onsdag 27. februar 2013

የሳውዲው ም/ል የመከላከያ ሚኒስትር ኢትዮጵያን ወቀሱ


ምክትል የመከላከያ ሚኒሰትሩ ካሊድ ቢን ሱልጣንን በመጥቀስ ሱዳን ትሪቢዩን እንደዘገበው፣ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ በአባይ ላይ ምትገነባው ፕሮጀክት ለሱዳንና ግብጽ ከፍተኛ አደጋ አለው በማለት ተናግረዋል።

ግድቡ በ700 ሜትር ከፍታ ላይ የሚሰራ በመሆኑና 70 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሀ የሚይዝ በመሆኑ፣ ግደቡ ቢፈርስ ሱዳን ሙሉ በሙሉ ስትሰምጥ፣ የግብጽ አስዋን ግድብ ደግሞ አደጋ ያጋጥመዋል ብለዋል ሚኒስትሩ።

ግብጽ ሌላ አማራጭ ውሀ የሌላት በመሆኑ ከሁሉም በላይ እንደምትጎዳ የገለጡት ሚ/ር ካሊድ፣ ግድቡን ከሱዳን ድንበር 12 ኪሎሜትር እርቀት ላይ ለመስራት የተፈለገው ከኢኮኖሚ ጠቀሜታ ይልቅ የፖለቲካ ሴራ ለማሴር ነው ብለዋል።

ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ የአረብ አገራትን ለመጉዳት ሆን ብላ የነደፈችው ፕሮጅክት ነው ብለዋል። ግድቡ ከፍተኛ የሆነ ውሀ የሚሸከም በመሆኑም በአካባቢው ላይ የመሬት መንቀጥቀጥ ሊያስከትል ይችላል።

የሳውዲው ወኪል ግብጽን በመወከል እንዲናገሩ ያስገደዳቸው ምክንያት በውል አልታወቀም። የኢትዮጵያ መንግስት ከሱዳንና ግብጽ ጋር ያለውን ልዩነት ለመፍታት ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን ሲገልጽ ቆይቷል።

 ሟቹ ጠቅላይ ሚኒሰትር መለስ ዜናዊ ከአንዳንድ አፈንጋጭ ግብጻዊያን በስተቀር አብዛኛው ግብጻዊ በአባይ ላይ በሚሰራ ፕሮጀክት ተቃውሞ እንደሌለው ገልጸው እንደነበር ይታወሳል።

የግብጽ ከፍተኛ ባለስልጣናት ወደ አዲስ አበባ ሄደው በነበረበት ወቅትም፣ ግብጽ በአገሪቱ የተነሳው አብዮት ውጤት እስኪታወቅ ድረስ ተጨማሪ ጊዜ እንደምትፈልግ መጠየቋ በኢትዮጵያ መንግስት የመገናኛ ብዙሀን ቀርቦ ነበር።

የሳውዲው ሚኒስትር ንግግር ግብጽ በአባይ ላይ የሚሰራውን ግድብ አጥብቃ እንደምትቃወም የሚያመላክት ነው።

በአምስት ዓመታት ጊዜያት ውስጥ 196 ፕሬሶች ከሕትመት ውጪ ሆኑ


በኢትዮጽያ ባለፉት አምስት ዓመታት በፖለቲካ፣በማኀበራዊ፣በኢኮኖሚ ፣በስፖርት፣በሃይማኖት፣በፍቅር፣ በኪነጥበብ እና በመሳሰሉት ርዕሰ ጉዳዮች አተኩረው ይታተሙ ከነበሩ 235 የፕሬስ ውጤቶች መካከል 196 ያህሉ በተለያየ ምክንያት ከህትመት ውጪ መሆናቸውን የብሮድካስት ባለስልጣን ሰሞኑን በድረገጹ በለቀቀው መረጃ አስታወቀ፡፡

ባለስልጣኑ ከየካቲት 2001 እስከ ጥር 2005 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ለ91 ጋዜጦችና ለ144 ያህል መጽሔቶች በድምሩ ለ235 ያህል የፕሬስ ውጤቶች የምዝገባ የምስክር ወረቀት መስጠቱን አስታውሶ ከነዚህ መካከል እስከ ጥር ወር 2005 ዓ.ም ድረስ መዝለቅ የቻሉት 18 ጋዜጦች እና 21 ያህል መጽሔቶች በድምሩ 39 ያህል የፕሬስ ውጤቶች ብቻ መሆናቸውን አመልክቷል፡፡

ባለስልጣኑ በአምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ በአስደንጋጭ መልኩ ፕሬሶቹ ከሕትመት ውጪ የሆኑበትን ዝርዝር ምክንያት ባያስረዳም ጠቅለል ያሉ ምክንቶችን ለማቅረብ ሞክሯል፡፡

በዚሁ መሰረት 15 የሕትመት ውጤቶች ፈቃድ ከወሰዱ አንድ ዓመት በታች በመሆናቸው በዝግጅት ላይ መሆናቸውን፣ 81(42 ጋዜጦች፣39 መጽሔቶች) በራሳቸው ፈቃድ ስርጭት ማቋረጣቸውን፣ 89 (27 ጋዜጦች እና 62 መጽሔቶች) ፈቃድ ወስደው ወደሕትመት ስራ ሳይገቡ ከአንድ ዓመት በላይ በማስቆጠራቸው በሕጉ መሰረት መሰረዛቸውን አመልክቷል፡፡

በያዝነው የካቲት ወር 2005 ዓ.ም “መሰናዘሪያ” እና “አዲስታይምስ” የተባሉ ጋዜጣና መጽሔት ከሕትመት ውጪ በመሆናቸው በሕትመት ላይ ያሉት ፕሬሶች ጠቅላላ ቁጥር ወደ 37 ዝቅ ያደርገዋል፡፡

ባለስልጣኑ በአሁኑ ወቅት በሕግ ከተሰጠው ኃላፊነት ውጪ የፕሬስ ምዝገባ ጥያቄ ሲቀርብለትና ዓመታዊ የፈቃድ እድሳት የብቃት ማረጋገጫ በሚጠየቅበት ወቅት አንዳንድ አሳታሚዎችን የተለያዩ ምክንያቶችን በማቅረብ የምዝገባ የምስክር ወረቀት የሚከለክልበት አሰራር ሕጋዊና ተቋማዊ አድርጎ በመንቀሳቀስ ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡

በቅርቡም “አዲስታይምስ” የተባለውን መጽሔት ዓመታዊ እድሳት የሙያ ማረጋገጫ ፈቃድ በመከልከሉ መጽሔቱ ከሕትመት ውጪ መሆኑ ይታወቃል፡፡

በኢትዮጽያ በፕሬስ የመሰማራት መብት በሕገመንግስት ተረጋግጧል ቢባልም አስፈጻሚው አካል እያካሄደ ባለው ግልጽና
ስውር ተጽዕኖ ምክንያት በርካታ ጋዜጦችና መጽሔቶች ከሕትመት ውጪ ከመሆናቸውም ባሻገር ወደዘርፉ ለመግባት ፍላጎት
ያላቸውን ወገኖች ስራውን ሳይጀምሩት ተስፋ ቆርጠው የሚወጡበት ሁኔታ የመኖሩ ጉዳይ በዓለም ዓቀፍ ተቋማት ጭምር
በየጊዜው አቤቱታ የሚቀርብበት መሆኑ ይታወቃል፡፡

ተከራካሪውን በማህበራዊ ፍርድ ቤት ውስጥ በሽጉጥ የገደለው ፖሊስ አልተያዘም


ድርጊቱ የተፈጸመው ከአንድ አመት ከስድስት ወር በፊት በአስኮሪ ከተማ ነበር። ወ/ሮ ወርቅነሽ ኢፋ የተባሉ አርሶአደር በ2002 ዓም የልማት ጀግና ተብለው ተሸልመዋል። ወ/ሮ ወርቅነሽ ሳጂን ኣካለወልድ ተክለማርያም የተባለ የእንጀራ ልጅ አላቸው።

 ግለሰቡ የእንጀራ እናቴ በአደራ የሰጠሁዋትን መሬት ክዳለች በሚል በፍርድ ቤት ክስ መሰረተ። ከፍተኛው ፍርድ ቤትም ለሳጅን አካለወርድ መፍረዱን ተከትሎ ወ/ሮ ወርቅነሽ ስድስት ኪሎ በሚገኘው የኦሮሚያ ሰበር ሰሚ ችሎት ይግባኝ ጠይቀው፣ ይፈረድላቸዋል። የፍርድቤቱ ውሳኔ በማህበራዊ ፍርድ ቤት በኩል እንዲፈጸም በተሰጠው ውሳኔ መሰረት፣ ማህበራዊ ፍርድ ቤቱ ተሰይሞ ሳጅን አካለወልድ መሬቱን እንዲያስረክብ ይጠይቃል።

 ሳጅኑም ብድግ ብሎ በጃኬቱ ውስጥ ሸፍኖ ያስቀመጠውን ሽጉጥ በማውጣት የሴትዮዋን ልጅ የ41 አመቷን ወ/ሮ ብርቅነሽ ተክለማርያምን ይመታቸዋል።

 ወ/ሮ ወርቅነሽ የልጃቸውን መመታት ሲያዩ በላዩ ላይ ሄደው በመውደቅ ሊከላከሉ ሲሞክሩ እሳቸውንም በሽጉጥ ይመታቸዋል። በሁኔታው የተደናገጡት የፍርድ ሸንጎው አባላት ተቃውሞ ሲያቀርቡ በእነሱም ላይ ለመተኮስ ቃታውን ሲስብ መሳሪያው ነክሶበታል።

  በዚህም ሌሎች ሰዎች ከመመታት ይድናሉ፣ የሟች ልጅ ኤደን ብርሀኑ ለኢሳት እንደገለጠችው
የሰው ነፍስ ያጠፋ ሰው የዋስትና መብት እንደማይሰጠው ህጉ ቢደነግግም፣ በፖሊስ ሳጅን አካለወልድ ግን ወዲያውኑ በገንዘብ ዋስ እንዲለቀቅ ተደርጓል።

 የሟች ቤተሰብም ጉዳዩን ወደ ዞን ፍርድ ቤት በመውሰድ ገዳይ እንዲቀርብ ቢያስወስንም፣ አቃቢ ህጉና ፖሊስ ግለሰቡን ልናገኘው አልቻልንም የሚል መልስ ለፍርድ ቤት በመስጠት ግለሰቡ ላለፈው አንድ አመት ከ6 ወር ያክል ጊዜ ፍርድ ቤት እንዳይቀርብ ማድረጉን ኤደን ተናግራለች።

ፖሊሶቹ የገዳይ ወገኖች በመሆናቸው ሳጅን አካላወልድን እንደለቀቁት ኤደን ተናግራለች።
ግለሰቡ ሳሪስ አካባቢ እንደነበር የገለጠችው ኤደን በአሁኑ ጊዜ ናዝሬት ከተማ ውስጥ ያለምንም ችግር እንደሚኖር ሰዎች እንደነገሯት ገልጻለች።

ሟች እናት ወጣት ኤድንን ጨምሮ አንድ ሌላ የ12 አመት ልጅ እንደነበራቸው ታውቋል።
የመንግስት ባለስልጣናት በአገሪቱ ውስጥ የተለያዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን እየፈጸሙ በነጻ የሚለቀቁበት አሰራር በስፋት እየታየ ነው።

የኦሮሚያ ፖሊስ ጽ/ቤትን አስተያየት ለማወቅ ተደጋጋሚ የስልክ ጥሪ ብናደርግም ምላሽ ለማግኘት አልተቻለም።

በስደት ላይ የሚገኘው ሲኖዶስ አዲስ የሚሾሙትን ፓትሪያርክ ህዝቡ እንዳይቀበል ጥሪ አቀረበ


ሲኖዶሱ ለኢሳት በላከው መግለጫ አገሪቱን እስር ቤት አድርጎ ህዝቡን በባርነት ለመግዛት የተነሳው ሀይል የቤተ ክርስቲያንን ሀዋርያዊና የነጻነት አንደበት ለመዝጋት ከሚጠቀምባቸው መንገዶች ተቀዳሚውና ዋነኛው ለህገ ቤተክርስቲያን ሳይሆን ለራሱ ፈቃድ ተገዢ የሆነ ሰው በፓትሪያርክ ስም በቤተ ክርስቲያን መንበር ላይ በማስቀመጥ ቤተክርስቲያንን መድፈር ነው ብሎአል።

ሲነዶሱ ” ላለፉት 21 አመታት በመንግስት አስተባባሪነትና ደጋፊነት በህገ ወጥ መንገድ በተቀመጡት አባት ምክንያት ቤተ ክርስቲአንን ክፉኛ የጎዳው መከፋፈል እና መለያየት ሳያንስ አሁን ደግሞ እነዚህ ጥቂት {አ{አሳት በስልጣን አለውን የመንግስት ሀይል መከታ አድርገው ፓትሪያርክ ብለው የሚሰይሙትም ፣ አባትነቱ የሀሰት አባት፣ ሹመቱም የሲሞ ን መሰርኢ ስለሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ አጥብቆ ያወግዘዋል።

 በተለይም ለቤተክርስቲያን ሰላምና አንድነት ከፍተኛ መስዋትነት በመክፈል የቆሙ እውነተኛዎቹ አባቶች በዚህ ሂደት ውስጥ ተሳታፊዎች ሆነው በታሪክም በእግዚአብሄርም ተወቃሾች እንዳይሆኑ” ጥሪ አቅርቧል።

ሲኖዶሱ የቤተከርስቲያን ልጆች በአንድነት የሚቆሙበት ጊዜ አሁን መሆኑም በአጽንኦት ገልጿል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኖርዝ ካሮላይና ቤተክርስቲያን በአቡነ መርቆርዮስ የሚመራውን ሲኖዶስ እንደሚደግፍ አስታውቋል።

የኖርዝ ካሮላይና መካነ ብርሀን ቅድስት ስላሴ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ለኢሳት በላከው መግለጫ ፣ ላለፉት 13 አመታት በገለልተኝነት ከሁሉም የአስተዳደር መዋቅር ውጭ ሆኖ ቢቆይም፣ አሁን ግን በብጹወ ቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ በሚመራው ህጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚተላለፈውን አመራር እንደሚቀበል አስታውቀዋል።

በአዲስ አበባ እየተከናወነ አለው ህገወጥ የስድስተኛ ፓትሪያርክ ሲመት የቤተ ክርስቲያን የሰላም በር የሚዘጋ በመሆኑና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን የመከራና ልዩነት ዘመን የሚያረዝም በመሆኑ ፣ ምርጫውን አጥብቆ እንደሚቃወም ገልጿል።

ከቀኖና ቤተክርስቲያን አኳያ በስደት አለም የሚገኙት 4ኛው ፓትሪያርክ ብጹወ ቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ርእሰ ሊቃነጳጳስ መሆናቸውን እንደሚቀበል መግለጫው አመልክቷል።

tirsdag 26. februar 2013

በብራሰልስ የኢሳት የገቢ ማሰባሰብ ዘግጅት ተካሄደ



እውቁ አርቲስትና የሰብአዊ መብት ተሟጋች ታማኝ በየነ በተገኘበት ትናንት የካቲት 17፣2005 ዓም የተካሄደው የኢሳት የገቢ ማሰባሰብ ዝግጅት በቤልጂየም የሚኖሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ተገኝተዋል።

ከሰአት በሁዋላ የተጀመረው ስብሰባ የተከፈተው በቤልጂየም የኢሳት የገቢ አሰባሳቢ ግብረሀይል ወኪል በሆኑት በአቶ ገበየሁ ደስታ ነበር። በመቀጠልም ሌላው የኮሚቴ አባል አቶ ኤፍሬም ሻውል ኢሳት ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚሰጠውን ግልጋሎት የተመለከተ ጥናታዊ ወረቀት አቅርበዋል።

 አቶ ኤፍሪም እንደገለጡት ኢሳት መረጃ ከመስጠት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታየውን ሙስና ፣ የሰብአዊ መብቶች ጥሰትና የመልካም አስተዳደር እጦት ከማጋለጥ ባሻገር የኢትዮጵያውያን የትግል መንፈስ የማነቃቃት ሚና እየተጫወተ ነው።

ከአቶ ኤፍሪም በሁዋላ ንግግራቸውን ያቀረቡት የአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባል እና በኢትዮጵያ የነጻነት ትግል ውስጥ ከፍተኛ ቦታ የያዙት የተከበሩ ሚስ አና ማርያ ጎሜዝ ተወካይ ናቸው።

 ክብርት አና ጎሜስ በጽሁፍ ባስተላለፉት መልእክት የኢትዮጵያ መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽማቸውን የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በዝርዝር ከገለጹ በሁዋላ ተቃዋሚዎች ልዩነቶቻቸውን ወደ ጎን ትተው በአንድነት በመቆም፣ ለውጥ እንዲያመጡ ጥሪ አቅርበዋል።

 ሚስ አና ጎሜዝ ተቃዋሚዎች በህብረት ከታገሉ ገዢውን ሀይል በማስወገድ ሁላችንም መስቀል አደባባይ ላይ ተገናኝተን ድላችንን የምናከብርበት ጊዜ እሩቅ አይሆንም ብለዋል።

ሌላው ተናጋሪ በቤልጂየም የሉቅማን ኢትዮጵያውያን ቤልጂየማውያን ማህበር ሊቀመንበር የሆኑት አቶ አብየ ያሲን ሲሆኑ፣ አቶ አብየ በአሁኑ ጊዜ በምርጫ 97 ወቅት ባልተናነሰ በሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ በፊዲዮ አስደግፈው አቅርበዋል።

በእለቱ የብዙዎችን ስሜት የነካ ንግግር ካቀረቡት ተናጋሪዎች መካከል የአፋር ህዝብ ፎረም ሊቀመንብር አቶ ጋአስ አህመድ አንዱ ነበሩ። ” አቦይ ስብሀት አፋርን ኢትዮጵያዊነቱን ያስተዋወቅነው እኛ ነን” በማለት የተናገሩትን ያወሱት አቶ ገአስ፣ “ኢትዮጵያን የሰው ልጅ መገኛ አገር ያስባለቻት ሉሲ የተገኘችው ከአፋር ምድር ነው፣ እንዴት ነው ታዲያ አቶ ስብሀት ለአፋር ኢትዮጵያዊነቱን ያስተዋወቁት?” በማለት ጠይቀዋል።

' እንዲሁም ” አፋሮችን ከሽርጥ አውጥተን ሱፍ ያለበስናቸው እኛ ነን ይሉናል ያሉት አቶ ገአስ፣ “ለእኔ ግን ሱፉ ቀርቶብኝ ነጻነቴን ሰጥተውኝ በሽርጤ ብኖር ይሻለኛል።

” በማለት በአፋር ክልል እየተፈጸመ ያለውን የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ዘርዝረዋል።

