 18. november 2015

እነ ማቲያስ መኩሪያ ጥፋተኛ ተባሉ

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
አይ ኤስ በኢትዮጵውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ ድርጊት ለመቃወም መንግስት በጠራው ሰልፍ ሰበብ የታሰሩት ማቲያስ መኩሪያ፣ ብሌን መስፍን፣ ተዋቸው ዳምጤ እና መሳይ ደጉሰው ዛሬ ህዳር 8/2008 ዓ.ም በፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት በመናገሻ ምድብ ችሎት ቀርበው ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡
ችሎቱ በቢሮ ከመታየቱም ባሻገር ችሎት አስከባሪው ‹‹መግባት አይቻልም፡፡ ተከልክሏል፡፡ የከለከልኩት ግን እኔ አይደለሁም፡፡›› በማለቱ ማንም እንዳይገባ ተከልክሎ በዝግ ታይቷል፡፡ ፖሊስ ተከሳሾቹ ላይ የቪዲዮ ማስረጃ አለኝ በማለቱ ተከሳሾቹም ‹‹የቪዲዮ ማስረጃው ለእኛም በመከላከያ ማስረጃነት ስለሚያገለግለን ይቅረብልን›› ባሉት መሰረት ቪዲዮውን አይቶ ብይን ለመስጠት ለወራት ሲቀጠርባቸው ቆይቷል፡፡
ከመሳይ ደጉሰው ውጭ ያሉት ተከሳሾች የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፡፡ ተከሳሾቹ ከታሰሩ ከ6 ወር በላይ የሆናቸው ሲሆን በፍርድ ሂደቱ ከፍተኛ መጉላላት እየደረሰባቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ሲያቀርቡ ቆይተዋል፡፡ እነ ማቲያስን ጥፋተኛ ያለው ፍርድ ቤቱ ለህዳር 22/2008 ዓ.ም ለውሳኔ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

mandag 16. november 2015

በዘመናችን የተራቡ ዜጎችን መደበቅ እንደ ገጽታ ግንባታ የሚቆጥሩ ሰዎችን ከባለሻሽ ሌቦች ለይቼ ኣላያቸውም | ከበእውቀቱ ስዩም

beweketuባገራችን ኣብዛኛው ዜጋ ለቀን ጉርስና ላመት ልብስ ሲታገል የሚኖር ነው፡፡ ጌቶች ደግሞ ኣማርጠው ይበላሉ፡፡ ኣማርጠው ይለብሳሉ፤በለስ ሲቀናቸው ደግሞ የሃያ ኣምስት ሚሊዮን ብር ቪላ ይቀልሳሉ፡፡ እንዲያም ሆኖ ደግሞ መከበርና መደነቅ ይፈልጋሉ፡፡

 ሰው ምንም በስጋው ቢመቸው በሌላው ተመዝኖ እንደቀለለ ሲሰማው ደስተኛ ኣይሆንም፡፡ ስለዚህ ጌቶች ያስንቀናል ብለው የሚያስቡትን ነገር በሙሉ ጠምድው ይይዙታል፡፡ ይዋጉታል፡፡

 ኢትዮጵያ- ጌቶች ለኩራታቸው፤ ዜጎች ለራታቸው የሚታገሉባት መድረክ ናት፡፡ ብዙ ጊዜ ረሀብ ሲከሰት ጌቶች ራብተኛውን ሁሉ ሰብስበው ጎተራ ውስጥ ሊደብቁት ይቃጣቸዋል፡፡

 የድሆች የተራቆተ ሰውነት የገጠጠ ኣጥንት፤ የጌቶችን የመከበር ፍላጎት ያከሽፈዋል፡፡ ባንድ ወቅት በቦሌ መዳኒያለም ዳርቻ ስራመድ ኣካባቢው ኣለወትሮው በለማኞች ኣለመሞላቱን ታዝቤ ተገረምሁ፡፡

ያዲሳባ ኣስተዳደር ፤ ለማኞችን“ በጥቃቅንና ኣነስተኛ ” ኣደራጅቶ ያሳለፈላቸው መስሎኝ ነበር፡፡ እንደተሳሳትሁ ለመረዳት ጥቂት ደቂቃ በቦታው መቆም ነበረብኝ፡፡


 ኣንዲት ተመጽዋች ሴት ልጇን ይዛ ከቅጽሩ ስር ለመቀመጥ ስታነጥፍ ፖሊስ በቆረጣ ገብቶ “ዞር በይ ነግሬሻለሁ” እያለ ሲያዋክባት ተመለከትሁ ፡፡ የደነገጠ ልጇን እየጎተተች ተወገደች፡፡ ከዚያ ወዲያ ከኣቡነ ጳውሎስ ሃውልት በቀር ባካባቢው ደፍሮ የቆመ ኣልነበረም፡ ፡ ወደ ቤቴ ከመሄዴ በፊት ያቡኑን ወፍራም ሀውልት ዞር ብየ ሾፍኩት፡፡

 እጁን እንደ ራሱ ሀይሉ ሙርጥ ገትሮ ከፊትለፊት ያለውን “ ሬድዋን ህንጻ ” ሲባርክ ነበር፡፡ “ገጽታ ግንባታ?” በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን የፍርድ ምኒስተር የነበሩት ኣፈንጉስ ነሲቡ የሌባ ብዛት ቢያስቸግራቸው ኣንድ መላ መቱ፡፡ ሲሰርቅ የተገኘ ወሮበላ ግንባሩ ላይ በጋለ ስለት ምልክት እንዲደረግበት ደነገጉ፡፡

 ታድያ ሌቦች የዋዛ ስላልነበሩ ሻሽ በመጠምጠም የግንባራቸውን ጠባሳ ሊሰውሩት ሞክረዋል፡፡ በጊዜው ደግሞ ሻሽ መጠምጠም ካክሱም ዘመነ መንግስት ጀምሮ የወረደ የነገስታቱና የመሳፍንቱ ወግ ነበር፡፡ ጮሌ ሌቦች ውርደታቸውን ከመሸፈን ኣልፈው የንጉስ ገጽታ ተላብሰው ብቅ ኣሉ፡፡ በዘመናችን የተራቡ ዜጎችን መደበቅ እንደ ገጽታ ግንባታ የሚቆጥሩ ሰዎችን ከባለሻሽ ሌቦች ለይቼ ኣላያቸውም፡፡ በነገራችን ላይ፤ ብርቱካን ኣሊ ግለሂስ ያደረገችበትን ዘገባ ካየሁ በኋላ ለጊዜው ለመናደድ እንኳ ቸግሮኝ ነበር፡፡

 ዘገባውን የሠራው ጋዜጠኛ እንዲህ ኣይነቱን ካንድ ድንጋይ የተጠረበ ደደብነት ተሸክሞ የመኖር ችሎታው በጣም ኣስደነቀኝ፡፡ በዚህ በሰላቢው ቀን ይቅርና፤ በደህናው ቀን እንኳ የባላገሩን ራብና መከራ ከጉያው የበቀልን ልጆቹ እናውቀዋለን ፡፡ ኣስራ ኣምስት ሚሊዮን ህዝብ መደበቅ ሰማይን በመዳፍ ለመሸሸግ እንደ መሞከር ይቆጠራል፡፡

 መመፍትሄው በተቸገሩ ሰዎች ጫማ ቆሞ ነገሮችን መመልከት ነው፡፡ ለነገሩ ችግርን ያልቀመሰ ሰው ለችግረኛ መራራት እንዴት ይቻለዋል? ኣብን ተውትና ፤ንገሩት ለወልድ ተገርፏል ተሰቅሏል ፤ እሱ ያውቃል ፍርድ እንዲል ባላገር፡፡