የእለቱ የክብር እንግዳ የሆኑት አርቲስቲትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ፣ የቤልጂየም የኢሳት ኪሚኒቲ ባዘጋጀለት ሊሞዘን ወደ አዳራሹ ሲመጣ፣ የአፋር ወጣቶች ጊሌያቸውን በመያዝ ውብ በሆነ ባህላዊ ጭፈራ ተቀብለውታል።


 ወጣቶቹ አርቲስቱን አጅበው ወደ አደራሹ ከገቡ በሁዋላ የተለያዩ የአፍርኛ ሙዚቃዎችን ለተመልካቹ ተጫውተዋል።

አርቲስት ታማኝ የተመልካቹን ስሜት ሙሉ በሙሉ በገዛበት ንግግሩ በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በአገራቸው ፍርተው ተሰደው፣ በውጭ አገርም በፍርሀት እንደሚኖሩ፣ ፍርሀቱም እየደረሰብን ላለው መከራ አስተዋጽኦ ማድረጉን ተናግሯል ።


በእለቱ ከጫረታ ከ5 ሺ ዶላር ያላነሰ ገንዘብ ተሰብስቧል።

የ6ኛው ፓትርያርክ እጩዎች ምርጫ አከራካሪ እንደሆነ ቀጥሏል


የ6ኛው ፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴ በእጩነት ባቀረባቸው 5 ሊቃነ ጳጳሳት ዙሪያ ተወያይቶ ለማፅደቅ ባሳለፍነው ቅዳሜ የተሰበሰበው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስሲኖዶስ ምልአተ ጉባዔ፣ ያለ አንዳች ውሳኔ መበተኑ ታወቀ።

እንደ ሃራ ተዋሕዶ ብሎግ ዘገባ የዕለቱ የቅዱስ ሲኖዶሱ ጉባዔ፣ በተለይም ለእጩነት በቀረቡት አባቶች መካከል ከረር ያለ የቃላት ልውውጥ የተስተናገደበት፤ ዋና ጸሐፊውን ተክቶ የኮሚቴውን ሪፖርት ያቀረበውየሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው አቶ ባያብል ሙላቴ ለቅ/ሲኖዶሱና ለአጀንዳው ታላቅነት የማይመጥን፣ እንዲሁም ውክልናውና ያጸደቀለትን ማህበሩን የሚያስንቅና የሚያስወቅስ ደርዝ የሌለው ንግግር የተደመጠበት፣ ኮሚቴውም ከብፁዓን አባቶች ለቀረቡለት ጥያቄዎች የተረጋገጠ መልስ ሊሰጥ ያልቻለበት ነበር፡፡

በጉባዔው ላይ አምስቱ ዕጩዎች የተመረጡት የትውልድ አካባቢያቸውን መሰረት በማድረግ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን፣ እነርሱም ከትግራይ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፣ ከጎንደር ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ከወሎ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣ ከሸዋ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ እና ከኦሮሚያ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ናቸው። ይህም ምርጫው የተደረገው የተሿሚውን መንፈሳዊ ብቃት ከግምት በማስገባት ሳይሆን የዘመኑ ፖሊቲካዊ አስተሳሰብና ጎጠኛ ስሜት ላይ ተመስርቶ ለመኾኑ ማረጋገጫ ሆኖ ተገኝቷል ተብሏል።


በዚሁ ስብሰባ ላይ ለአስመራጭ ኮሚቴው ከቀረበሉት ጥያቄዎች አንዱ ‹‹መንግሥት ጣልቃ ገብቷል ወይስ አልገባም?›› የሚል ሲሆን ከኮሚቴው አባላት አንዳቸውም ቢሆኑ ለጥያቄው ምላሽ ሊሰጡ እንዳልደፈሩ ታውቋል፡፡

 ከሕዝብ ግንኙነት ሃላፊው በስተቀር ሌሎቹ የኮሚቴው አባላት በስብሰባው ላይ ብዙም ለመናገር ፈቃደኞች እንዳልነበሩ የተገለፀ ሲሆን፣ የኮሚቴው ዋና ፀሃፊ የሆኑት ሊቀ ማእምራን ፈንታሁን ሙጬ “አሞኛል” በማለት በኮሚቴው ውስጥ መታየት ካቆሙ የሰነባበቱ ሲሆን፣ የታዋቂ ምዕመናን ተወካይ የተባሉት ቀኝ አዝማች ኀይሉም ራሳቸውን ማግለላቸው ይነገራል። በዚህም የተነሳ ኮሚቴው በዕጩዎቹ ማንነት

ላይ በአንድ ድምፅ፣ ያለልዩነት የተፈራረመበት ቃለ ጉባኤ ስለመኖሩ ለቅዱስ ሲኖዶሱ የቀረበ ማስረጃ አለመኖሩ ታውቋል።


በዚሁ የፓትርያርክ ምርጫ የሕወሃት መንግስትን ይሁንታ አግኝተዋል የተባሉት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ሲሆኑ፣ ይህንኑ ጠንቅቀው የተገነዘቡት ሌሎቹ 4 ሊቃነ ጳጳሳትእኛ የታጨነው ለአጃቢነት ብቻ ነው!” በማለት በጉባዔው ላይ የተለያየ ሃይለ-ቃል ሲናገሩ ተደምጠዋል።



በዚህም መሰረት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ÷‹‹በአበው ገዳማዊ ሥርዐት በዕጩነት መመረጥ አይገባኝም፤ እንኳን አይደለም ፕትርክናው ጵጵስናውም ከብዶኛል፤ ይህን ነገር ከሰማኹ ጀምሮ ብርክ ይዞኛል፤ እኔን ተዉኝ፤ እኔ እጠፋለኹ፤›› ያሉ ሲሆን ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል‹‹ያው አጃቢ ነን፤ እናየዋለን›› ማለታቸው ተሰምቷል። ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ በበኩላቸው÷ ‹‹እኛ መናጆ ተብለን ነው የገባነው፤ የሚመረጠው አባ ማትያስ ነው፤ ያኔ በዕጣ ይኹን ብዬተከራክሬ ነበር፤ የኾነ አካል አባ ማትያስን አምጥቶ ያስቀምጣል፤ እኔ መናጆ አልኾንም፤ ይህ መንፈስ ቅዱስ የተለየውና ሥርዐተ ቤተክርስቲያን ያልጠበቀ ምርጫ ነው።

» በማለት በአጽንዖት ተናግረዋል፡፡


አጠያያቂ ስለሆነው የብፁእ አቡነ ማትያስ አሜሪካዊ ዜግነታቸው ጉዳይ በብፁዕ አቡነ ገብርዔል እና በብፁዕ አቡነ አብርሃም ጥያቄ ቀርቦላቸው አሜሪካዊ ዜግነቴን መልሻለሁ ብለዋል፡፣ ሆኖም ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚሉ ከኾነ ማረጋገጫው ፓስፖርቱ ነው፤ ፓስፖርቱን ያምጡ? የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው የተጠየቁትን ማቅረብ አልቻሉም። እንደሚታወቀው «ቤተክርስቲያኗ በቅርቡ ባፀደቀችው የምርጫ ሕግ መሰረት ለፓትርያርክነት የሚመረጥ ሰው በዜግነት ኢትዮጵያዊ የሆነ እድሜውም ከ50 ዓመት ያላነሰ ከ75 ዓመት በላይ ያልበለጠ መሆን አለበት የሚል ድንጋጌ የተቀመጠበት ሲሆን ይህም ሆን ተብሎ የተካተተው አቡነ ማትያስን ከምርጫው ለማስወጣት እንደሆነ ሲነገር ነበር።



ፓትርያርክ ለመሰኘት የቤተክርስቲያኗን ገንዘብ ለቅስቀሳና ለማግባባት አውለዋል በመባል የሚታሙት ብፁዕ አቡነ ሳሙዔልም የብፁዕ አቡነ ማትያስ ዜግነት ጉዳይ ሳይጣራ ከዝርዝሩ ውስጥ መግባታቸውን በመኮነን ለዕጩነት መቅረባቸው አግባብ አይደለም ሲሉ ኮንነዋል። ባጠቃላይ የቤተክርስቲያኗ አባቶች ምርጫውን አስመልክቶ ያላቸው የተከፋፈለ አቋም፣ እንዲሁም እያሰሙት ያለው ቅሬታና ተቃውሞ 6ኛ ፓትርያርክ ተብሎ የሚሾመው ሊቀ ጳጳስ የሚኖረውን ተቀባይነት ከወዲሁ ጥያቄ ውስጥ የሚከተው ሆኖ ተገኝቷል።


አስቀድሞ ለምርጫው በወጣው መርሃ ግብር መሰረት ቅዱስ ሲኖዶሱ በአስመራጭ ኮሚቴው የቀረቡለትን አምስት እጩዎች ዛሬ ለሕዝብ ይፋ ያደርጋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ይህንኑ ተከትሎም የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ በመጪው ሓሙስ የካቲት 21 ቀን 2005 . ተደርጎ በዓለ ሲመቱ የካቲት 24 ቀን እንደሚከናወን ታውቋል ሲል ቅዱስ-ሀብት በላቸው ከአውስትራሊያ ዘግቧል።

ስድስተኛ ፓትርያር ለመሾም የሚደረገውን ጥድፊያ አጥብቀው እንደሚቃወሙ በኒውዮርክና አካባቢው የሚገኙ የ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመናን አስታወቁ


ምዕመናኑ ባወጡት መግለጫ ስድስተኛ ፓትርያርክ ለማስቀመጥ በአገር ቤት እየተደረገ ያለውን ጥድፊያ እንደሚቃሙትና በውጪ የሚገኘው ሲኖዶስ በጉዳዩ ዙሪያ ያወጣውን መግለጫ እንደተቀበሉት ገልጸዋል።

ይህን ያደረጉትም አንዱን ወገን አግልለው አንዱን ወገን ለመደገፍ ሳይሆን መጽሐፍ ፦<<እውነትን የሚፈልግ ልብ ደስ ይበለው>>ባለው መሰረት ከሁለቱም ወገን የተባሉትን እና እየሆነ ያለውን ነገር ከሥረ-መሰረቱ በመመርመር እንደሆነ አስረድተዋል።

<<በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው በደል ያስከተለው ሀዘንና ጉዳት በቀላሉ ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም>> የሚለው የምዕመናኑ መግለጫ፤ የቤተ
ክርስቲያኑ ካህናትና ምዕመናን ላለፉት ሃያ አንድ ዓመታት ዕርቀ ሰላም እንዲወርድና ሕገ ቤተክርስቲያን እንዲከበር ሲመኙና ሲጸልዩ እንደኖሩ ያወሳል።


ከዚህም ባሻገር የቤተክርስቲያኒቱ የቁርጥ ቀን ልጆች፦<< የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው>> በሚለው አማናዊ ቃል መሰረት የሰላምና የአንድነት ጉባኤ በማቋቋም በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ባሉት አባቶች መካከል ዕርቅ እንዲፈጠርና ቀኖና ቤተክርስቲያንም እንዲከበር ያላሰለሰ ጥረት ማድረጋቸውን ያወሳው መግለጫው፤ይህም በጎ ተግባራቸው ሲያስመሰግናቸው ይኖራል ብሏል።


ይሁንና የመጨረሻው ድርድር ፍፃሜ ሳያገኝ ከአዲስ አበባው ሲኖዶስ የተሰማው ድምፅ ካህናቱንና ምዕመናኑን ከበፊቱ ለከፋ ሀዘን ዳርጎታል ያሉት የኒውዮርክ ምዕመናን፤ይህንም ተከትሎ ከህጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ሰፊ መግለጫ መሰጠቱን ጠቁመዋል።


<<እኛም በኒውዮርክና በአካባቢው የምንገኝ ምዕመናን ከሁለቱም ወገን የተሰጡትን መግለጫዎች በጥልቅ በመመርመር እውነትን <የሚፈልግ ልብ ደስ ይበለው> ተብሎ እንደተጻፈ በውጭ ሀገር በሚገኘው ሕጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠውን መግለጫ ሙሉ በሙሉ በመደገፍና በውስጡም የተሰጡትን መመሪያዎች በሥራ ላይ ለማዋል ቆርጠን ተነሥተናል>> ሲሉም አቋማቸውን አሳውቀዋል።


ምዕመናኑ ይፋ ባደረጉት ባለ አራት ነጥብ የአቋም መግለጫ ላይ

<<ባለፉት 21 ዓመታት ፓትርያርክ በህይወት እያለ ሌላ ፓትርያርክ በመሾሙ ሳቢያ ያስከተለውን ጥፋት በማረምና በማስተካከል፣ የተፈጠረውንም ታሪካዊ አጋጣሚ ተጠቅሞ ህጋዊውን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስን ከነሙሉ ክብራቸው ወደ መንበራቸው በመመለስ ፋንታ፤ በጥፋት ላይ ጥፋት እንዲሉ ሌላ ስድስተኛ ፓትርያርክ ለመሰየም የሚደረገውን ጥድፊያ እንቃወማለን፣ ተመራጩንም አንቀበልም።>>ብለዋል።


የተለያዩ መንፈሳዊ ጉባኤዎችን በማዘጋጀት፣ ማኅበረ ምዕመናኑ ስለቅዱስ ሲኖዶስ አመሠራረትና ስለ ቀኖና ቤተክርስቲያን መከበር አሰፈላጊነት ጥርት ባለ መንገድ እንዲገነዘብ በማድረግ፤ ለሀገራችን ለኢትዮጵያ ሰላም፤ ለቤተክርስቲያናችን ፍቅርና አንድነት በሙሉ ልብና በሙሉ ኃይል እንዲነሳ ያለሰለሰ ጥረት እናደርጋለን።ብለዋልም-የኒውዮርክ ምዕመናን።


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው የመከፋፈል አደጋ የኢትዮጵያና የውጪ በሚል ብቻ እንዳላበቃና <<ከሁለቱም ያልወገነ ገለልተኛ>> በሚል ስም የሚጠራ ሦስተኛ አካል እንዳለ የጠቆመው መግለጫው፤<< ቅድስት ቤተክርስቲያናችን አጣብቂኝ ውስጥ በገባችበት በአሁኑ ወቅት ሰላምና አንድነትን ዕውን ለማድረግ እርምጃ መውሰድ የግድ ይላል።

>>ብሏል።

ስለዚህም በሰላምና አንድነት ኮሚቴ አማካይነት በህጋዊው ሲኖዶስና በገለልተኛው ወገን መሀከል አንድነት ለመፍጠር ይቻል ዘንድ የዕርቅ ድርድሩ በአስቸኳይ እንዲጀምር ጠይቋል።


በመጨረሻም በህጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ሥር ያሉ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ከምን ጊዜውም በበለጠ የቅዱስ ሲኖዶሱን መመሪያዎች በሥራ ላይ ለማዋል የሚፋጠን ልዩ ኮሚቴ እንዲቋቋም መንፈሳዊ ምክራችንን እንለግሳለን፣ ያለው መግለጫው፤ በዚሁም መሠረት በኒውዮርክና በአካባቢው ቤተክርስቲያናት ልዩ ኮሚቴ ተቋቁሞ ሥራውን መጀመሩን አስታውቋል።

የደህንነት መስሪያ ቤት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች ከአገር እንዳይወጡ አዘዘ


የኢትዮጵያ አየር መንገድ 15 የትኬት እና 30 የኤርፖርት ሰራተኞችን ከስራ ካባረረ በሁዋላ ከአገር እንዳይወጡ አገደ።

 ከአየር መንገድ የውስጥ ምንጮች የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ሀብታሙ ጫኔ፣ ዳንኤል ገበየሁ፣ ኢማን ያሲን፣ ኤደን ካሳየ፣ ቤዛ ኤፍሬም፣ ይገርማል ታደሰ፣ ሰለሞን ይብራህ፣ ክንፈ ሚካኤል ሽጉጤን ጨምሮ በርካታ ሰራተኞች ከስራ የተባረሩ ሲሆን ፣ አየር መንገዱ ለደህንነት እና አሚግሬሽን መስሪያ ቤት በጻፈው ደብዳቤ ሰራተኞቹ ከአገር እንዳይወጡ አሳግዷል።

ሰራተኞቹ ከአገር እንዳይወጡ ሲታገዱ ከተዘረዘሩት ምክንያቶች መካከል ለህዳሴው ግድብ ገንዘብ ለማዋጣት ፈቃደኛ አለመሆን፣ የድርጅቱን ሚስጢራዊ መረጃዎች የአገር ጠላት ለሆኑት የሽብርተኞች ሚዲያዎች ለኢሳት እና ለፍትህ ጋዜጣ መስጠታቸው፣ እንዲሁም የባለራእዩን መሪ የአቶ መለስ ዜናዊን ራእይ ለማሳካት በሚል የተነደፈውን የስድስት ቀን የነጻ የስራ አገልግሎት እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ አለመሆን የሚሉት ይገኙበታል።

 የሰራተኞቹ ፓስፓርት ቁጥር ለኢሚግሬሽንና ደህንነት ክፍል በመላኩ ሰራተኞች ከአገር ለመውጣትና ራሳቸውን ለማዳን አልቻሉም።

ከዚህ ቀደም ከስራ ከተባረሩት መካከል ከሙስሊሙ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የታሰሩት ሰባ ማይልስ ስራ አስኪያጅ እስካሁን አልተፈቱም።

አካሉ አሰፋ፣ አንተሰናይ አማረ፣ ቤተልሄም ተፈራ፣ ቤተልሄም ጌታቸው፣ ኤደን በየነ፣ ኤደን ካሳየ፣ ኢማን ያሲን፣ ሳሙኤል እንዳለ፣ ሶሎሞን በቀለ፣ አይዳ ዘልኡል፣ አማኑኤል በልስቲ፣ አማኑኤል ነጋሽ፣ አማኑኤል ጸጋው፣ አንዱአለም ግርማ፣ ብርሀኑ ሰሎሞን፣ ቸርነት አለሙ፣ እኑ ገብረእግዚአብሄር፣ ሀይማኖት ንጉሴ፣ ሂሩት መለሰ፣ ቅድስት አበራ፣ ቅድስት ከበደ፣ ማትያስ አድማሱ፣ መቅደስ አበራ፣ ሜላት አስራት፣ ትንግርት ደምሴ፣ ሳምራዊት ገረመው፣ ሰሚራ አማን፣ ተዘራ ወርቁ፣ ወንዶሰን ሀብቴ፣ ዮሀንስ ፍሰሀ እና አልአዛር ተክለ ሚካኤል ከአገር እንዳይወጡ ትእዛዝ ከተላለፈባቸው መካከል ይገኛሉ።

የተባረሩ ሰራተኞችን በተመለከተ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስራ አስኪያጅን ለማነጋገር ተደጋጋሚ የስልክ ሙከራ ብናደርግም አልተሳካልንም። አየር መንገዱ ነባር ሰራተኞችን እያባረረ በታማኝ የኢህአዴግ አባላት እየተካ መሆኑን በተደጋጋሚ መዘገባችን ይታወሳል።

søndag 24. februar 2013

በብራሰልስ የሚካሄደው የኢሳት ገቢ ማሰባሰቢያ ቅድመ ዝግጅት በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ዘጋጆች ገለጹ