በእነ ሀብታሙ አያሌው ላይ አቃቤ ህግ የጠየቀው ይግባኝ ያስቀርባል ተባለ

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
አቃቤ ህግ የሽብርተኝነት ክስ መስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ እንዲሰናበቱ ተበይኖላቸው በነበሩት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ላይ አቃቤ ህግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት የጠየቀው ይግባኝ ያስቀርባል ተባለ፡፡
ዛሬ ህዳር 6/2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በእነ ሀብታሙ አያሌው ላይ የተጠየቀውን ይግባኝ መዝገቡን መመርመሩን በመግለጽ ዝርዝር ሁኔታውን በንባብ ሳያሰማ በአጭሩ፣ ‹‹ይግባኙ ያስቀርባል ብለናል›› ብሏል፡፡
በመሆኑም ይግባኝ የተጠየቀባቸው ተከሳሾች ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሺ እና አብርሃም ሰለሞን በቀረበባቸው ይግባኝ ላይ በአካል ቀርበው የቃል ክርክር ለማድረግ ለህዳር 29/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
የስር ፍርድ ቤት በነጻ እንዲሰናበቱ ቢበይንም፣ ሁሉም ተከሳሾች አሁንም ድረስ በእስር ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡

mandag 9. november 2015

እነ የሺዋስ ለሶስተኛ ጊዜ ባልተገኙበት ቀጠሮ ተሰጠባቸው


በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው በፌደራል ክፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ከተበየነላቸው በኋላ አቃቤ ህግ ይግባኝ ጠይቆባቸው ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ዛሬ ጥቅምት 29/2008 ዓ.ም ለሶስተኛ ጊዜ ባልቀረቡበት ለህዳር 6/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ጥቅምት 17/2008 ዓ.ም፣ ጥቅምት 22/2008 ዓ.ም እንዲሁም ዛሬ ጥቅምት 29/2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸው ለሶስተኛ ጊዜ በሌሉበት የተቀጠረባቸው አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ሀምታሙ አያሌው፣ አቶ ዳንኤል ሽበሺና አብሯቸው ይገብኝ የተጠየቀበት አቶ አብርሃም ሰለሞን ናቸው፡፡
ጥቅምት 22/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ማስረጃ ዝርዝር ከብይን ጋር ተያይዞ ባለመቅረቡ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት የቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ላይ መርምሮ ለመወሰን ስላልቻለ፤ ይግባኝ ያስቀርባል አያስቀርባል የሚለውን ለመወሰን በእስር ፍርድ ቤቱ ያሉ ዝርዝር የአቃቤ ህግ ማስረጃዎች ተያይዘው እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ሲሆን በዛሬው ችሎት አቃቤ ህግ ማስረጃዎቼ ያላቸውን አያይዞ ቀርቧል፡፡ ይሁንና ፍርድ ቤቱ ‹‹መረጃዎቹ ስላልተመረመሩ መርምሮ ይግባኝ ያስቀርባል አያስቀርብም የሚለውን ለመወሰን›› በሚል ለህዳር 6/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቶባቸዋል፡፡