እውቁ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አርቲስት ታማኝ በየነ የሚሳተፍበት በቤልጂየም ብራሰልስ የኢሳት ገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት በጥሩ ሁኔታ ሲካሄድ መሰንበቱን የዝግጅቱ አስተባባሪ የሆኑት አቶ ገበየሁ ደስታ ለኢሳት ገልጸዋል።

በቤልጂየም የኢትዮጵያውያን ኮሚቴ ማህበር ከኢሳት የቀረበለትን የትብብር ጥያቄ ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆኑ እንዳሳዘናቸው አቶ ገበየሁ አልሸሸጉም ።

የኢሳት የገቢ መሳባሰቢያ አዘጋጆች ለማህበሩ ያቀረቡት ጥያቄ ፣ የኮሚኒቲውን ኔት ወርክ በመጠቀም ጥሪውን እንዲያስተላልፉላቸው የሚጠይቅ ነበር።

ጉዳዩን በማስመልከት በቤልጂየም የኢትዮጵያ ማህበር ሊቀመንበር ለሆኑት ለአቶ ያሬድ ሀይለማርያም እና ለዋና ጸሀፊው ለጀርመን ድምጽ ዘጋቢው አቶ ገበያው ንጉሴ ጥያቄ ብናቀርብም፣ መሪዎቹ በጽሁፍ ካልሆነ በስተቀር በቃል መልስ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ገልጸዋል።

የኮሚቴው መሪዎች የኢሳትን ጥያቄ ለመቀበል ያልፈቀዱት ኢሳት ገለልተኛ ሚዲያ ነው ብለው ባለማመናቸው መሆኑን ተናግረዋል። ኢሳት ከተለያዩ ወገኖች የሚሰነዘርበትን ትችት በአግባቡ ባለማስተባባሉ እንዲህ አይነት አመለካከት ለመያዝ እንዳስገደዳቸው ገልጸዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ አስተያየቱን የጠየቅነው ጋዜጠኛ ፋሲል የኔአለም፣ ሊ/መንበሩ አቶ ያሬድ ሀይለማርያም በተደጋጋሚ በኢሳት ላይ ቀርበው ቃለምልልስ መስጠታቸውን አስታውሶ፣ “ቃለ ምልልስ ሲሰጡ የኢሳት ገለልተኝነት ጥያቄ አልታያቸውም ነበር፣ ዛሬ እርዳታ ስንጠይቃቸው ግን የገለልተኝነት ጥያቄ አነሱ፣ ለማንኛውም ግለሰቦች የመሰላቸውን አመለካከት መያዝ ይችላሉ፣ መንግስትም አሸባሪ ማለቱን መርሳት የለብንም ” ብሎአል።

ጋዜጠኛ ፋሲል “ኢሳት ገለልተኛ ሚዲያ ነኝ የሚለው ከእምነት ተነስቶ እንጅ ለጊዜያዊ ጥቅም ብሎ አለመሆኑን ገልጾ፣ አላፊ አግዳሚው ለሚያናፍሰው አሉባልታ ኢሳት መልስ ለመስጠት ጊዜውም ፍላጎቱም የለውም፤ ጊዜው ተረት ተረት የምናወራበት ሳይሆን፣ ታሪክ የምንሰራበት ነው” ሲል ተናግሯል።

የቤልጂየም የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ነገ እሁድ ፌብሩዋሪ 24፣ 2013 ይካሄዳል።

ካኤልም- ኤር ፍራንስ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርገውን በረራ ሰረዘ


የኔዘርላንድስ አየር መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርገውን በረራ የሰረዘው አትራፊ ባለመሆኑ ነው ብሎአል።

ድርጅቱ ለሪፖርተር እንደገለጠው ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርገውን በረራ ከተለያዩ አየር መንገዶች በገጠመው ውድድር እንዲሁም የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ በማሳየቱ ለመሰረዝ ተገዷል።

“ወደ ኢትዮጵያ የምናደርገው በረራ አትራፊ አይደለም” ያሉት የካኤል ኤም የኢትዮጵያና የሱዳን ወኪል ሚ/ር ዲክ ቫን ኒወንሀውዘን፣ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርጉትን በረራ ሸሪክ በሆነው በኬንያ አየር መንገድ በኩል እንደሚያስተናግዱ ገልጸዋል።


 ካ ኤል ኤምን ጨምሮ አራት አየር መንገዶች ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርጉትን በረራ ሰርዘዋል።


ካኤል ኤም በ90 አገራት በረራ የሚያካሂድ ሲሆን በአለም ላይ ካሉት አየር መንገዶች ቀደምት ነው።

ፓትሪያርክ ለማሾም የሚደረገ ው የምረጡኝ ዘመቻ ቀጥሏል


በኢትዮጵያ የኦርቶዶክስ ሀይማኖት ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ፣ የፓትሪያርክ የምርጫ ቅስቀሳ በስፋት እየተካሄደ መሆኑን የሀይማኖት አባቶች ገለጹ። ሰሞኑን በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀን ሲዘገብ የቆየውን የፓትሪያርክ የምርጫ ቅስቀሳ፣ ፓትሪያርክ ይሆናሉ ተብሎ ባለፈው ሳምንት በተሰራጨው ዘገባ ላይ ስማቸው የተነሳው አቡነ ሳሙኤል አረጋግጠዋል።

አቡነ ሳሙኤል ለአዲስ አድማስ በሰጡት አጭር ቃለምልልስ እንደገለጡት በምርጫው ዙሪያ የተለያዩ ቡድኖች ተፈጥረው የምርጫ ቅስቀሳ እያካሄዱ መሆኑን አጋልጠዋል። አቡነ ሳሙኤል ” በየብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ቤት ፣ በእኔም ቤት ሳይቀር እየዞሩ እገሌን ካልመረጣችሁ፣ ካላስመረጣችሁ የሚሉ አካላት እንዳሉ ግልጽ ነው” ያሉት አቡነ ሳሙኤል ፣ “ስልጣን ባለው አካል መንፈሳዊ ስልጣንን ለመያዝ የሚደረገው ሽር ጉድ ሁሉ በፍትህ መንፈሳዊ፣ በቀኖና ቤተክርስቲያን የተወገዘ መሆኑን” በመግለጽ ድርጊቱን አውግዘዋል።

 እንዲህ ሆኖ የሚሾመው አባትም ቢሆን ሲመቱ ስጋዊ ሹመት ይሆንና በነፍስም በስጋም ያጎድለዋል፣ ያለጊዜውም ሊያስቀስፍ ይችላል በማለት አስጠንቅቀዋል። በመሆኑም ይላሉ አቡነ ሳሙኤል ” በምርጫው የሚሳተፉ ካህናትና መእምናን ለቤተ ክርስቲያንና ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ማሰብ መወሰንና መቆም ይገባቸዋል።”

አቡነ ሳሙኤል ባለፈው ሳምንት ” ፓትሪያርክ ሆነው ለመመረጥ ቅስቀሳ ጀምረዋል” የሚለውን የሰንደቅ ጋዜጣ ዘገባ አስተባብለዋል።

 ” ምረጡኝ ብየ አላልኩም፣ ምረጡኝ ብየ አላውቅም” ያሉት አቡነ ሳሙኤል፣ ይህንን የሚያስወሩት በምርጫው ዙሪያ የተደራጁ ቡድኖች ናቸው” ብለዋል። አቡነ ሳሙኤል ” ፓትሪያርክነት የአባትነት፣ የቡራኬ ስልጣን ነው፤ ለእኔ አገልጋይነት ይሻለኛል፤ አገልጋይ መሆን ነው እንጅ፣ አዛዥ፣ ገዢ፣ አሳሪ፣ አሳሳሪ መሆን አይደለም” በማለት ተናግረዋል።

አቡነ ሳሙአል ፓትሪያርክነት በ ” አዛዥነት፣ በገዢነት፣ በአሳሪና አሳሳሪነት የተመለከቱበት መንገድ ለውዝግብ ሳይዳርጋቸው እንደማይቀር ይታመናል።

አቡነ ሳሙኤል ቀጣዩ ፓትሪያርክ ይሆናሉ ተብሎ ከተገመተ በሁዋላ በእጩነት አለመቅረባቸው ከምርጫው ጋር በተያያዘ እየተፈጸመ ያለውን ሴራ እንደሚያሳይ ዘጋቢያችን ገልጿል። የአቡነ ሳሙኤል ንግግር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤትክርስቲያን የገባችበት የዝቅጠት ደረጃ ያሳያል ያለው ዘጋቢያችን፣ የእርስ በርስ መጣላለፍ፣ የስም ማጥፋት፣ ለገዢው ፓርቲ ሎሌ ሆኖ መቅረብ፣ መንፈሳዊነትን ረስቶ ለስጋ ማደር፣ ጥቅምን ማሳደድ፣ ዘረኝነት እና ንግድ” የቤተክርስቲያኑዋ መገለጫ እየሆኑ ነው ብሎአል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትሪያሪክ፤ መሠረተ ቢስ መረጃዎችን በማስተላለፍ ህዝቡን ለማደናገር ይሠራሉ በማለት ክስ የመሠረተባቸው አራት ጋዜጠኞች ማዕከላዊ ፖሊስ ጣቢያ ቀርበው ቃላቸውን ሰጡ፡፡

በስልክ ከፖሊስ በደረሳቸው ጥሪ መሠረት ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቀርበው የተከሳሽነት ቃላቸውን የሰጡት፤ የ “ሎሚ” መጽሔት፣ የ “ሊያ” መጽሔት፣ የ“አርሂቡ” መጽሔት እና የ “የኛ ፕሬስ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጆች ናቸው።

እንደ አዲስ አድማስ ዘገባ፤ጋዜጠኞቹ ፎቶግራፍ እና አሻራቸው ተወስዶ በዋስ ተለቀዋል፡፡

የ“ሎሚ”፣ የ “ሊያ” እና የ “አርሂቡ” መጽሔት ዋና አዘጋጆች ማክሰኞ የካቲት 12 ቀን 2005 ዓ.ም ለፖሊስ ቃል የሰጡ ሲሆን፤ የ “የኛ ፕሬስ” ዋና አዘጋጅ ደግሞ ሃሙስ የካቲት 14/ ቀን ቃሉን ሰጥቷል፡፡

የየኛ ፕሬስ ጋዜጣ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ ስዩም ለአድማስ እንደገለፁት፤ ዋ“ሲኖዶስ ተከፋፍሏል” እና “ስደተኛው ሲኖዶስ መግለጫ አወጣ” በሚሉ ርዕሶች በጋዜጣው ላይ በወጡ ዘገባዎች በዋና አዘጋጁ በካሳሁን ወልደዮሐንስ ላይ ክስ ቀርቦበታል፡፡

የ“አርሂቡ” መጽሔት ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ ካሣሁን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ በመጽሔቱ የታህሳስ ወር እትም ቁጥር 40 ላይ “አቡነ ማቲዎስና አቡነ ሣሙኤል ተፋጠዋል” በሚል ባወጣው ዘገባ ክስ ቀርቦባቸዋል።

በክሱ ዙሪያ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ አበራ የተከሳሽነት ቃሉን ሰጥቷል።

የ“ሎሚ” መጽሔት ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛው ታዬ እንዳሉት ደግሞ የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ የሆነችው ወ/ት ብዙአየሁ ጥላሁን በሶስት ርዕሰ ጉዳዮች ለቀረበባት ክስ ማክሰኞ ዕለት ቃሏን ከሠጠች በኋላ -እርሳቸው የመኪናቸውን ሊብሬ አስይዘው በዋስ አስለቅቀዋታል።

ዋና አዘጋጇ “መንግሥት በሃይማኖት፤ ሃይማኖትም በመንግስት ጣልቃ አይገባም” የሚለውን ህገመንግስታዊ ድንጋጌ በመጣስ፣ ህዝብ- በመንግስትና በቤተክርስቲያን አመኔታ እንዳይኖረው የሚያደርግና ህዝብን ለአመጽና ለሁከት የሚያነሳሳ ጽሑፍ አትማ አሠራጭታለች “ የሚሉ ክሶች የቀረቡባት ሲሆን ለሁሉም ክሶች ቃሏን መስጠቷን አቶ ግዛው ገልፀዋል፡፡

የ“ሊያ” መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ መላኩ አማረ በበኩላቸው፤ ስለ ጉዳዩ ዋና አዘጋጇ ብዙም የምታውቀው ስለሌለ እሣቸው የተከሳሽነቱን ቃል እንደሰጡና በክስ ዝርዝር መግለጫው ላይም ከሳሽ ሆነው የቀረቡት አቡነ ናትናኤል መሆናቸውን ተናግረዋል።

መጽሔቱ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቀጣይ እጣ ፈንታ ምንድነው?” በሚል በቁጥር 19 እትሙ ባቀረበው ዘገባ ክስ እንደቀረበባቸውም አቶ መላኩ ተናግረዋል፡፡

ጋዜጠኞችን በመክሰስ፣በማሰር፣በማዋከብና በማሳደድ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱትና የፕሬስ ጠላቶች ከሚባሉት አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንዷ እንደሆነች ዓለማቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተንከባካቢ ኮሚቴ(ሲፒጄ) በቅርቡ ያወጣው ሪፖርት ያመለክታል።

torsdag 21. februar 2013

አቡነ ሳሙኤል ለፓትሪያርክነት ለመመረጥ ቅስቀሳ መጀመራቸው ተዘገበ



የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን አወዛጋቢውን ጳጳስ አቡነ ጳውሎስን የሚተካ ስድስተኛው ፓትሪያሪክ ለማስመረጥ በዝግጅት ላይ ባለችበት በዚህ ወቅት ከዚህ የፓትሪያሪክ ምርጫ ጋር በተያያዘ የቤተ ክርስትያኒቷ የተራድኦ ኮሚሽን ሊቀጳጳስና ከዚህ ቀደም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በነበሩበት ወቅት ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ግጭት ውስጥ ገብተው የነበሩት አቡነ ሳሙኤል በቀጣዩ ምርጫ ስድስተኛው ፓትሪያሪክ ሆነው ለመመረጥ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን፣ የቤተክህነት አመራሮችን፣ የተለያዩ ሀገረ ስብከቶች ስራ አስኪያጆችንና ታዋቂ ግለሰቦችን በማግባባት ላይ መሆናቸው ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮቻችን ጋዜጣው ዘግቧል።

ሊቀ ጳጳሱ ለዚህ ይረዳቸው ዘንድ ከፍተኛ ገንዘብ መድበው እየተንቀሳቀሱ ነው የሚለው ጋዜጣው፣ በጥቅምት ወር በተካሄደው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን 31ኛው ጉባኤ ወቅት ተሳታፊ ለነበሩ ቁጥራቸው ወደ 900 የሚጠጋ ከተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የተሰባሰቡ ተሳታፊዎች 500 ሺህ ብር በአበል መልክ እንዲከፈል አድርገዋል።

 ይህም ለሚካሄደው የፓትሪያሪክ ምርጫ
ይጠቅማቸው ዘንድ ያከናወኑት መሆኑን ጋዜጣው ዘግቧል።

አያይዘውም ገንዘቡ በሶማሌ እና አፋር ክልሎች ለሚሰሩ የልማት ፕሮጀክቶች እንዲውል ከእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች የተገኘ እንደሆነና ተሳታፊዎቹም ከየሀገረ ስብከታቸው አበል ተከፍሏቸው የመጡ መሆናቸው ነገር ግን አቡነ ሳሙኤል ተወዳጅነት ለማግኘት ሲሉ የልማት ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስነታቸውን በመጠቀም ገንዘቡ ለተሳታፊዎች እንዲበተን ማድረጋቸውን ዘገባው ያመለክታል።

በዚህ የምረጡኝ ዘመቻቸው ወቅት ድምፅ ለሚሰጡዋቸው እና ከጎናቸው ለሚሆኑ ሰዎች ፓትሪያሪክ ሆነው ከተመረጡ በኋላ በተሻለ የኃላፊነት ቦታ እንደሚሾሟቸው፣ ለቤተሰቦቻቸው የውጭ ዕድል እንደሚያመቻቹላቸውና ቤተ ክርስትያኒቷ በተለያዩ የአዲስ አበባ አካባቢዎች በምታስገነባቸው ህንፃዎች ውስጥ የንግድ ቦታ እንደሚሰጧቸው ቃል እየገቡላቸው እንደሆነ ተዘግቧል።

ከአቡነ ጳውሎስ ህልፈት በኋላ በአዲስ አበባና በአሜሪካው ሲኖዶስ መካከል ሲደረግ የነበረው እርቀ-ሰላም እንዲቋረጥ እና የቀድሞው ፓትሪያሪክ አቡነ መርቆሪዮስ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ አቋም ከነበራቸው ጳጳሳት መካከል አቡነ ሳሙኤል ግንባር ቀደሙ ናቸው።

ከዚህ በተጨማሪ አቡነ ሳሙኤል አንዳንድ የመንግስት ባለስልጣናትን እንዳግባቡና መንግሰት ፓትሪያሪክ ሆኜ እንድመረጥ ይፈልጋል የሚለው አቡነ ሳሙኤል ተናግረውታል የተባለው ወሬ በአሁኑ ሰዓት በጠቅላይ ቤተክህነት ውስጥ በሰፊው እየተነዛ እንደሚገኝ ተገልጿል።

አንዳንድ ሊቃነ ጳጳሳትንና የቤተ ክህነት አመራሮችን በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገረው ጋዜጣው አቡነ ሳሙኤል እያደረጉት ያለው ተግባር ከአንድ ኃላፊነት የሚሰማው የሀይማኖት አባት የማይጠበቅ እና ሀይማኖታችን የማይፈቅደው ተግባር ነው ብለዋል።

አቡነ ሳሙኤል ዕድሜያቸው ከ50 የማይበልጥ በመሆኑ እና በስነ ምግባራቸውም በተደጋጋሚ ከሲኖዶሱ አባላት ጋር ግጭት ሲፈጥሩ የነበሩ አባት በመሆናቸው ለቤተ ክርስትያኒቷ ትልቅ ኃላፊነት እንደማይመጥኑ አንዳንድ ምዕመናን አስተያየታቸውን ለጋዜጣው ሰጥተዋል።

የአስመራጭ ኮሚቴው ባወጣው መርሃ ግብር መሠረት በዕጩነት ከቀረቡት አምስት አባቶች መካከል የሚመረጡት 6ኛው ፓትሪያሪክ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በዓለ ሲመታቸውን ይፈፀማል።

ህወሀት መራሹ መንግስት በፖለቲካው ውስጥ የሚታየውን ዘረኝነት በቤተክርስቲያን ውስጥ አስገብቷል በሚል የሚቀርብበትን ትችት የአቡነ ሳሙኤልን ሹመት በማገድ ለማለሳለስ ይሞክር ይሆናል የሚሉ አስተያየቶች ይቀርባሉ።

በኦሮሚያ ለአባ ገዳ የተሰበሰበው ገንዘብ በባለስልጣናት ተመዘበረ



በጉጂ ኦሮሞ ባህል አንድ አባገዳ ስልጣን በተረከበ በስድስተኛው አመት ጉማታ ወይም ስጦታ ከህዝቡ ይሰበስባል።

 ስልጣኑን የሚያስረክበው በስምንተኛው አመት ሲሆን፣ ለሁለት አመታት የሚሰራበትን ገንዘብ፣ እህል ወይም የቤት እንስሳ ከህዝቡ በስጦታ መልክ ይቀበላል።

በዚህ አመት አባገዳው ጉማታውን ለመሰብሰብ ዝግጅት በሚጀምርበት ጊዜ የቦረና ዞን የመንግስት ባለስልጣናት ከአሁን በሁዋላ ጉማታው መሰብሰብ ያለበት በመንግስት ነው በሚል ምክንያት፣ የጉማታ ሰብሳቢዎች በተለያዩ አካባቢዎች ተዋቅረዋል።

የመንግስት ባለስልጣናቱም ከህብረተሰቡ እየዞሩ በአባገዳው ስም የሰበሰቡትን እጅግ በርካታ ገንዘብ ፣ ለአባገዳው ሳይሰጡ የተወሰነውን ለመንግስት የተወሰነውን ለራሳቸው በማድረጋቸው፣ የአካባቢው ህዝብ መንግስት ባህላችንን ሆን ብሎ ለማፍረስ ወሰደው እርምጃ ነው በሚል ተቃውሞን እያሰማ ነው።

አባገዳው ከተሰበሰበው ገንዘብ ውስጥ አንድ ሳንቲም ባለማግኘቱ፣ አባገዳውና የእርሱ ተወካዮች አቤት ቢሉም ሰሚ አላገኙም።

 ባለፈው እሁድ ከተወካዮች ምክር ቤት የተውጣጡ የፓርላማ አባላት ወደ አካባቢው በሄዱበት ወቅት፣ ባህላችንን ልታንቋሽሹ ሆን ብላችሁ የሰራችሁት ነው በሚል ተቃውሞ ገጥሞዓቸዋል።

የመንግስት ባለስልጣናት የሰበሰቡት ገንዘብ ትክክለኛ መጠኑ ባይታወቅም፣ የዞኑ ነዋሪዎች ከ100 ብር እስከ 15 ሺ ብር እና በርካታ የቀንድ ከብቶችን ለግሰው እንደነበር የደረሰን መረጃ ያሳያል።


 በጉዳዩ ዙሪያ አባገዳውን ለማግኘት ሙከራ ብናደርግም ስልካቸው ጥሪ አይቀበልም።

 የአካባቢው ባለስልጣናትን ለማግኘት ያደረግነው ጥረትም አልሳካም። ይሁን እንጅ ባለስልጣናቱ በዞኑ ውስጥ ለኢሳት መረጃዎችን የሚሰጡ ሰዎችን ለመያዝ በጀመሩት ጥረት አንዳንድ ተጠርጣሪ ግለሰቦችን ለመያዝ ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን በመስተዳዳሩ ውስጥ ከሚሰሩ ውስጥ አዋቂዎች ለማወቅ ተችሎአል።

የውጭ ምንዛሬ እጥረት በእህልና በእቃዎች ዋጋ ላይ ጭማሪ እያስከተለ ነው

በኢትዮጵያ የተከሰተው አሳሳቢ የውጭ ምንዛሬ እጥረት ነዳጅን ጨምሮ በተለያዩ ከውጭ ተገዝተው በሚመጡ እቃዎች እና በእህል


ዋጋ ላይ ጭማሪ እያሳየ መምጣቱ ታወቀ
ዘጋቢያችን እንደገለጠው ካለፉት 7 ወራት ጀምሮ የተከሰተው ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እጥረት፣ ከውጭ በሚገቡ በተለይም ከትራንስፖርት ጋራ ተያያዢነት ባላቸው እቃዎች ላይ ከፍተኛ ጭማሪ እያሳየ ነው።
 
የፍጆታ እቃዎች ባልሆኑት ላይ የታየው ጭማሪ በእህል ዋጋ ላይም ጭማሪ እንዲከሰት እያደረገው ነው። ባለፈው ጥቅምት ወር ወደ አንድ አሀዝ ይወርዳል ተብሎ የተገመተው የዋጋ ንረት ፣ ላለፉት ሶስት ወራት መጠነኛ መረጋጋት ያሳየ ቢሆንም ተመልሶ እየጨመረ መምጣቱን ህብረተሰቡን እያማረረ ነው።

በመላው አገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ጊዜ ቁጥር እንድ ችግር ብለው የሚወስዱት የኑሮ ውድነቱ መሆኑን መንግስት ባለፈው ሳምንትየተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች አነጋገሮ ካሰባሰበው መረጃ ለማወቅ ተችሎአል።

በመንግስት መረጃ መሰረት በእየለቱ የሚጎነውን የኑሮ ውድነት መግታት ካልተቻለ፣ ህብረተሰቡ እስከ ዛሬ የታገሰውን ያክል ላይ ላይታገስ ይችላል።

ከፍተኛ ጭማሪ እያሳየ የመጣውን የእህል ዋጋ ለማረጋጋት መንግስት ተጨማሪ ስንዴ ከውጭ ወደ አገር ውስጥ እያስገባ ነው። በቅርቡ ከገባው 500 ሺ ኩንታል ስንዴ በተጨማሪ ወደ 4 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ እህል ተገዝቷል።

ሪፖርተር ዛሬ እንደዘገበው ደግሞ መንግሥት በተከሰተው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ምክንያት እስከ ሰኔ ወር ድረስ ለኢንዱስትሪዎችና ለዘመናዊ እርሻዎች ብቻ ቅድሚያ እንዲሰጥ ወስኗል።

የንግዱ ማኅበረተሰብ በርካታ የውጭ ምንዛሪ ጥያቄዎችን ለባንኮች ሲያቀርቡ ቢሰነብቱም፣ በተፈጠረ የውጭ ምንዛሪ እጥረት ምክንያት ሊስተናገዱ አልቻለም፡፡ ጉዳዩን በሚመለከት መንግሥት የተከሰተው ሰው ሠራሽ የውጭ ምንዛሪ እጥረት ነው የሚል መግለጫ ሲሰጥ ቢቆይም፣ በተካሄዱ ተደጋጋሚ የፋይናንስ ዘርፍ ግምገማዎች መንግሥት የውጭ ምንዛሪ እጥረት መኖሩን ለማመን ተገዷል።

መንግሥት በጊዜያዊነት የውጭ ምንዛሪ ቅድሚያ ለኢንዱስትሪው ዘርፍና የዘመናዊ እርሻ አካል ለሆኑት የአበባና የአትክልት እርሻዎች ብቻ እንዲሰጥ ወስኗል፡፡


የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት በአንድ ዶላር እስከ 1.70 ብር በጉቦ መልክ መስጠት የተለመደ መሆኑን፣ ብሄራዊ ባንክም እርምጃ እንደሚወሰድ እያስጠነቀቀ መሆኑን ጋዜጣው ዘግቧል።

onsdag 20. februar 2013

በሰሜን ጎንደር የተለያዩ ፖለቲካዊና ማኀበራዊ ይዘት ያላቸው መፅሔቶችና መፅሐፎች እንዳይሸጡ ታገደ



ፍኖተ ነጻነት እንደዘገበው መጽሄቶችንና መፅሀፎችን አዙረው የሚሸጡ ወጣቶችም ከየካቲት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ የያዙዋቸው መጽሀፎችና መጽሄቶች ተወርሶባቸዋል።

በተለይ በጎንደር ከተማ ቀበሌ 11 ልዩ ስሙ አባጃሌ በሚባል አካባቢ ያሉ የደንብ አስከባሪዎች እዚህ ጎንደር ውስጥ ምንም ዓይነት ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸውን መፅሔቶች፣ ጋዜጦችና መፅሐፎች መሸጥ አትችሉም በሚል በተደጋጋሚ ጊዜ ከአዙሪዎች እየወረሱ ቅጣት እያሉ ያስከፍሏቸው እንደነበር ቢታወቅም የካቲት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ግን ሙሉ በሙሉ እንደወረሱባቸው ተዘግቧል።

የተመራጭ እጩዎች ምዝገባ በተጠናቀቀ በሳምንቱ ዛሬም ምዝገባ እየተካሄደ ነው



በመጪው ሚያዚያ ለሚካሄደው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ፣ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ባለፈው ሳምንት የእጩዎች ምዝገባ መጠናቀቁን አውጆ ነበር። ኢሳት ባለው የመረጃ መረብ ለማረጋጋጥ እንደቻለው በቦረና ዞን ቡሌ ሆራ ወረዳ የተማራጮች ስም ዝርዝር አለመተላለፉን ምርጫ ቦርድ ለኢህአዴግ ከገለጸ በሁዋላ ከክልልና ከዞን የተውጣጡ የኢህአዴግ አመራሮች ወደ ወረዳው በመሄድ አቶ ሀይሌ አየለ የተባሉትን የኦህዴድ ኢህአዴግ የፖለቲካ ጉዳይ ሀላፊ ከስልጣን ካባረሩት በሁዋላ ከትናንት ጀምሮ የተመራጮች ምዝገባ እንደአዲስ ተጀምሯል።

ምርጫ ቦርድ የመራጮች ምዝገባ መጠናቀቁ በይፋ ከተገለጠ በሁዋላም እንዲሁ ምዝገባ እንዲካሄድ መፍቀዱን የተመዘገቡ ሰዎችን በማነጋገር መዘገባችን ይታወሳል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በመጪው ምርጫ ለመሳተፍ ያልፈቀዱ 33 የፖለቲካ ድርጅቶች 28ቱ ፓርቲዎች ኢህአዴግን በጋራ ለመታገል የሚያስችልን ህብረት ለመመስረት የመግባቢያ ስምምነት ለመፈራረም ወሰነዋል፡፡ ፓርቲዎች ረጅም ጊዜ የወሰደ ምክክር ካደረጉ በኋላ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም የመግባቢያ ስምምነቱ ን ለመፈራረም መወሰናቸውን ዘጋቢያችን ገ_ልጸዋል፡፡ ፓርቲዎቹ በጋራ ለመስራት የጀመሩትን እንቅስቃሴ አጠናክረው በመቀጠል በቅርቡ ወደ ተሻለ የፓርቲ ስብስብ እንደሚያድጉ ገልጸዋል።

ጄነራል ሳሞራ የኑስ በ80 ሚሊዮን ብር ህንጻ አሰርተው እያከራዩ ነው

Samora house 1Samora house 4ኢታማጆር ሹሙ ጄኔራል ሳሞራ የኑስ በቄራ መብራት ሀይል አካባቢ በ80 ሚሊዮን ብር ዘመናዊ ህንጻ ማሰራታቸውን በፎቶ ግራፍ አስደግፈው ውስጥ አዋቂዎች ለኢሳት ላኩት መረጃ ያመለክታል።
የጄኔራል ሳሞራ ህንጻ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶችም መከራየታቸውን ለማወቅ ተችሎአል።
ጄኔራል ሳሞራ መከላከያ ሚኒስቴር በወር 10 ሺ ዶላር የሚከፍልበት በልዩ የደህንነት መሳሪያዎች በየሚጠበቅ መኖሪያ ቤት ውስጥ ይኖራሉ። አብዛኞቹ የህወሀት ጄኔራሎች በቦሌ ክፍለ ከተማ የሚያሰሩዋቸውን ህንጻዎች በፎቶግራፍ በማስደገፍ መዘገባችን ይታወሳል።
ጄኔራል ሳሞራ በፎቶ ግራፍ ከሚታየው ህንጻዎች በተጨማሪ ሌሎች ህንጻዎች እንዳሉዋቸውም ለማወቅ ተችሎአል።

ጣሊያን ኢትዮጵያውያንን በግፍ የጨፈጨፈችበት 76ኛ አመት በመላው አለም ታስቦ ዋለ



ፋሽስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በወረረች ማግስት፣ አገራቸውን ከወረራ ለመታደግ ሞገስ አስገዶምና አብረሀ ደቦጭ የተባሉ ሁለት ኢትዮጵያውያን፣ የጣሊያኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒቶ ሙስሎኒ የኢትዮጵያ ልኡክ የነበረውን ሮዶልፎ ግራዚያኒን ለመግደል ሙከራ ማድረጋቸውን ተከትሎ፣ ወራሪው ሀይል ከ30 ሺ በላይ ኢትዮጵያውያንን በአንድ ቀን በግፍ መጨፍጨፉ ይታወሳል።

ኢትዮጵያውያን በእየአመቱ የካቲት 12 የሚያከብሩት ይህ የሰማእታት ቀን በመላው አለም በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ዘንድሮም ተከብሮል።

በአዲስ አበባ ስድስት ኪሎ በሚገኘው የሰማዕታት ሐውልት የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ አርበኞች፣ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች በተገኙበት የመታሰቢያ ሥነ ሥርዓት ተካሂዷል። ሰማዕታቱን ለማሰብም በሐውልቱ ሥር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታው አስተዳደሩን በመወከል የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል። የኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ተወካይም የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል።

በአሜሪካ ሎስ አንጀለስ በቨርጂን ሜሪ ኦርቶዶክስ ካቴደራል ልዩ የጸሎት ስነስርአት ተካሂዶአል። በስነስርአቱ ላይ አባ አለቃ ማሪያም እና ቀሲስ መላኩ ባወቀ ፋሺስት ኢጣሊያ በኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመችውን ግፍ ዘርዝረው አቅርበዋል። በዚሁ እለት ከ200 በላይ የደብረ ሊባኖስ መነኮሳት መገደላቸውም ተወስቷል።

በአምስተርዳም ከተማ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እውቁ የሰብአዊ መብት ተሟጋች የሆነው አርሰቲስት ታማኝ በየነ በተገኘበት እለቱን የህሊና ጸሎት በማድረግ አስበውታል።

ፋሺስት ጣሊያን ኢትዮጵያን አንበርክካ ቅኝ ግዛቷ ለማድረግ በተደጋጋሚ ብትሞክርም፣ በኢትዮጵያውያን አስደናቂ ጀግንነት ምኞቷ ህልም ሆኖ እንደቀረ ይታወቃል።

በአፍሪካ ውስጥ በቅኝ ግዛት ውስጥ ካልተያዙ ሁለት አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንዱዋ ናት።

mandag 18. februar 2013

 
 
 
 

በዳውሮ ዞን የሚታሰሩ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል



የመረጃ ምንጮች እንደገለጡት የእና አቶ ዱባል ገበየሁን እስር ተከትሎ የዩኒቨርስቲ መምህራን እና የመንግስት ሰራተኖች እየታሰሩ ነው።

ከአርባምንጭ ዩኒቨርስቲ አቶ አባተ ኡካ፣ ከጅማ ዩኒቨርስቲ አቶ አብረሀም ሰሞኑን ተይዘው ታስረዋል።

በክልሉ የሚታየው ውጥረት መንግስትን በእጅጉ እንዳሳሰበው ለማወቅ ተችሎአል።

 የአቶ ዱባለ ገበየሁ ዘመዶችና ወዳጆችም እየተለቀሙ በመታሰር ላይ ሲሆኑ፣ ከግንቦት 7 ጋር በተያያዘ በአሸባሪነት ክስ እንደሚቀርብባቸው የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

ዳውሮ መምህር የኔሰው ገብሬ ዲሞክራሲና ፍትህ በሌለበት አገር አልኖርም በማለት ራሱን በእሳት አቃጥሎ ያገደለባት ቦታ ነው።

በአዲስ አበባ ምርጫ ከ99 በመቶ በላይ በእጩነት የተመዘገቡት ኢህአዴግ ናቸው



በተለያዩ የምርጫ ጣቢያዎች= በመዘዋወር ያጠናቀረው ዘገባ እንደሚያመለክተው በመጪው ሚያዚያ ለሚካሄደው የአዲስ አበባ የወረዳና የአካባቢ ምርጫ፣ ተወዳዳሪ ሆነው በእጩነት የቀረቡት 99 በመቶ የሚሆኑት የኢህአዴግ አባላት ናቸው።

አብዛኞቹ ተመራጮች የመንግስት ሰራተኞችና በጥቃቅንና አነስተኛ ስራ ተመድበው የሚሰሩ ናቸው። በእጩዎች ስም ዝርዝር ላይ እንደሚታየው ከ40 በመቶ በላይ ተመራጮች ከ3ኛ ክፍል እስከ 10ኛ ክፍል የሚሸፍን የትምህርት ደረጃ አላቸው።

 40 በመቶ የሚሆኑት ተወዳዳሪዎች ደግሞ ከ10ኛ ክፍል እስከ ዲፕሎማ የሚደርስ የትምህርት ደረጃ አላቸው። ከ20 በመቶ በላይ ተወዳዳሪዎች የመጀመሪያ ደግሪ እንዳላቸው ለማወቅ ተችሎአል።

ከ99 በመቶ በላይ በሆኑት ጣቢያዎች በእጩነት የቀረቡት ኢህአዴጎች ሲሆኑ፣ የተቃዋሚ አባላትን ፈልጎ ማግኘት በእጅጉ አስቸጋሪ ነው።

33 የተቃዋሚ ድርጅቶች በምርጫው ላለመወዳደር የያዙት ጠንካራ አቋም ገዢው ፓርቲ የዘንድሮውን የአካባቢና አዲስ አበባ ምርጫ ብቻውን እንዲሮጥ አስገድዶታል።

በ1997 ዓም ምርጫ ቅንጅት በአዲስ አበባ ሙሉ በሙሉ ካሸነፈ በሁዋላና ገዢው ፓርቲ ውጤቱን በጉልበት ከቀማ በሁዋላ፣ በአዲስ አበባም ሆነ በመላ አገሪቱ በቂ ፉክክር የታየበት ምርጫ አልተካሄደም።


የገዢው ፓርቲ አባላት እስካሁን ድረስ ምርጫ ካርድ ላልወሰዱት ሰዎች ካርድ እያደሉ እንደሚገኙ በተለያዩ

søndag 17. februar 2013






የካቲት 11/2005 ዓም ህወሓት 38ኛ ዓመቱን ያከብራል።አቶ ኃይለማርያምም ለስብሰባው መቀሌ መግባታቸውን የ ኢትዮጵያ ቴሌቭዥን በ ዜና እወጃው ላይ ተናግሯል።

 አቶ ገብረ መድህን አርአያ የቀድሞው የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል እና የፋይናንስ ክፍል ኃላፊ ስለ ህወሃት ይናገራሉ።

 በ 1977 ዓም በነበረው ድርቅ የ ህወሃት አመራር የ ትግራይ ህዝብ እየሞተ እያየ ዝም አለ አለም በሙሉ ለትግራይ ህዝብ የረዳውን እህል አመራሩ ሸጠው እነርሱ ግን ለ ማሌ ሊግ ምስረታ ሸብ ረብ ይባል ነበር ።