fredag 6. november 2015

በርሃብ የተጠቁት ዜጎች ቀያቸውን ለቀው እየተሰደዱ ነው • መንግስት በርሃብ ለተጠቁት ዜጎች እርዳታ እየሰጠ አይደለም

መንግስት በርሃብ ለተጠቁት ዜጎች እርዳታ እየሰጠ እንዳልሆነ ታወቀ

• ‹‹ሰው በርሃብ እያለቀ ነው››




• ‹‹የሚላስ የሚቀመስ የለም፡፡ ቤተሰባችን ፈርሷል››

• ‹‹እርዳታ ቢሰጥማ ከዚህ ድረስ አንመጣም ነበር፡፡››
መንግስት በርሃብ ለተጎዱት ዜጎች እርዳታ እየሰጠ እንዳልሆነ ቀያቸውን ለቀው አዲስ አበባ የገቡት የርሃቡ ሰለባዎች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ከወሎ የተለያዩ አካባቢዎች በርሃብ የተጠቁ ዜጎች ህይወታቸውን ለማትረፍ ወሎ ውስጥ ከሚገኙት ከተሞች አልፈው ወደ ጎጃም፣ ጎንደርን እንዲሁም አዲስ አበባ እየተሰደዱ ሲሆን አዲስ አበባ በርካታ ተጎጅዎች ህፃናትን አዝለው እየለመኑ ይገኛሉ፡፡ የነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር ካነጋገራቸው መካከል ሁሉም መንግስት ለርሃቡ ተጎጅዎች እርዳታ እየሰጠ እንዳልሆነ ገልፀዋል፡፡ ቤተሰቦቻቸውና ጎረቤቶቻቸውም እንደነሱ ቀያቸውን ጥለው ወደ መተማ፣ ሁመራ፣ ባህርዳር፣ ደሴ፣ እንዲሁም ወደ አዲስ አበባ መሰደዳቸውን በሀዘን ገልፀዋል፡፡
rehab3
rehab3

ወሎ ውስጥ ጮሬ ሶዶማ ከተባለ ቦታ ተነስታ እንደመጣች፣ አዲስ አበባ ከገባች ሶስት ሳምንት እንደሆናት የገለፀችውና ሁለት ህፃናትን ይዛ ስትለምን ያገኘናት፤ በግምት በ30ዎቹ መጨረሻ ዕድሜ የምትገኝ እናት ‹‹የመጣነው የሚላስ የሚቀመስ ስለሌለ ነው፡፡ ከብቶቻችን አልቀዋል፡፡ አዝመራ የሚባል የለም፡፡ ሰው በርሃብ እያለቀ ነው፡፡ እኛ ሴቶቹ ወደ ከተማው ስንመጣ ወንዶቹ ደግሞ ወደ ሁመራና መተማ ሄደዋል፡፡ እኛም ከዚህ የመጣነው ጉልበት ስላለን ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ደካሞች በዛው አካባቢ ቀርተዋል፡፡›› ስትል በሀዘን ገልፃልናለች፡፡ መንግስት እርዳታ አይሰጥም ወይ ብለን ላነሳንላት ጥያቄም ‹‹ምንም እርዳታ አልተሰጠንም፡፡ እርዳታ ቢሰጥ ኖሮ ቤታችን ጥለን አንመጣም ነበር፡፡ ባያበቅልም መሬት አለን፡፡ የከተማው ሰው ይሻላል ብለን ነው ወደዚህ የመጣነው›› ስትል ስለ ርሃቡ አስከፊነትና መንግስትም እርዳታ እየተሰጠ እንዳልሆነ ገልፃልናለች፡፡
rehab 4
rehab 4

ባለቤቷ ወደ መታማ ሲሄድ እሷም ቤቷን ጥላ ወደማታውቀው አዲስ አበባ እየጠየቀች እንደመጣች የገለፀችልን ወጣት በበኩሏ ‹‹ቤቴ ተፈትቷል፡፡ ባለፈው አመት ከብቶችም እህልም ነበረን፡፡ ዘንድሮ ግን ምንም ነገር የለም፡፡ ጊዜው ከፍቷል፡፡ ባሌ ወደ መተማ ሄዷል፡፡ እኔም ልጄን አዝዬ እስከ ደሴ በእግሬ መጣሁ፡፡ ከዛ በኋላ እየለምንኩ ከዚህ ደርሻለሁ፡፡ ማንም እርዳታ አልሰጠንም፡፡›› ስትል ስለሁኔታው ገለፃልናለች፡፡