ማሌ ሊግ የተመሰረተው ለድርቅ የመጣውን እህል ተሸጦ በ ሰላሳስድስት ሚልዮን ብር ነበር።''አቶ ገብረ መድህን ከተናገሩት።

lørdag 16. februar 2013

የአማራ ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተከሰሰ


በአማራ ክልል የሚሰሩ የተለያዩ የመንግስት መስሪያቤት ሰራተኞች እና የኢህአዴግ አባላት ለኢሳት እንደገለጡት ከመሬት ሽያጭ ጋር በተያያዘ በክልሉ የሚታየው ከፍተኛ ሙስና ሊገታ ያልቻለው የክልሉ ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስናው ዋና ተዋናይ ሆኖ በመገኘቱ ነው።

ሰራተኞቹ ከወራት በፊት ከፍተኛ የዜና ሽፋን ተሰጥቶት የነበረውን የሙስና ጉዳይ በማንሳት እንደገለጡት ፣ የክልሉ ባለስልጣናት ከባለሀብቶች ጋር በመመሳጠር በባህርዳር ከተማ ከፍተኛ የሆነ የመሬት ችብቸባ እያካሄዱ ቢሆንም፣ የክልሉ የጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተወናይ በመሆኑ አደጋውን ለመከላከል አልተቻለም።

በመሬት ላይ የሚካሄደውን ዘረፋ የሚመሩት የከተማው የኢንዱስትሪ ልማትና ከተማ አገልግሎት ጽ/ቤት ሰራተኞች የሆኑት አቶ ገብሩ ጸሀይነህ፣ አበ ሰማ፣ አየነው አለሙና በጊዜው ጸሀየ መሆናቸውን ሰራተኞች ይገልጣሉ።

የክልሉ የጸረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ የሆኑት መቶ አለቃ እንዳለው አራቱ ግለሰቦች የከተማውን መሬት በድርድር በመሸጥ የሚጠረጠሩ መሆናቸውን በመግለጽ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ካስደረጉ በሁዋላ፣ አርብ ጥቅምት 30/2005 ዓም ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ተደርጓል።

አራቱ ተከሳሾች ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በከተማዋ የሚገኙ ባለሀብቶች ፍርድ ቤቱን ያጨናነቁ ሲሆን፣ ዳኛውም የተከሳሾችን ፋይል አይተው ዋስትና ያሰጣል አያሰጥም በማለት ለመወሰን የጊዜ ቀጠሮ ሰጥተው ፋይሉን ወደ መዝገብ ቤት ከመሩት በሁዋላ፣ የጸረ ሙስና ኮሚሽነሩ ተከሳሾች የዋስትና መብት ይፈቀድላቸው የሚል ደብዳቤ ዳኞች እንደገና ችሎት እንዲሰየሙ ተደርጎ እያንዳንዳቸው በ5 ሺ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ተደርጓል።

በስፍራው የነበሩ አንድ ባለሀብት ለሁሉም ተከሳሾች የዋስትና ገንዘብ በማስያዝ እንዲለቀቁ አድርገዋል።

ሰራተኞቹ እንደገለጡት የጸረ ሙስና ኮሚሽን ባለስልጣናት እስረኞችን በዋስ ለማስለቀቅ 30 ሺ ብር፣ ክሱን ለመሰረዝ ደግሞ 150 ሺ ብር ለመቀበል ከባለሀብቶች ጋር ተደራድረዋል።

 በከፍተኛ ሙስና የተከሰሱት ሰራተኞች ላለፉት ሶስት ወራት አንድም ቀን ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀድሞ በነበራቸው የሀላፊነት ቦታዎች ላይ እየሰሩ እንደሚገኙ ታውቋል።

 አብዛኛውን ውሎውን በመስሪያ ቤቱ አድርጎ የነበረው የኮሚሽኑ ባለስልጣንም ምርመራውን ማቋረጡ ታውቋል።

ተጠርጣሪ ግለሰቦቹ ቀደም ሲል ኢሳት ይፋ ያወጣው የሙስና ወንጀል መሪ ተወናይ ከሆኑት ከባህርዳር ከተማ አቶ ስማቸው ወንድማገኝ ጋር ጥብቅ የጥቅም ቁርኝት እንዳላቸው ታውቋል።

የባህርዳር ጸረሙስና ኮሚሽን መስሪያቤትን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።

የእነ አቶ አንዱአለም አራጌ ይግባኝ ተራዘመ


በፌደራሉ አቃቤ ህግ በሸባሪነት ክስ ተመስርቶባቸው በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ የተላለፈባቸው የአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን፣ አቶ አንዱዓለም አያሌው ፣ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ የስር ፍርድ ቤቱን ውሳኔ በመቃወም 6 ኪሎ ለሚገኘው የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኛ በጠየቁት መሰረት ለየካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም. ለውሳኔ ተቀጥሮ እንደነበር ይታወቃል።

ነገር ግን በዕለቱ የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የመሐል ዳኛው ሳይገኙ ከመቅረታቸውም በላይ ጠቅላይ ፍርድ ቤትም ውሳኔውን ለመስጠት ጉዳዩ ሰፋ ያለ ጊዜ ስለሚፈልግ አይተን አልጨረስንም የሚል መልስ ሰጥቷል፡፡

 በዚህም ምክንያት የይግባኙን የመጨረሻ ፍርድ ውሳኔ ለመስጠት ለ3ኛ ጊዜ ለመጋቢት 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ከፍተኛ ስጋት ላይ የወደቀው መንግስት ሞባይል ኔትወርክ አቋርጦ እንደነበር ታወቀ



በዛሬው ዕለት ከተካሄደው ጁምአ ጸሎት ስርዓት ጋር ረብሻና ከፍተኛ ተቃውሞ ሊነሳ ይችላል በሚል ስጋት በተያያዘ በአዲስአበባ ዛሬ ማለዳ ላይ የሞይባል አገልግሎት ከአምስት ሰዓታት በላይ ተቋርጦ እንደነበር ተሰማ፡፡

በዛሬው ዕለት ሙስሊሙ ህብረተሰብ በመደበኛ የጁምአ ፕሮግራሙ እርስ በእርስ በመጠራራት እና አጫጭር የስልክ መልዕክቶችን በመለዋወጥ ከፍተኛ ተቃውሞ ሊያደርግ ይችላል በሚል ግምት ሐሙስ ለዓርብ አጥቢያ በግምት ከለሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ እስከ ንጋቱ 4፡00 ሰዓት ድረስ የተወሰኑ የሞባይል ሰልክ ቁጥሮችን ከግንኙነት ውጪ በማድረግ ወይ
ኔትወርክ በማቋረጥ እርምጃ ተወስዷል፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞም የስልክ አገልግሎት በመቋረጡ የአጭር መልዕክት ልውውጥ
እንዲሁም የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲቋረጥ ግድ ሆኗል፡፡ በዚህ ምክንያት በርካታ ግለሰቦችና የቢዝነስ ተቋማት የእርስ በርስ ግንኙነት ማድረግ ሳይችሉ ለማርፈድ ተገደዋል፡፡

ሁሉም የሞይባል አገልግሎት ያልተቋረጠበት ዋንኛ ምክንያት ምን እንደሆነ የተጠየቁት ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጭ የተወሰኑ የደንበኛ ጭነት ያለባቸውን መስመሮች ግንኙነት ከተቋረጠ ያልተቋረጠባቸው ስልኮች ከእነዚህ ጋር ግንኙነት ማድረግ አይችሉም ብለዋል፡፡

በተጨማሪም ሁሉም ቁጥሮች አለመቋረጣቸው ቴሌ ለሚነሳበት ቅሬታ የኔትወርክ መጨናነቅ
ነው በሚል ጉዳዩን ለማስተባበል ስለሚረዳው ሆን ተብሎ የተደረገ መሆኑን ጠቅሰው የዚህ ዓይነቱ አሰራር ሲፈጸም የመጀመሪያው አለመሆኑን አመልክተዋል፡፡

እንደምንጫችን ገለጻ ከዚህ በፊት ጠ/ሚኒስትሩ እና ሌሎች የአገር መሪዎች
በከተማ ውስጥ ሲዘዋወሩ፣ሲገቡና ሲወጡ መንገዶችን ከመዝጋት ባሻገር ሸብርተኝነትን አስቀድሞ ለመከላከል በሚል የተወሰኑ የሞይባል ግንኙነቶች ለተወሰኑ ደቂቃዎች ሲቋረጡ መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡

በመንግስት ሞኖፖል የተያዘው የቴሌኮም ዘርፍ ለግሉ ዘርፍ ክፍት እንዲሆን ከማይፈለግባቸው ምክንያቶች አንዱ መንግስት ባሻው ጊዜ ስልኮችን የማቋረጥ፣የመጥለፍና የመሳሰሉ ኢ-ሕገመንግስታዊና ኢ-ሰብዓዊ ድርጊቶችን ለመፈጸም እንዲረዳው በማሰብ መሆኑን ጠቅሶ ዘርፉ በግል ተይዞ ቢሆን ኖሮ መንግስት የዚህ ዓይነቱ ዕድል የማይኖረው
ከመሆኑም በላይ ከጸጥታ ጉዳይ ጋር ተያይዞ እንኳን አገልግሎት ማቋረጥ ቢከሰት ኪሳራ የመክፈል ግዴታ ስለሚኖርበት የዜጎችም መብት ለማስከር ይረዳ እንደነበር ምንጫችን አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

የኢትዮጵያ ደህንነት መ/ቤት “ጀሃዳዊ ሃራካት” በሚል ርዕስ በሕግ ጥላ ስር የሚገኙ ሙስሊም እስረኛችን በማስገደድ የተጠናቀረ ፊልም ጥር 28 ቀን ምሽት በኢቴቪ ካሰራጨ በኋላ እንደገና ከዳር እስከዳር የተቀጣጠለውን የሙስሊሞች ተቃውሞ ለማዳፈን ዜጎች በነፍስ ወከፍ ኮንትራት ገብተው እያገኙ ያሉትን የሰልክ አገልግሎት ከፈቃዳቸው ውጪ በማቋረጥና በማስተጓጎል ሥራ ውስጥ መጠመዱ የገባበት ገደብየለሽነት ፍርሃት የሚያሳይ ነው፡፡

ኢህአዴግ የቴሌኮሚኪሽን መስሪያ ቤት ማኔጅመንት እጅግ ታማኝ በሆኑ የህወሀት አባላት እንዲያዝ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል።

  ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን በብዛት መልእክቶችን የሚለዋወጡት በሞባይል ስልኮች በመሆኑ መንግስት ምናልባትም ዘወትር አርብ ኔትወርክ በማጥፋት ስራው ሊቀጥል ይችላል የሚል ግምት መኖሩን ዘጋቢያችን ገልጿል።

fredag 15. februar 2013

የኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ለሁለት ሊከፈል ነው



የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽንን ሁለት ቦታ ለመክፈል እየተደረገ ያለው እንቅስቃሴ በቂ ጥናት ያልተደረገበትና ዓለም አቀፍ ሁኔታዎችን ያገናዘበ ባለመሆኑ መንግሥት ዕርምጃውን እንዲገታ እና ዳግም እንዲያጤን በዓለማቀፍ አበዳሪዎች መጠየቁን ሪፖርተር ዘገባ።

እንደ ጋዜጣው ዘገባ የዓለም ባንክ፣ የአፍሪካ ልማት ባንክና ሌሎች ዓለም አቀፍ አበዳሪዎችም ኮርፖሬሽኑ የመዋቅር ለውጥ የሚደረግበት ከሆነ ብድር ላለመስጠት እያንገራገሩ ናቸው፡፡

መንግስት በአሁኑ ጊዜ ኮርፖሬሽኑን ለሁለት በመክፈል፦” የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮንስትራክሽን ኮርፖሬሽን “ እና “ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስተላላፊ ኮርፖሬሽን” የሚባሉ ሁለት ራሳቸውን የቻሉ ኩባንያዎች በመመሥረት ሒደት ላይ ነው፡፡

ዋናውን ኮርፖሬሽን ሁለት ቦታ ከመክፈል ይልቅ ውስጣዊ መዋቅሩን በማሻሻል፣ በማጠናከርና የባለሙያዎችን አቅም በመገንባት ራሱን አስችሎ የተጀመሩ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ማስቀጠል የተሻለ እንደሆነ የዘርፉ ሙያተኞችና ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች ቢመክሩም፤መንግስት ግን ከጀመረው የመክፈል እንቅስቃሴ ሊገታ አልቻለም።

ዓለም አቀፍ አበዳሪ ተቋማቱ ደግሞ ኮርፖሬሽኑን ለሁለት ለመክፈል የሚደረገውን እንቅስቃሴ በጥርጣሬ ከማየት ባሻገር የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ኃላፊዎችን ማብራሪያ እየጠየቁ ሲሆን፤ እንደ ዓለም ባንክ የመሳሰሉ አበዳሪዎች ደግሞ የተሰጣቸው ማብራሪያ ያላረካቸው በመሆኑ፣ ለኮርፖሬሸኑ እየተደረገ ያለው የመዋቅር ለውጥ እንዲቋረጥ እያሳሰቡ ናቸው፡፡

ጋዜጣው እንዳለው ፤የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ሁለት ቦታ እንዲከፈል ሐሳቡ የመጣውና ጥናቱ ተግባራዊ የተደረገው በውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አማካይነት መሆኑን ባለሙያዎቹ ገልጸው፣ በሚኒስቴሩ የተሠራው ጥናት የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችን ያላገናዘበ ነው ይላሉ፡፡

የዘርፉ ሙያተኞች ኮርፖሬሽኑ ሁለት ቦታ በሚከፈልበት ጊዜ የኃይል ማስተላለፍ ሥራ የሚያከናውነው ተቋም ማኔጅመንት ለውጭ ኩባንያ እንዲሰጥ እንደሚደረግ የተገለፀ ቢሆንም፤ ዓለም አቀፍ አበዳሪዎች በራሳቸው ፖሊሲ መሠረት ይህንን ዓይነቱን አካሄድ አይቀበሉም ይላሉ፡፡

ኮርፖሬሽኑ እንደበፊቱ አንድ ሆኖ መዋቅሩን እያጠናከረ ልክ ኢትዮ ቴሌኮም እንዳደረገው ለተወሰነ ጊዜ የኃይል ማስተላለፍ ተቋሙ ማኔጅመንት ለውጭ ኩባንያ በኮንትራት ቢሰጥ ትክክል ይሆናል የሚሉት ባለሙያዎቹ፣ ኮርፖሬሽኑ ሁለት ቦታ ከተሰነጠቀ በኋላ የሚሰጥ ከሆነ ግን የአበዳሪዎችን አመኔታ ያጣል ይላሉ፡፡

በተለይ ዓለም ባንክና የአፍሪካ ልማት ባንክ ኮርፖሬሽኑን ሁለት ቦታ ለመክፈል የተደረገው ጥናት በጥድፊያና በግብታዊነት የተወሰነ በመሆኑ ጥያቄ ማንሳታቸው ትክክል ነው የሚሉት ባለሙያዎቹ፣ ኮርፖሬሽኑ ለወሰዳቸው ብድሮች ዋስትና ስለማይኖርና የሕግ ክፍተት ስለሚፈጥር ገንዘባቸው አደጋ ውስጥ የሚወድቅ ይመስላቸዋል በማለት የሥጋቱን መጠን ይገልጻሉ፡፡


ኮርፖሬሽኑን ሁለት ቦታ የመክፈል ሐሳብ መጥቶ ወደ ተግባር የተገባው በባለሙያዎች በሚገባ ተጠንቶበት ሳይሆን በይድረስ ይድረስ በቀረበ ጥናት ላይ የፖለቲካ ውሳኔ ስለተሰጠበት ነው ሲሉም ይተቻሉ፡፡


የዓለም ባንክም ሆነ የአፍሪካ ልማት ባንክ ከበርካታ አበዳሪ ተቋማት አምጥተው የሚሰጡትን ብድር ሁለት ቦታ ለሚከፈል ድርጅት ለመስጠት እንደሚቸገሩ ገልጸው፣ አገሪቱ ከምታገኛቸው የውጭ ብድሮች ከ30 እስከ 40 በመቶ የሚሆነው ብድር ለኢነርጂ ሴክተር በመሆኑ መንግሥት ውሳኔውን ሊያጤነው ይገባል ሲሉ ባለሙያዎቹ ይመክራሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሐምሌ 2002 ዓ.ም. ኮርፖሬሽኑ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች የደረሱበት ደረጃ ለማድረስ ጥናት እንዲደረግ ትዕዛዝ መስጠታቸውን የሚያስታውሱ አንድ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ባለሙያ፣ ሐሳቡ ፈሩን ስቶ ሄዶ ወደ አላስፈላጊ ውሳኔ እንደተደረሰ ያስረዳሉ፡፡

የሌሎች አገሮች ልምድ እንደሚያስረዳው እስከ 50 ሺሕ ሜጋ ዋት የሚያመነጩ ኩባንያዎች እንኳን ይህንን ዓይነቱን ዕርምጃ አያስቡትም አያስቡትም ያሉት ባለሙያው፤ የተለያዩ የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ለመገንባት ከውጭ ከፍተኛ ብድር እያስፈለገ ባለበት ወቅት ኮርፖሬሽኑን ሁለት ቦታ ሰንጥቆ የአበዳሪዎችን አመኔታ ማጣት ከባድ ነው ሲሉም ያስጠነቅቃሉ፡፡

አበዳሪዎች ከፍተኛ ገንዘብ ያበደሩ እንደመሆናቸው መጠን ኮርፖሬሽኑ ለሁለት ሲከፈል የወደፊቱን የመክፈል አቅምና ያበደሩትም ሆነ ለማበደር እየተዘጋጁ ያሉትን ገንዘብ የትኛው መዋቅር እንደሚከፍላቸው ጥያቄ ከማንሳታቸውም በላይ ባለፉት ሳምንታት ተቋማቱ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴርን ማብራርያ ሲጠይቁ ሰንብተዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ እንዳለ የኃይል ሥርጭት ተቋም ማኔጅመንት የእስራኤል ኩባንያ እንደሚረከብ ቀደም ሲል ቢገለጽም፣ አሁን በተገኘው መረጃ “ኢንዲያን ፓወር ግሪድ ኮርፖሬሽን” የተባለ የህንድ ኩባንያ ጨረታውን ሊያሸንፍ እንደሚችል እየተነገረ መሆኑን ነው ጋዜጣው ጨምሮ የዘገበው።

በመሆኑም በቅርቡም ከህንዱ ኩባንያ ጋር የማኔጅመንት ኮንትራት ስምምነት እንደሚፈረም ምንጮች ገልጸዋል፡፡


በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የኢኮኖሚና የፋይናንስ ዘርፍ ክላስተር ኃላፊና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር ደብረ ፅዮን ገብረ ሚካኤል የሚመሩት የኮርፖሬሽኑ ቦርድ፣ ጨረታው በሚገባ ተካሂዶ ተወዳዳሪዎቹ በሚገባ ከተመረመሩ በኋላ የህንዱ ኩባንያ ተሽሎ እንደተገኘ መናገራቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል፡፡


የፓወር ግሪድ ኮርፖሬሽን ሊቀመንበር ህንዳዊው አር.ኬ. ናያክ በበኩላቸው ትናንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ኩባንያቸው ለሁለት ዓመታት የሚቆይ የ16 ሚሊዮን ዶላር የማኔጅመንት ኮንትራት ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ጋር እንደሚፈራረም አስታውቀዋል፡፡

የፕሬስ ነጻነት አስከፊ ከሆነባቸው 10 አገራት ኢትዮጵያ አንዷ ናት ተባለች



ሲፒጄ የፕሬስ ነጻነት አደጋ ውስጥ የወደቀባቸው 10 የአለም አገራት በማለት በግንባር ቀደምነት ያስቀመጣቸው አገሮች ብራዚል፣ ኢኳዶር፣ ኢትዮጵያ፣ ኢራን፣ ፓኪስታን፣ ራሺያ፣ ሶማሊያ ፣ ሶሪያ፣ ቱርክ እና ቬትናም ናቸው።'


ኢትዮጵያ የጸረ ሽብር ህግ በማውጣት ጋዜጠኞች በእስር ቤት እንዲማቅቁ ማድረጓን በዚህ ድርጊቷም ከኤርትራ በመቀጠል የሁለተኛነት ስፍራ መያዙዋ ተጠቅሷል።'


አምና 4 ጋዜጠኞች ፣ ከ2007 ጀምሮ ደግሞ በድምሩ 49 ጋዜጠኞች አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን፣ ከአለም አገራት ጋር ሲተያይ አገሪቱ በሶስተኛ ደረጃ እንድትታይ ማድረጉን ጠቅሰዋል።


በአገር ውስጥ የሚገኙ ጋዜጠኞች የሀይለማርያም ደሳለኝ መንግስት በፕሬስ ላይ የሚታየውን አፈና ይለውጠዋል ብለው እንደማያስቡ ሲፒጄ ገልጿል።

33ት የፖለቲካ ፓርቲዎች ጂሀዳዊ ሀረካትን ተብሎ በኢቲቪ የቀረበውን ፊልም አወገዙ



በመጪው የአዲስ አበባ እና የአካባቢ ምርጫ ላለመሳተፍ የወሰኑ 33ቱ የፖለቲካ ድርጅቶች ” መንግስት ጅሀዳዊ ሃረካት በሚል ርእስ በኢቲቪ ያስተላለፈው ፊልም ዋና አላማ የህዝብን የዘመናት አብሮነት በመሸርሸርና የመብት ጥያቄ የሚያነሳን ከሽብረተኝነትና ጦርነት ጋር በማያያዝ ህዝብን ለማሸማቀቅ ሆኖ በውጤቱም ህዝብ በአገሩ ላይ ያለውን የባለቤትነትና ሃላፊነት ስሜት በመናድ አንገት ማስደፋትና መብት ጠያቂዎችን በመነጣጠልና መከፋፈል ጥያቄዎችን ማደፈንና ማፈን ነው” ብለዋል።

ኢህአዴግ በለመደው መንገድ ፊልሙን ሲያዘጋጅ በኪሚቴአባላት ላይ ለከፈተው የፈጠራ ክስ በፍትህ አደባባይ ሊያቀርብ ያልቻለውን መረጃና ማስረጃ በህገወጥ መንገድ ታሳሪዎችን በማሰቃየት ” ከተናገሩት”ና ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ጉዞው ከተለያዩ ከጉዳዩ ጋር ተዛማጅ ካልሆኑ የሌላ አገር ፊልሞችን ጨምሮ በተቀናበረ የፕሮፓጋንዳ ድርሰት ለማስደግፍ ቢሆንም የተፈለገውን ውጤት አላስገኘለትም ብሎአል።

ፓርቲዎቹ ” የስርአቱ ህልውና በሰለጠነ መንገድ ከመወያየት ይልቅ በማጭበርበር፣ ህዝብ ከህዝብ በማጋጨትና በመነጣጠል፣ በማሸበርና በሀሰት ላይ የተንጠለጠለ በመሆኑ በአደባባይ ለመከራከርና መፍትሄ ለመሻት ተፈጥሮውና ባህሪው አይፈቅድለትም” ብሎአል።

ፓርቲዎ፤የፊልሙ ግብ መንግስት ላለፉት 21 አመታት ህዝብን በጎሳ፣ በብሄር፣ በክልል እና በሀይማኖት ለመከፋፈል፣ ለመነጣጠል፣ ለማጋጨት ሲያደርግ የነበረውን ሙከራ መድገም ቢሆንም አለመሳካቱን፣ የኮሚቴ አባላቱን ከሙስሊሙ ማህበረሰቡ ያለመነጠሉን፣ በህዝበ ሙስሊሙና ክርስቲያኑ መካከል የመከፋፈልና የጥርጣሬ ስሜት ለመፍጠር የተደረገው ጥረት በተቃራኒው ህብረተሰቡ እንዲተባበርና በጋራ እንዲቆም ትምህርት መስጠቱን አመልክተዋል።

ፓርቲዎቹ በማያያዝም ” ገዢው ፓርቲ ህገመንግስቱን የማያከብርና ከህግ በላይ መሆኑን፣ የሙስሊሙን ሰላማዊ ተቃውሞ ሊቀለብሰው አለመቻሉን፣ ህዝቡ በኮሚቴ አባላት ላይ ያለው እምነት መጠናከሩን፣ በሙስሊሙና ክርስቲያኑ ህዝብ መካከል ባለው የዘመናት መከባበርና አብሮነት ቀጣይነት ላይ ችግር አለመፍጠሩን፣ የፍርድቤቶች ህገመንግስታዊ ስልጣንና ሃለፊነት በአስፈጻሚው አካል መነጠቁን፣ ህዝቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ በመንግስት ላይ ያለው እምነት መሟጠጡን፣ የለውጥ ፍለጎቱ እንዲጨምርና ለመብቱ በጋራ እንዲነሳ ያደረገው መሆኑን” ጠቅሰዋል።

በመጨረሻም የፊልሙ አዘጋጆች፣ ኢቲቪ እንዲሁም የስራ አስፈጻሚዎች በህግ እንዲጠየቁ፣ የሙስሊም መሪዎች እንዲፈቱ፣ ጥያቄያቸው መልስ እንዲያገኝ እና ህዝቡ ለሰላማዊ ትግል በህብረትና ቆራጥነት በጋራ እንዲቆም ” ፓርቲዎቹ ጠይቀዋል።

በጎንደር መድሀኒዓለም ቤ/ክ የተጠለሉ 48 ባህታዊያንን ወደ መጡበት ዋልድባ መወሰዳቸው ታወቀ

ባህታዊያኑ ከጥር 2 ቀን 2005 ዓም ጀምሮ በጎንደር ከተማ በሚገኝ መድሀኒአለም ቤ/ክርስቲያን ውስጥ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገላቸው ተጠልለው ቆይተዋል።
ትናንት ባህታዊያኑ ከቀኑ ስምንት ሰአት ላይ በአውቶቡስ ተጭነው ወደ አልታወቀ ስፍራ መወሰዳቸውን የዘገብን ሲሆን፣ ወኪላችን ሂደቱን ተከታትሎ እንደዘገበው ባህታዊያኑ የተወሰዱት ፣ ከተለያዩ የአማራ ክልል የተውጣጡ የሀይማኖት አባቶች ችግሩን


በሽምግልና እንፈታዋለን የሚል ሀሳብ ካቀረቡ በሁዋላ ነው።

ባህታዊያኑ በአውቶቡስ ሲጫኑ የተመለከተ አንድ የጎንደር ነዋሪ ፣ እንደገለጠው ባህታዊያኑ ከህዝቡ እንዳይቀላቀሉ ሌት ተቀን ሲጠበቁ ሰንብተዋል (10፡42-11፡45 )
31ባህታዊያን ጥር 15 ቀን 2005 ዓም ለሰሜን ጎንደር ዞን መስተዳድር እና ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን በጻፉት አቤቱታ፣ ደረሰብን ያሉዋቸውን በርካታ በደሎች ዘርዝረው አቅርበዋል።

በደብዳቤው ፣ የጸለምት ወረዳ አስተዳደርን የተቆጣጠሩ ግለሰቦች ለዘመናት አንድነቱ ተከብሮና የዘር መድልዖ ሳይደረግበት ማንኛውም መናኝ በሀይማኖታዊ ምክንያቶች ብቻ ተመርምሮ ይኖርበት በነበረው ቦታ ግልጽ በሆነ መልኩ የትግራይ ክልል ተወላጅ ካልሆናችሁ በዚህ ገዳም መኖር አትችሉም በማለት ማህበረ-መነኮሳቱን መከፋፈላቸውን እንዲሁም የአካካቢውን የሚሊሺያ ሀይል በመጠቀም የመብት ጥሰት መፈጸማቸው ፣ ተመልክቷል።

ከተጠቀሱት የመብት ጥሰቶች መካከል የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ሲሳይ መረሳ ማህበረ-መነኮሳቱን በዘር በመከፋፈልና የራሳቸውን የፖሊስ ታጣቂና ሚልሻ በመጠቀም እያሰሩ በተደጋጋሚ ማስደብደባቸው ተጠቅሷል።

ጥር 2 ቀን 2005 ዓም አባ ወ/ገብርኤል ገ/ስላሴ እና አባ ገ/ህይወት ተ/ማርያም የተባሉ መናንያን ከከዳሙ ተወስደው ሽፍታ መነኩሴዎች ተብለው ለ4 ቀናት መታሳራቸውን፣ የወረዳው አስተዳዳሪውም ” እናንተ ተመልሳችሁ ወደ ገዳሙ መግባት አትችሉም፣ የወጡትም አይመለሱም፣ በገዳሙ የቀሩትንም እየመነጠርን እናወጣቸዋለን፣ እንገባለን ካላችሁ ገዳያችሁን ሳታውቁ ትገደላላችሁ መባላቸውም ተመልክቷል።

” ከገዳሙ ለመውጣትም ሆነ ወደ ገዳሙ ለመግባት በምንቀሳቀስበት ጊዜም የትግራይ ክልል ነዋሪ መሆናችሁን የሚያሳይ የቀበሌ መታወቂያ ካላመጣችሁ እያሉ ያስገድዱናል የሚሉት ባህታዊያኑ ፣ የገዳሙን አስተዳደር ከወረዳ አስተዳደር የተላኩ ሚሊሺያዎችን ይዘው መምህር፣ እቃቤትና ሌሎች ሰራተኞችን በአዲስ አዋቅረዋል” ብለዋል።

የ31 መነኮሳትን ስም እና ፊርማ የያዘው ደብዳቤ በተለያዩ ቀናት የተፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በዝርዝር ከመያዙም በላይ፣ ፖለቲካን ተገን ያደረገው ዘረኛ አስተሳሰብ በገዳሙ የመቀጠል መብታቸውንና የማህበረ መነኮሳቱን ህልውና አደጋ ላይ መጣሉን አመልክቷል።

መነኮሳቱ ያቀረቡትን አቤቱታ በተመለከተ የጸለምት ወረዳ ባለስልጣናትን ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።

fredag 8. februar 2013

ግንቦት 7 ጅሐዳዊ ሐረካት ተብሎ የተዘጋጀውን ፊልም አወገዘ



ግንቦት ሰባት የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ለኢሳት በላከው መግለጫ ጅሃዳዊሐረካት የተባለው ድራማ ሁለቱን ትልልቅና ጥንታዊ የኢትዮጵያ ሐይማኖቶች ለማጣላት ሆን ተብሎ የተሰራ ነው ብሎአል።

ኢትዮጵያ እስልምናንም ሆነ ክርስትናን በቅድምያ ከተቀበሉ አገሮች አንዷ መሆኗ ብቻ ሳይሆን ክርስትናና እስልምና ከአንድ ሺ አመታት በላይ በሠላም ተከባብረዉ ጎን ለጎን የኖሩባት ብቸኛ አገር መሆኑዋን የገለጠው ግንባሩ፣ የአገር አንድነትና የህዝብ ሠላም እረፍት የሚነሳዉ አገዛዙ ግን ይህንን ዘመናት ያስቆጠረ ታሪክ ለመለወጥና የህዝብን በሠላም አብሮ መኖር ለማደፍረስ ቆርጦ የተነሳ ይመስላል ብሎአል።

የኢትዮጵያ ህዝብ አኬልደማን አይቶ ትግሉን አጠናክሮ እንደቀጠለ የገለጠው ግንቦት7፣ ጅሃዳዊ ሐረካትን አይቶ የጀመረዉን ትግል ከፍጻሜዉ ለማድረስ በተጠንቀቅ እንዲቆም ጥሪ አድርጓል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በእስር ላይ የሚገኙ የድምጻችን ይሰማ ኮሚቴ አባላት ሰብሳቢ የሆኑት ኡስታዝ አቡበክር ለፍርድ ቤት እንደተናገሩት ማእከላዊ እስር ቤት ላይ በነበሩበት ጊዜ የተፈጸመባቸውን ግፍ ዘርዝረው አቅርበዋል። በእስረኞች ላይ የደረሰው በደል አልበቃ ብሎ የሀሰት ምስክሮች ቀርበው እንዲመሰክሩ መደረጉን፣ በመቀጠልም ኢቲቪ በአደባባይ ፍርድ ቤቱ ወንጀለኛ ሳይላቸው፣ ወንጀለኛ አድርጎ እንዳቀረባቸው ለፍርድቤቱ ገልጸዋል።

 ውሳኔው በኢቲቪ አስቀድሞ የተሰጠ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ከዚህ በሁዋላ መሰየሙ ትርጉም እንደሌለው ሰብሳቢው ተናግረዋል። ዳኞቹ ፊልሙ እንዳይተላለፍ የሰጡት ትእዛዝ በምን ሁኔታ ሳይተገበር እንደቀረ ለእስረኞች ገልጸዋል፣ ይሁን እንጅ ፊልሙ በፍርድ ቤቱ ሂደት ላይ የሚያመጣው ተጽእኖ እንደሌለም ገልጸውላቸዋል።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ባለሙያ፣ ” ኢቲቪ ያስተላለፈው ፊልም  አንድ ሰው ከፍርድ ውሳኔ በፊት ነፃ ተብሎ የመገመት መብቱን ማሳጣት ብቻ ሳይሆን፤ በችሎቱ ላይ የተቀመጡት ዳኞች የይስሙላ መሆናቸውን ለማሳየት እና እስረኞቹ የሚያደርጉትን ክርክር ዋጋ ለማሳጣት” ነው ብለዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን በነገው እለት ከፍተኛ ተቃውሞ እንደሚያሰሙ ከተላለፈው መርሀ ግብር ለመረዳት ተችሎአል።

የምርጫ ምዝገባ መጠናቀቁ በይፋ ከተገለጠ በሁዋላ ምዝገባው ዛሬም ቀጥሎአል


የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ባለፈው ሳምንት የምርጫ ምዝገባው 100 በመቶ የተሳካ በመሆኑ ምርጫውን ከሁለት ቀናት የበለጠ እንደማያርዝም ገልጾ ነበር።

 ኢሳት ለምርጫው ተገዶም ቢሆን የተመዘገበው ህዝብ ከ30 በመቶ እንደማይበልጥ የምርጫ ቦርድ የውስጥ ምንጮችን በመግልጽ ዘግቧል።

ከፍተኛ የኢህአዴግ ካድሬዎች ለወረዳ አመራሮች ቀይ መብራት በርቶባችሁዋል በማለት ማስፈራራታቸውን ተከትሎ ፣ አመራሩ ወደ ህዝቡ በመውረድ በእየቤቱ ሲያስገድዱ ቆይተዋል።

 ባለፈው ሳምንት ለኢህአዴግ የወረዳ አመራሮች በተላለፈው መመሪያ ደግሞ ለስራ ጉዳይ ወደ ቀበሌዎች የሚሄዱ ነዋሪዎች የምርጫ ካርድ መውሰዳቸውን የቀበሌ ሹሞች እንዲያጠሩ መመሪያ ተላልፎላቸዋል።

ኢሳት የምርጫው ምዝገባ ከተጠናቀቀ ከሳምንት በሁዋላ ፣ ዛሬ ጥር 30፣ 2005 ዓም በደቡብ ክልል የወረዳ አመራሮች እየዞሩ የምርጫ ካርድ ሲያድሉ ውለዋል። ነዋሪዎች እንደሚሉት ዛሬ የተካሄደው ምዝገባ የንግድ ድርጅቶችን ማእከል ያደረገ ነው።

የጅማ ዩኒቨርስቲ ሙስሊም ተማሪዎች ተቃውሞአቸውን ገለጹ


ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ ተማሪዎች ለኢሳት እንደገለጡት ቁጥራቸው ከ500 የማያንስ ሙስሊም የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች በስታደየም አካባቢ በመሰባሰብ     ጥያቄያቸው መልስ እንዲያገኝ ጠይቀዋል።

  በደህንነት ሀይሎች ታፍነው የተወሰዱት ተማሪዎች ያሉበትን ሁኔታ ዩኒቨርስቲው  እንዲያሳውቃቸው ተማሪዎች ጥያቄ አቅርበዋል። የዩኒቨርስቲው ባለስልጣናት ዲኑ ለስብሰባ ከአካባቢው በመራቃቸው መልስ ሊሰጡዋቸው እንደማይችሉ ለተማሪዎች ቢነግሩም፣ ተማሪዎቹ ግን በተቃውሞአቸው ገፍተውበታል።

ይህን ዜና እስካጠናከርንበት በኢትዮጵያ ሰአት አቆጣጠር እስከ ምሽቱ 12 ሰአት ድረስ ተማሪዎች አልተበተኑም።

 የግቢው ፖሊሶች ዙሪያቸውን ከበው መታየታቸውን ተማሪዎች ገልጸዋል። የፌደራል ፖሊስ አባላት በአካባቢው ባይታዩም፣ በማንኛውም ሰአት ይደርሳሉ ብለው እንደሚገምቱ ተማሪዎች ተናግረዋል።

ባለፈው ወር ክርስቲያን ተማሪዎች ያነሱትን ተቃውሞ ተከትሎ 3 ተማሪዎች መባረራቸውንና 20 ተማሪዎች ደግሞ ከባድ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሎአል።