ከመርሳ ወረዳ እንደመጡ የገለፁልንና ከልጃቸው ልጅ ጋር እየለመኑ ያገኘናቸው የ65 አመት አዛውንት በበኩላቸው ‹‹ዝናቡ ሲቀር ከብቶቻችንም ሞቱ፡፡ አዝመራ የሚባልም ነገር የለም፡፡ ከመርሳ ደሴ እየለመንኩ መጣሁ፡፡ ደሴም እንደኛ ብዙ ሰው አለ፡፡ አገኝ ብሎ በየከተማው ተሰራጭቷል፡፡ ወደዚህ ይሻላል ብዬ በለመንኳት ተሳፍሬ መጣሁ፡፡ ርሃቡ ሲብስብን ወደማናውቀው አገር መጣን፡፡›› ሲሉ የርሃቡን አስከፉነት ገልፀውልናል፡፡
‹‹እርዱኝ!›› እያሉ እየለመኑ ያገኘናቸው ከኬሚሴ አካባቢ እንደመጡና ከ8 ቀን በፊት አዲስ አበባ እንደደረሱ የገለፁልን ሌላኛዋ እናትም ቤታቸውን ጥለው እንደመጡና፣ ሌሎች ቤተሰቦቻቸው ወደ የት እንደሄዱ እንኳን እንደማያውቁ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ መንግስት እርዳታ እየሰጠሁ ነው እንደሚል ስንገልፅላቸው ‹‹ለእኔ አልደረሰኝም፡፡ እርዳታ ተሰጠኝ ያለም አልሰማሁም፡፡ እርዳታ ቢሰጥማ ከዚህ ድረስ አልመጣም ነበር፡፡ አሁን ነው ከከተማው ሰው ትንሽ ትንሽ እያገኘን ያለነው፡፡ በየ ከተማው ስንደርስ ሰው አይነፍገንም›› ሲሉ ከህዝብ እንጅ ከመንግስት እርዳታ እንዳላገኙ ገልፀዋል፡፡
rehab 5
rehab 5

ካሳንቺስ አካባቢ ልጅ አዝለው ታክሲ ተሳፋሪዎችን ምንም አይነት ቃል ሳያሰሙ ልጃቸውን በመዘርጋት ብቻ እንዲረዷቸው እየጠየቁ ያገኘናቸው እናትም የራሳቸውንና የታዘለውን ልጅ ነፍስ ለማዳን ቀያቸውን ጥለው ወደ አዲስ አበባ መምጣታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡

የርሃቡ ተጎጅዎች አዲስ አበባ ውስጥም ነፍሳቸውን ለማቆየት በጠራራ ፀሀይ ሲለምኑ እንደሚውሉና ምቹ ያልሆነ ቦታ አንድ ላይ የሚያድሩ በመሆኑ ልጆቻቸው ለበሽታ እየተጋለጡ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ተማሪ የነበሩና በርሃቡ ምክንያት ለማቋረጥ የተገደዱት ልጆቻቸው ከእነሱ ጋር ወይንም ወደ ሌላ አካባቢ ነፍሳቸውን ለመዳን መሰደዳቸውን፣ በያለፉበት ከተማም በርካታ ስደተኛ እንዳለም ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡

tirsdag 3. november 2015

በቡሬ ግንባር ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የህወሓት መራሹ መከላከያ ሰራዊት አባላት ከዱ

የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ) ባጠቃላይ በአራቱም ማዕዘን የኢትዮጵያ ጠረፎች በቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ የሚኖረው በህወሓት ቁጥጥር ስር የሚገኘው መከላከያ ሰራዊት አባላት በየዕለቱ ያለማቋረጥ ስርዓቱን እየከዱ ሲሆን በተለይም ደግሞ ከሰሞኑ ቡሬ ግንባር በስልጠና ላይ ይገኙ የነበሩ እጅግ በጣም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ወታደሮች ያገኙትን ቀዳዳ ተጠቅመው በቡድን በቡድን እየሆኑ በመሽሎክ ከአካባቢው ተሰውረዋል፡፡ ወሎ ውስጥ ከአንድ ቀበሌ ብቻ 10 ወታደሮች ከጦር ግንባር ከድተው ወደ ቀያቸው መመለሳቸውን ምንጮቻችን ተናግረዋል፡፡ አሁንም ቢሆን አብዛኛው ሰራዊት መሽሎኪያ ቀዳዳ እያነፈነፈ ሊከዳ በቋፍ ላይ እንደሚገኝ የመከላከያ ምንጮቻችን የላኩት መረጃ ያረጋግጣል፡፡
clash