ሁለት የጎንደር ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ታፍነው መወሰዳቸውን ተከትሎ የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች ተቃውሞ አድርገው እንደነበር ይታወሳል።

torsdag 7. februar 2013

ኢቲቪ በኦርቶዶክስ የሃይማኖት አባቶች ላይ እንደ ሙስሊሙ ተመሳሳይ ፊልም ለማሰራጨት ዝግጅት ማጠናቀቁን ታወቀ



 በእስር ላይ የሚገኙ የኢትዮጵያ ሙስሊም የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትንበተመለከተ በዛሬው እለት ዶክመንተሪ ፊልም ለማሰራጨት ያስተዋወቀውየኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ የሃይማኖት አባቶች ላይ ተመሳሳይፊልም ለማሰራጨት ዝግጅት ማጠናቀቁን ውስጥ አዋቂ ምንጮችን የጠቀሱዘገባዎች አመልክተዋል፤ቤተ ክህነት ለፊልሙ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጏ የተገለፀሲሆን ፤የሃይማኖት አባቶችም በሂደቱ ተዋናይ መሆናቸው ተመልክቶአል።

ሐራ ተዋህዶ የተባለው የኦርቶዶክሳዊያን ድህረ ገፅ እንደዘገበው በኢትዮጵያቴሌቪዥን የተቀነባበረው ፊልም ፓትሪያርክ አቡነ መርቆሪዎስን ጨምሮ በሶስትአባቶች ላይ አተኩሯል።

ፓትሪያልክ አቡነ መርቆሪዮስን ከቀድሞው ስርአት ጋር ግንኙነት አላቸው የሚልውንጀላ የጨመረው ፊልም ብፁእ አቡነ መልክአ ጻዲቅን ለኢትዮጵያ ሙስሊሞች የመብት ጥያቄ ድጋፍ መስጠታቸውን በአሸባሪነት መፈረጁም ተመልክቶል::

በብጹ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ፓትሪያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያና በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሀፊ በብጹ አቡነ መልክአ ጻዲቅ እንዲሁም በብፁዕ አቡነ መቃሪዎስ ላይ የተነጣጠረው ይህ ዶክመንተሪ ፊልም በቅርቡም ይቀርባል ተብሎ እየተጠበቀ ነው::

ብጹ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስ ነፍጥ ካነሱ ሀይሎች በተልይም ከግንቦት ሰባትና አርበኞች ግንባር ጋር ይሰራሉ ተብ የተወነጀሉ ሲሆን በአሸባሪነትም ተፈርጀዋል ተብሎል::

በዚህ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይቀርባል በተባለው ፊልም ላይ ንቡረዕድ ኤሊያስ አብርሀና 3 ሊቃነ ጳጳሳት በአስረጂነት መካተታቸውም ተመልክቶል:: ሌሎች አባቶችም ፍቃደኛ አለመሆናቸውም ከዘገባው ለመረዳት ተችሎል:;

የፊልሙ ርዝማኔ 1 ፡ 30 ሲሆን በሁለት ክፍል ይቀርባል ተብሎ እየተጠበቀ ነው::

የባለራእይ ወጣቶች ማህበር የአመራር አባላት ማደኛ ወጣባቸው



ከአመራሩ ለመረዳት እንደቻለው፣ የፍርድ ቤት የእስር ትእዛዝ የወጣባቸው በማህበሩ ሊ/መንበር በወጣት ሀብታሙ አያሌው፣ በምክትሉ ሚኬኤል አለማየሁ እና በህዝብ ግንኙነት ሀላፊው በብርሀኑ ተክለያሬድ ላይ ነው።

ወጣት ብርሀኑ በፖሊስ ተይዞ እስር ቤት የገባ ሲሆን፣ ሊቀመንበሩና ምክትሉ ዜናውን እስካጠናከርንበት ጊዜ ድረስ አልተያዙም። ግለሰቦቹን በግንቦት7 ስም ለመክሰስ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል።


በቅርቡ የመንግስት የደህንነት ሀይሎች የማህበሩ የአመራር አባል የሆነች ወጣትን መርፌ በመውጋት አፍነው ከወሰዱዋት በሁዋላ፣ አመራሮቹ ከግንቦት7 ጋር ይገናኙ ነበር ብለሽ ተናገሪ እየተባለች መደብደቡን መዘገባችን ይታወሳል።

ኢሳት ለማረጋጋጥ እንደቻለው ከብዙ ማንገራገር በሁዋላ ሆስፒታሉ ወጣቷ በመርፌ መወጋቷን የሚያሳይ የህክምና ማስረጃ ሰጥቷታል።

የቀድሞውጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ፎቶዎችና ፖስተሮች ይነሱ! ” ሲል ሪፖርተር ጋዜጣ ጠየቀ



ጋዜጣው በዛሬው ርዕሰ-አንቀጹ የ አቶ መለስ ፎቶና ፖስተር ያልተሰቀለበትን የ አዲስ አበባ ጎዳና ፈልጎ ማግኘት እንደማይቻልና ፎቷቸው በሁሉም ስፍራ እንዳለ በመጥቀስ፦<<አሁን ግን ይብቃ! ፎቶዎቹና ፖስተሮቹ ይነሱ!እንላለን>> ሰል በአጽንኦት ጠይቋል።

ፖስተሮቹ ሊያስተላልፉ የሚገባቸውን መልእክት በክብር እንደተሰቀሉ በክብር ይነሱ ያለው ጋዜጣው፤ ዝናምና ፀሀይ እስኪያበላሻቸው ዝም ብሎ መጠበቅ ማቆሸሽና ትርጉም ማሳጣት ነው ብሏል።

ፖስተሮቹ ዘላለማዊ ተደርገው መወሰድ እንደሌለባቸውም ጋዜጣው አቋሙን ገልጿል።

በማያያዝም፦<<በፖስተሮቹና በፎቶግራፎቹ መሰቀል ለመነገድ፣ ለማስመሰልና ለማጭበርበር የሚፈልግ ሰው ካለም በቃህ ሊባል ይገባል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ስም አትነግድ፣ አታጭበርብር፣ አታታል ሊባል ይገባዋል፡፡>>ብሏል።

ከዚህም ሌላ በቅርቡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የ አቶ መለስ ፋውንዴሽን እንዲቋቋም መወሰኑን ያወሳው ጋዜጣው፤ ፋውንዴሽኑን ለምን ተቋቋመ? የሚል ተቃውሞ ባይኖረውም ፤የመቋቋሙ ጉዳይ በፓርላማ መታወጅ እንደማይጠበቅበት አስፍሯል።

እንደ ጋዜጣው ርዕሰ-አንቀጽ ፋውንዴሽኑ በቤተሰብ፣በወዳጆች፣በደጋፊዎችና በፖለቲካ ፓርቲዎች በህግ ሳይሆን በፈቃደኝነትና በፍላጎት ሊቋቋም ይችል ነበር።

አስከትሎም፦<<በተግባር የማይደገፍ የፎቶና የፖስተር መለጣጠፍ መንፈስ ግን ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም፡፡ ሒደቱም በጊዜ ወሰን ውስጥ ሊከናወን ይገባል፡፡ በመሆኑም የዚህ ዓይነቱን ጨዋታ አቁመን ተግባር ላይ እናተኩር፡፡ ፖስተሮቹ ይነሱ፡፡

 ፎቶዎች ይነሱ፡፡ እየተቀዳደዱና እየቆሸሹ ናቸው፡፡>>ብሏል።

ቃላትም ትርጉም ይኑራቸው፡፡ በቃላት ድርደራ ብቻ ‹‹ራዕይ›› እና ‹‹ሌጋሲ›› እያልን እየለፈለፍን በተግባር ግን ራዕዩንና ሌጋሲውን የሚፃረር ሥራ የምንሠራ ከሆነ ያስተዛዝባል>>ያለው ሪፖርተር፤ << የእሳቸውን ስምና ሥራ መነገጃና መደለያ የምናደርገው ከሆነ ከሞራል አንፃር ያስወቅሰናል ብቻ ሳይሆን በታሪክም እንጠየቅበታለን>>ብሏል።

ከርእሰ አንቀጹ ስር በርካታ አንባብያን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

መለስ 123 የተባለ አስተያዬት ሰጪ፦<<ሁሉም ሰው ፎቶውን ማዬት ሰልችቷል፤አንገሽግሾታል ወደዚያ አንሱልን>>ሲል፤ቶማስ ቶማስ የተባለ ደግሞ፦<<እኔን የናፈቀኝ ቀጥሎ ደግሞ የማን እንደሚሰቀል ማወቅ ነው>>ብሏል።

ጀፒዲዲ የተባለ አስተያዬት ሰዐጪ ደግሞ፦<<ስለመለስ ዜናዊ መስማቱና ማየቱ የኢትዮጵያን ሕዝብ አንገሽግሾታል እጅ እጅ ብሎታል ሀገር ጥሎ ቢጥፋ ደስ ይለዋል ፎቶዎቹን የሚቀዳድድባቸው ጊዜ እየናፈቀ ነው >>ብሏል።

ኢትዮጵዮፍርደም ደግሞ ” በለውጡ ጊዜ የምንቀደው እንዳናጣ ይቀመጡ ብሎአል። የፖስተሩን መቀመጥ የደገፉ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎችም ሀሰባቸውን አስፍረዋል።

ኢሳት በባንቢስ አካባቢ ያሉት የመለስ ፎቶዎች እንዲወርዱ መደረጋቸውን ከወር በፊት መዘገቡ ይታወሳል። ሪፖርተር በይፋ ፎቶዎቹ ይነሱ የሚል ቅስቀሳ የጀመረው የኢህአዴግ መሪዎችን ከጎኑ አሰልፎ ከሆ እቅዱ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል፣ ጋዜጣው በራሱ ተነሳሽነት ያሰፈረው ሀሳብ ከሆነ ግን ጋዜጣውን ከኢህአዴግ ጋር የሚያላትመው ይሆናል፣ ምክንያቱም ኢህአዴግ ለፖስተሮቹ ማሰሪያ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አፍስሶባቸዋልና ሲል አንድ አስተያየት ሰጪ ተናግሯል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የመለስን ህይወት ታሪክ የያዘውን አዲስ ራእይ መጽሄት የኢህአዴግ አባል የሆኑት በመላ በ100 ብር ሁለት ሁለት ቅጅ እንዲገዙ በመታዘዛቸው አባላቱ ቅሬታቸውን እያቀረቡ ነው።

 አባላቱ ለኢሳት እንደተናገሩት መጽሄቱ የታሰበውን ያክል ሊሸጥ ባለመቻሉ እያንዳንዱ አባል እንዲገዛ ግዴታ ተጥሎበታል።

አንድነት ፓርቲ ጀሃዳዊ ሀረካትን አጣጣለው



በ‹‹ጀሃዳዊ ሃረካት›› ትረካ የሙስሊሙን ማህበረሰብ ጥያቄ ማዳፈን አይቻልም!” በሚል ርእስ ባወጣው መግለጫ፣ በገዢው ፓርቲ ድርጊት ማፈሩንና ማዘኑን ገልጿል።

 ገዥው ፓርቲ ዜጎች በማንኛውም መንገድ የሚያነሱትን ጥያቄ በግልጽና በውይይት መፍታት ያለመፈለጉ ግልጽ ሀገራዊ አደጋ እየሆነ መምጣቱ እየታየው ነው የሚለው አንድነት፣ “ኢትዮጵያን የምታክል ትልቅ ሀገር እያስተዳደረ ባለ መንግሥት” ማዘኑንም አልሸሸገም።

አንድነት በኢትዮጵያ ሕዝብ ግብር የሚተዳደረው ነገር ግን የገዥው ፓርቲ መሳሪያ በመሆን የሕዝብ ጥያቄዎችን ለማፈን ተባባሪ መሳሪያ ሆኖ እያለገለ ያለው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ‹‹ጀሃዳዊ ሃረካት›› በሚል የተሰናዳና እንደተለመደው የሙስሊሙን ህዝብ ጥያቄን ለማዳፈን የተዘጋጀ አይነት ትረካ ሲያቀርብ የመጀመሪያው አለመሆኑን አስታውሷል።

ዶክመንታሪዎች የሚሰጣቸው ርዕስ ግዝፈትና የአጽመ ታሪካቸው ትረካ ልልነት ከተራ ድራማም ያነሰ ነው ሲል ፣ በኢቲቪ ትናንት የተላለፈውን ፊልም ያጣጣለው አንድነት፣ ትረካው የቀረበው የሙስሊሙን አንድ ዓመት የዘለቀ ግልፅ ጥያቄ ፊት ለፊት ተወያይቶ በመመለስ ፋንታ በእጅ አዙር ለማድበስበስ ፣ በዜጎች ላይ የስነ-ልቡና ጫና በመፍጠር በፍርሓት ውስጥ አድርጎ ለመግዛት በማለም ፣ መንግሥት እጁን አስረዝሞ በኃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ በመግባት የሚያደርገውን የአድራጊ ፈጣሪነት ስራ ‹‹ሕግ ማስከበር›› የሚል ሽፋን በመስጠት የማደናገር ስራ ለመስራት ነው ብሎአል፡፡

ይህ ዶክመንተሪ በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት አራተኛ ወንጀል ችሎት የዕግድ ትእዛዝ ቢተላለፍበትም በማናለብኝነትና ሥልጣንን ካለአግባብ በመጠቀም ያለምንም ይግባኝ በከፍተኛው ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት ተሽሮ ለኢትዮጵያ ህዝብ እንዲተላለፍ መደረጉን ስንመለከት፣ ራሱ ህግ የሚጥስ ገዢ ፓርቲ እንዴት የሌሎችን ህግ ሊያስከብር ይችላል በማለት ጠይቋል።

ፓርቲው በመጨረሻም ” ‹‹ጀሃዳዊ ሃረካት›› የሚል ትረካ በማቅረብ የሙስሊሙን ጥያቄ ማዳፈን አይቻልም፡፡ ዶክመንተሪው የሙስሊሙ ማህበረሰብ ጥያቄ መልስ ሊሆንም አይችልም፡፡

” ብሎአል።በተመሳሳይ ዜና ኢቲቪ ያስተላለፈው ፊልም የመንግስትን ማንነት ከማጋለጥ ባለፈ ያስገኘው ለውጥ እንደሌለ የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን በማነጋገር ዘጋቢያችን የላከው ሪፖርት ያሳያል። በተለያዩ መዝናኛ ቤቶች የሚገኙ ወጣቶች ጉዳዩን ሲወያዩበት መዋላቸውን የገለጠው ዘጋቢያችን፣ ድራማው ከአቀነባበር ጀምሮ የታየበት ችግር ህዝቡ የመንግስትን ትክክለኛ ማንነት እንዲረዳ እንዳደረገው ገልጿል።

 ይህ በእንዲህ እንዳለ የድምጻችን ይሰማ መሪዎች ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አቡበክር አህመድ ሲመረመሩ የሚያሳይ ቪዲዮ በዩቱዩብ ከተለቀቀ በሁዋላ፣ በርካታ ኢትዮጵያውያን በማህበራዊ የመገናኛ ዘዴዎች ላይ በመንግስት ማፈራቸውን እየገለጡ ነው።

søndag 3. februar 2013

የጎንደር ዩኒቨርስቲ ሙስሊም ተማሪዎች የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ



ወደ አንድ ሺ የሚጠጉ የዩኒቨርስቲው ተማሪዎች ዛሬ ባካሄዱት ሰላማዊ ሰልፍ በትናንትናው እለት በደህንነት ሀይሎች ታፍነው የተወሰዱት 2ቱ ጓደኞቻቸው የት እንዳሉ ዩኒቨርስቲው እንዲያሳውቃቸው ጠይቀዋል።

የዩኒቨርስቲው አስተዳዳሪዎች ከተማሪዎች ለቀረበው ጥያቄ ” ተማሪዎቹ በደህንነት ሀይሎች ተፈልገው የተወሰዱ በመሆኑ እኛ ምንም ማድረግ አንችልንም፣ ለወደፊቱም የፍርድ ቤት ማዘዣ ይዘው ከመጡ አሳልፈን እንሰጣለን” በማለት መልስ መስጠታቸው ታውቋል።

በሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተሳተፉ ተማሪዎች እንደገለጡት በሙስሊም ተማሪዎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ እየጨመረ በመምጣቱ ትምህርታቸውን ተረጋግተው ለመማር አልቻሉም።

በደህንነት ሀይሎች የተወሰዱት ሰይድ እና ኡመር የተባሉት ተማሪዎች በዚህ አመት ይመረቃሉ ተብሎ ይጠበቅ ነበር። በሙስሊም የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ላይ የሚደርሰው ጉዳት እየጨመረ መምጣቱን መዘገባችን ይታወሳል።

በተመሳሳይ ዜና በሐረር ኢማን መስጂድ ዘበኛ የነበሩት ስማቸው ለጊዜው ያልታወቀው ግለሰብ በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸው ታውቋል።

 ግለሰቡ ከመገደላቸው በፊት በአካባቢው መብራት ጠፍቶ የነበረ ሲሆን፣ ሁኔታው ከተረጋጋ በሁዋላ መብራት ተመልሶ መምጣቱ ታውቋል።

መንግስት በጉዳዩ ዙሪያ እስካሁን የሰጠው መልስ የለም።

”የመለስ ወራሾች አገሪቷን ወደ ድቅድቅ ጨለማ እየከተቷት ነው” ሲል ጋዜጠኛተመስገን ደሳለኝ ገለጸ


ጋዜጠኛ ተመስገን ይህን ያለው፤ <<የመለስ ራዕይ በ አዲስ ታይምስ መጽሔት ተተገበረ>>በሚል ርዕስ የአዲስ ታይምስን መዘጋት አስመልክቶ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ ባሰፈረው ማስታወሻ ነው።

“ምንም ጥርጥር የለውም መለስ ዜናዊ ፍፁም አምባገነን ነበር፡፡ ምንም ጥርጥር የለውም ከአንድ ክፍለ ጦር በላይ የተለየ ሀሳብን እና ነፃ ሚዲያን ይፈራ ነበር>> በማለት አስተያዬቱን መስጠት የጀመረው ተመስገን፤ << ወራሾቹም ሀሳቡን በነፃነት የሚገልፅን ከመለስ በባሰ መልኩ ይፈራሉ፡፡

 ይህ ፍራቻቸው ወደ ጭፍን አምባገነንነት ስለቀየራቸው መላ ሀገሪቷን ወደ ድቅድቅ ጨለማ እየገፏት ነው፡፡
>> ብላል።
አቶ መለስ ከአደባባይ ከተሰወሩ በኋላ በፍትህ ቤተሰቦች የሚመራ ትልቅ ሚዲያ ሲዘጋ ‹‹አዲስ ታይምስ›› ሁለተኛዋ መሆኗን

ያወሳው ጋዜጠኛ ተመስገን፤ ለ‹‹አዲስ ታይምስ›› መዘጋት መንግስት የሰጣቸው ሦስት ምክንያቶችም-የባለቤትነት ድርሻ ከአንዱ ወደ ሌላው ሲዞር በ15 ቀን ውስጥ አላሳወቃችሁም፣ ህትመቱ ሲወጣ ለቤተ-መዛግብት ሁለት ሁለት ኮፒ በነፃ አልሰጣችሁም እና የገንዘብ ምንጫችሁ አይታወቅም የሚሉ መሆናቸውን አመልክቷል።

እንደተመስገን ገለፃ የተሰጠው ምክንያት ፈጽሞ ውሸት ነው።

ምክንያቱም እሱ እንዳለው የባለቤትነት ድርሻ ሲዞር በጊዜው አሳውቀዋል፣ ህትመቱ ሲወጣም ለቤተ-መዛግብት ሁለት ሁለት ብቻ ሳይሆን ሳይሆን አምስት አምስት ኮፒ በነፃ የሰጠንበትን ማስረጃ አቅርበዋል፣ ምንጩ አይታወቅም ለሚለው ደግሞ የመፅሄቱ ኮፒ 35 ሺህ በመሆኑ ምንጩ ህዝባችን(አንባቢያን) መሆናቸውን ብሮድ ካስት አብጠርጥሮ ያውቃል።


ተመስገን አያይዞም፦<<አልተፈጸሙም እንጂ እነዚህ የተጠቀሱት ምክንያቶችስ ተፈፅመው ቢሆን እንኳ አዋጁ የሚለው አስራ አምስት ሺህ ብር ያስቀጣል ነው።ታዲያ መዝጋትን ከየት ያመጡት ህግ ነው? ማንአለብኝነት እና ጉልበተኝነት ካልሆነ በቀር፡፡>>ብሏል።

በነገራችን ላይ ‹‹ብሮድ ካስት›› በሚል ስያሜ የተመሰረተ ተቋም ከቴሌቪዥንና ራዲዮን ውጭ ያልተፈቀደለትን የ‹‹ህትመት ሚዲያ››ንም ጨምሮ መቆጣጠሩ ከበረከት ስምዖን ውጪ ለማንም ግልፅ አይደለም ያለው ጋዜጠኛ ተመስገን፤ ለቤተ-መፅሀፍት መፅሄት ማስገባትን እና አለማስገባትንም እንዲሁ ከሙያ ብቃት ጋር ያላቸውን ግንኙነት የሚያውቀው በረከት ብቻ ነው ፡፡

>>ብላል።

አክሎም፦<<… አሁን የመለስ ራዕይ ግልፅ ነው፤ አፈናውን አጠናክሮ ማስቀጠል ነው>> ብሏል ጋዜጠኛ ተመስገን።'

“መቼም ሃያ አንድ ዓመት ሙሉ በስልጣን ላይ ተቀምጦ ምንም ያልፈየደን መሪ፣ ልክ ስልጣን በያዘ ማግስት ህይወቱ እንዳለፈ ሰው ሁሉ፦ ‹‹ራዕይ ነበረው፣ እናስቀጥለዋለን… ጂኒ ቁልቋል ማለቱ በህዝብ ላይ ማላገጥ ነው>>ያለው ተመስገን፤ ለሀገር የሚጠቅም ራዕይ ቢኖረው ኖሮ፣ በስልጣን ላይ ያሳለፋቸው ሃያ አንድ ዓመታት ከበቂ በላይ ነበሩና፡፡
>>ብላል።

ሀሳቡን ሲቋጭም፦<<ዋናው ጥያቄ ግን ‹‹ይህ የቀልድ ዘመን ዕድሜው ስንት ነው?›› የሚል ነው፡፡ ስድስት ወር? አንድ ዓመት? ወይስ ሁለት ዓመት? ….በጣም… በጣም በቅርቡ የምናየው ይሆናል….በዓለም አቀፍ መድረክ የተሸነፈበትንም ታላቅ ዜና ጊዜው ሲደርስ እንሰማለን፡፡

>>ብላል።

ኦህዴድ ለሶስት ቡድኖች መከፋፈሉ ታወቀ



የኦህዴድ ምንጮች እንደገለጡት በአብዛኛው የኦሮሚያ ዞኖች በተለይም በምስራቅ ኦሮሚያና በአርሲ ዞኖች የሚገኙ የድርጅቱ አባላት ለ3 ተከፍለው እርስ በርስ እየተካሰሱ ነው።

የክፍፍሉ መንስኤዎች በድርጅቱ እምነት ማጣት፣ ሙስናና የግል ጥቅምን ማሳደድ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሎአል።

አመራሮቹ እርስ በርስ እየተባሉ ይገኛሉ ያሉት ምንጮች፣ ሁኔታው በዚህ ከቀጠለ የድርጅቱ ህልውና ሊያከትም እንደሚችል ጠቁመዋል።

በዞን ደረጃ የሚታየው መከፋፋል ዋናዎቹን የኦህዴድ አመራሮችን መጨመሩንም ለማወቅ ተችሎአል። ሰሞኑን በዝግ በከፍተኛ አመራሮች ዙሪያ እየተካሄደ ያለው ግምገማ የዚህ አካል መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል።

ድርጅቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ መዳከሙን የገለጡት ምንጮች ክፍፍሉ እስከ ወረዳ መዝለቁንም ጠቁመዋል።

መድረክ ለረጅም ጊዜ ሲያጓትተው የነበረውን ማንፌስቶ አጸደቀ



ከፍተኛ ክርክር በታየበት የመድረክ ጉባኤ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ አባላት ማንፌስቶውንና መተዳደሪያ ደንቡን አጽድቀዋል። ባለ 25 ገጹ ማንፌስቶ ላለፉት ስድስት ወራት ሲዘጋጅ የቆየ ሲሆን ከ6 ሰአት በላይ በፈጀ ክርክር ጸድቋል:፡፡

 ላለፉት 4 አመታት ሲንከባለል የቆየውና የድርጅቶች የልዩነት ምንጭ ተደርጎ ይታይ የነበረው መተዳደሪያ ደንብም እንዲሁ ጸድቋል።

“በጣም ደስ የሚል ኢትዮጵያዊ መድረክ ነበር፣ ቋንቋው፣ ቀለሙ፣ አመለካከቱ፣ ሁሉም አንድ ቋንቋ ሲናገር ለመጀመሪያ ጊዜ ተመለከትን” በማለት አንድ ተሳታፊ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

መድረክ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች በጋራ የፈጠሩት ግንባር ነው።
'
ድርጅቱ አቶ ጥላሁን እንዳሻው በሊቀመንበርነት እንዲቆዩ ወስኗል።

fredag 1. februar 2013

በዱባይ የሚኖሩ 5 ነጋዴዎች ለአዳነ ግርማ መኪና አበረከቱለት



በዱባይ የሚኖሩ አምስት ኢትዮጵያውያን ነጋዴዎች የ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ኮከብ ተጫዋች ለሆነው አዳነ ግርማ ቶዮታ ኮሮላ መኪና ገዝተው ሰጡት።

ኢትዮጵያውያኑ ነጋዴዎች ለ አዳነ ግርማ የመኪና ስጦታ ያበረከቱለት ከሰላሳ አንድ አመት በሁዋላ ኢትዮጵያ ለኣፍሪካ ዋንጫ አልፋ ባደረገችው ውድድር ጎል ከማስቆጠሩና ኮከብ ተጨዋችነቱን በማስመስከሩ ነው።

ለአዳነ ግርማ የመኪና ስጦታ ያበረከቱለት ፦አቶ ጌታቸው ሙሶኮሬ ፥ አቶ ይልማ ተፈራ፥ ወ/ሮ ቀለም ተክሉ፥ አቶ መሃመድ የሱፍ እና ወ/ሮ ህሊና ነጋሽ የተባሉ ነጋዴዎች ናቸው።

ከዛምቢያ ጋር በተደረገው ጨዋታ ኮከብ ሆኖ የታየውና ቡድኑን አቻ ያደረገችውን ጎል ያስቆጠረው አዳነ፤ኢትዮጵያ ሁለተኛ ጫዋታዋን ከቡርኪናፋሶ ጋር ስታደርግ ዘጠነኛው ደቂቃ ላይ ተጎድቶ መውጣቱ፤ በቡድኑ አጨዋወት ላይ ክፍተት ከመፍጠሩም በላይ በተጫዎቹም ዘንድ አለመረጋጋትን አስከትሎ እንደነበር ይታወሳል።

በዳውሮ ዞን ሰዎች እየታሰሩ ነው



በዞኑ ያለው ችግር እየተባባሰ መሄዱን ተከትሎ ፣ የችግሮች ምንጭ ናቸው የተባሉ ግለሰቦች እየተያዙ ሲሆን፣ መምህር ጸጋየ ገብረመስቀል የተባሉት በቁጥጥር ስር ውለዋል። ሌሎች ሶስት ተፈላጊ መምህራን ለመሸሸግ የተገደዱ ሲሆን፣ ፖሊስ እያሳደዳቸው የሚገኙ የመንግስት ሰራተኞችም አሉ።

ከትናንት በስቲያ በእስር ላይ ከሚገኙት ከአቶ ዱባለ ገበየሁ እና ከሁለት ጠበቆች የእስር ቦታ ማዛወር ጋር በተያያዘ የታዘዙትን ለመፈጸም ፈቃደኛ ያልሆኑ ኮንስታብል ዘነበ ዶዮ እና ኮንስታብል ሚስታ ናቸው።

የታሳሪዎቹንና የታሰሩበትን እስር ቤት የሚያሳይ ፎቶግራፍ በፌስ ቡክ ላይ መለጠፉ ያስደነገጠው የዳውሮ ፖለቲካ ክፍል ሃላፊዎች በእስር ቤት እስረኞቹ ኮምፒተር ሳይጠቀሙ አይቀርም በሚል ሥጋት የሌሊት ጥበቃ ፖሊሶች በተጠናከረ ጥበቃ ሌሊቱን እንዲያሳልፉ ልዩ መመሪያ እንደተሰጣቸው ታውቋል።

ኢሳት እስር ቤት እያሉ ቃለመጠይቅ ያደረገላቸውን አቶ ዱባለ ገበየሁን በልዩ ሁኔታ ክትትል እንዲደረግባቸው የወረዳው ፖሊስ ትእዛዝ ደርሶታል። ከሌሎች እስረኞች ጋር ተቀላቅለው እንዳይታሰሩና ለብቻ ተለይተው እንዲታሰሩ ተደርጓል።

ሕዝቡን ቀስቅሰዋል በሚል ግምት የታሰሩትን ዐቃብያን ህጎች በግንቦት 7 አባልነት ለመክሰስ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ለማወቅ ተችሎአል።

የክልሉ ም/ል ፕሬዚዳንት አቶ አለማየሁ አሰፋ በመሩት የደህዴግ ካድሬዎች ስብሰባ ላይ አባሎቹ ችግሮችን ለማስታገስ ተብሎ የሚወሰደው የእሥራት እርምጃ ሕዝቡን ወደ ከፋ ሁኔታ ሊመራው ይችላል በማለት ስጋታቸውን ገልጸዋል።

የኔሰው ገብሬ ራሱን አቃጥሎ ባጠፋበት የዳውሮ ዞን የሚነሱ የመብት አሁንም እንደቀጠሉ ነው።

ሕዝቡ በምርጫ እንዳይሳተፍ ጥሪ ቀረበ



መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ኢህአዴግ ሊያካሂደው ባሰበው የአካባቢ ምርጫ እንዳይሳተፍ 39ኙ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥሪ አቀረቡ።

ፓርቲዎቹ ህዝባዊ ጥሪውን ያቀረቡት ”ኢህአዴግ ስለ አካባቢ ምርጫ የሰጠው መግለጫ የጥያቄዎቻችንን ትክክለኛነትና አግላይ አቋሙን ያረጋገጠበት ነው” በሚል ርዕስ ባወጡት መግለጫ ነው።

የ ኢህአዴግ ምክር ቤት ጸሀፊ አቶ ሬድዋን ሁሴን ፓርቲዎቹ በምርጫ ላለመሳተፍ መወሰናቸውን አስመልክቶ በቅርቡ በሰጡት መግለጫ ፦<<እነሱ ተሳተፉ አልተሳተፉ የሚጨምሩትም፤የሚቀንሱትም ነገር የለም>> ማለታቸው ይታወሳል።

የ አቶ ሬድዋን መግለጫ ኢህአዴግ ዛሬም በ አገራዊና ህዝባዊ ጉዳዮች ላይ ለሚነሱ ጥያቄዎች በሙሉ ወሳኝም፣ ባለመፍትሔም እኔ ብቻ ነኝ ከሚል የ እብሪት ስሜት አለመላቀቁንና ሀላፊነት በጎደለው ጭፍን ጥላቻ እየተነዳ መሆኑን ያመለክታል ብለዋል።

ባሻገር አህአዴግ በዋና ጸሀፊው አማካይነት የሰጠው መግለጫ በውሸት የታጀለ እና እርስ በርሱ የሚጣረስ እንደሆነ ፓርቲዎቹ በርካታ አብነቶችን በመጥቀስ አመላክተዋል።

አክለውም “ይህ አካሄድ ለማንም የማይጠቅም ከመሆኑም በላይ ብዙ ርቀት ሊያስኬደው እንደማይችል በድጋሚ ሊገለጽ ብቻ ሳይሆን በህዝባዊ ሀይል ሊገታ የሚገባው መሆኑን እንረዳለን” ሲሉም አስጠንቅቀዋል።

ደጋግመን እንደገለጽነው ጥያቄዎቻችን ቀላሎች ናቸው ያሉት ፓርቲዎቹ እነሱም፦መንግስትና ኢህአዴግ ይለያዩ፣የመገናኛ ብዙሀን ፍትሀዊ አጠቃቀም ይኑር!፣የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት የመንቀሳቀስ መብት ይከበር!፣ምርጫ ቦርድ ከገዥው ፓርቲ ተጽዕኖ ተላቅቆ በነፃነት ይደራጅ!የህግ የበላይነት ይረጋገጥ!፣በገዥው ፓርቲ አማካይነት ለ አፈና የወጡ ህጎች ይሻሩ! በድምሩ የዜጎች ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ተከብረው የህዝብ የሥልጣን ባለቤትነት ይረጋገጥ ዘንድ የምርጫ ሜዳው ይስተካከል የሚሉ ናቸው ሲሉም መሰረታዊ ጥያቄዎቻቸውን አስፍረዋል።

ነገር ግን ከ ኢህአዴግ መግለጫ ለመረዳት የቻልነው ገዥው ፓርቲ ባለፉት 21 ዓመታት በሄደበት የማናለብኝነትና የሀይል መንገድ ለመቀጠል መወሰኑን እና ችግሮችን ለማስተካከል ፈቃደኛ አለመሆኑን ነው ያሉት ፓርቲዎቹ፤በመሆኑም በምርጫው መሳተፍ የወንጀል አጃቢ ከመሆንና ለገዥው ፓርቲ ይሁኝታ ከመስጠት በዘለለ ፋይዳ እንደሌለው ተገንዝበናል ብለዋል።

መላው የ አገራችን ህዝብም የምርጫው አካል በመሆን ኢዲሞክራሲያዊና ኢህገ-መንግስታዊ ለሆነ አካሄድ ይሁኝታ እንዳይሰጥ ጥሪ እናቀርባለን በማለትም ህዝቡ በምርጫው እንዳይሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል።

<<ፓርቲዎቹ መግለጫቸውን ሲቋጩም፦በተባበረና በተቀናጀ ህዝባዊና ሰላማዊ ትግል ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት፤እንዲሁም ከድርጅታችን ይልቅ ለ አገራዊ የህዝብ ጉዳዮች ቅድሚያ በመስጠት በትብብር ለመሥራት ቃላችንን እናድሳለን>>ብለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢህአዴግ ለምርጫ ቀስቃሾች የሚያወጣው ገንዘብ አስደንጋጭ ሆኗል
ኢህአዴግ በመጪው ሚያዚያ ወር ለሚካሄደው የአዲስ አበባ፣ የድሬዳዋ ከተሞች እና የክልል ምክር ቤቶች እና የወረዳዎች ምርጫ በርካታ ሰዎች የምርጫ ካርድ እንዲያወጡ ቤት ለቤት ለሚቀሰቅሱለት ካድሬዎቹ የቀን ውሎ አበል እና የስብሰባዎችና ድግሶች በሚሊዮኖች የመንግሥት ገንዘብ እያወጣ መሆኑን ምንጮች አስታወቁ፡፡

በርካታ ሰዎች ካርድ እንዲያወጡ ቤት ለቤት እንዲቀሰቅሱ መልምሎ የላካቸው በዝቅተኛ ገቢ ላይ የሚገኙ እናቶችን፣ ሴቶችን እና ወጣቶችን ከሴቶች ሊግ፣ ከወጣቶች ሊጎች እና ፎረምና ወጣት ማህበራት እና ዝቅተኛ የየአካባቢው ካድሬዎቹን መልምሎ ሲሆን በቀን ከሃምሳ ብር እስከ 250 እንደ ቀኑ ውጤታቸውና ደረጃቸው እየከፈለ ነው ፡፡

ለአንዳንዶቹም በድርጅቱ ደብዳቤ ለሚመለከታቸው የሥራ መስኮች- የአንበሳ አቡቶቡስ ቴኬት ቆራጭነት፣ በየሴክተርና የመንግሥት መስሪያ ቤቶች በተላላኪነት፣ በአትክልተኝነት፣ በጥበቃ ሠራተኝነት ለመቅጠር ቃል በመግባትና የድጋፍ ደብዳቤ በመስጠት እና ነቃ ያሉ ወጣቶችን ደግሞ ተደራጅተው በሚፈልጉት የሥራ መስክ እንዲሰማሩ የገንዘብ ብድርና የመሥሪያ ቦታ ለማመቻቸት ቃል እንደገባላቸው ታውቋል፡፡ ያስቀመጠው የምርጫ ኮታ ባለመሙላቱም በልዩ ልዩ ምክንያት ላልተመዘገቡ ሰዎች በሚል ምርጫ ቦርድ ለተወሰኑ ተጨማሪ ቀናት ምዝገባውን እንዲቀጥል በውስጥ ደብዳቤ አዞአል ፡፡

የኢህአዴግ ካድሬዎችና በየማህበራቱ ያደራጃቸው ወጣቶች ቤት ለቤት በሚያደርጉት የማስመዝገብ ዘመቻ የቤቱ አባወራ እና እማወራ በማያውቁበት ሁኔታ በቤት ውስጥ ለእንግድነት የመጡ ሰዎችን፣ የቤት ውስጥ ሠራተኞችን ሳይቀር ጊዜያዊ የቀበሌ መታወቂያ ወረቀት በቀበሌዎችና ወረዳዎች በማሰጠት ድርጅቱ ያሰበውን ኮታ ለማሟላት ሌት ተቀን ሲሰራ ቆይቷል።

የአዲስ አበባ ኢህአዴግ ጽ/ቤት የዜና ምንጮቻችን እንደገለጹልን ኢህአዴግ በርካታ ሰዎችን በአንድ ለአምስት የጥርነፋ ዘዬው (ስትራቴጂ) የምርጫ ካርድ እንዲያወጡለት የፈለገው፣ በምርጫው ወቅት የምርጫ ካርድ ያወጡ ሰዎችን እንዴት አድርጎ የምርጫ ካርዳቸውን ወደ እራሱ የድምጽ ኮሮጆ የሚያስገባበትን የተጠና ዘዬ ለመተግበር ዝግጅቱን በማጠናቀቁ ነው ብለውናል፡፡