torsdag 31. juli 2014

ወያኔ ቆርጦ መቀጠልም ተሳናት ! የአቶ አንዳርጋቸው ቃልና የወያኔ ፕሮፓጋንዳ (ሳምሶን አስፋው)

ሰሞኑን በወያኔ መንግስት የፖሊስ ፕሮግራም የቀረበው “አቶ አንዳርጋቸው ለመንግስት ጠቃሚ መረጃ ሰጡ” የሚለው ዜና ኢትዮጵያዊውን ሁሉ እያነጋገረ ያለ ጉዳይ ነው። የዜናው አነጋጋሪነት የሚነሳው ለዜናው አብይ ግብአት እንዲሆን፤ በወጉም ሳይታሰብበት ተለጣጥፎ የቀረበው የቪዲዮ ክሊፕ የዜናውን ጩኸት አለማስተጋባቱ ነው ።
በመጀመሪያ የምናነሳው ጥያቄ የወያኔ ባለስልጣናት ይህንን በተራ ግለሰብ እንኳ ቢቀርብ የሚያሳፍር ደካማ የማስመሰል ስራ በመንግስት ደረጃ ለማቅረብ ያስገደዳቸው ምንድነው? የሚለውን ጥያቄ ይመስለኛል።
ለዚህ ደግሞ የተለያዩ መላምቶችን መሰንዘር እንችላለን። መላምቶቹን ወደ ኋላ እንመለሰባቸዋለን። አሁን ለዜናው ግብአት ሆኖ በተለጣጠፈው ክሊፕ ውስጥ ምን አለ? አቶ አንዳርጋቸው ምን ተናገሩ? የቪዲዮው ምስላዊ ይዘትስ ምን ይመስላል? ወደሚሉት ተከታታይና ተወራራሽ ጥያቄዎች እናምራ።
አቶ አንዳርጋቸው ምን ተናገሩ? ቋጠሮ ገጽ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ሳምሶን አስፋው የሚለው አለ። ላማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ….

እስላም እና ክርስቲያን የተከባበሩበት የኢድ በዓል – ኮልፌ ቀራንዮ

ባለፈው ሰኞ የኢድ በአል በሙስሊሞች በኩል ሲከበር፤ የዚያኑ እለት ደግሞ ማርያም የምትነግስበት እለት ነበር። በአዲስ አበባ ከተማ አጠገብ ላጠገብ ከተሰሩት መስጊድ እና ቤተ ክርስቲያን መካከል በኮልፌ ቀራንዮ ወረዳ 11 የሚገኙት የፊሊጶስ ቤተ ክርስቲያን እና የኢማም ሃሰን መስጊድ ይጠቀሳሉ። እናም ባለፈው ሰኞ የኢድ በአል ሲከበር በሁለቱ የእምነት ተከታዮች መካከል የታየው መተሳሰብ፤ በታሪካዊነት የሚጠቀስ፣ ለሌሎችም  ትምህርት የሚሆን ነውና… የሆነውን አጋጣሚ እዚህ ላይ ለመጥቀስ እንወዳለን።
እለቱ እንደኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች እምነት፤ ወር በገባ 21ኛው ቀን ማርያም የምትዘከርበት ነው። በመሆኑም ቅዳሴ እና ውዳሴ ማርያም በየቤተክርስቲያኑ ይከናወናል። እናም በኮልፌ ቀራንዮ በሚገኘው የፊሊጶስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የተገኙ የእምነቱ ተከታዮች እንደተለመደው የግቢ እና የውጭውን ስፒከር ከፍ አድርገው ቅዳሴ ያከናውናሉ። በሌላ በኩል ደግሞ ከዚያ አጠገብ የሚገኘው ኢማም ሃሰን መስጊድ የኢድ በአል ለማክበር በተዘጋጁ ሙስሊሞች መጨናነቅ ጀምሯል።
ትንሽ እንደቆዩ ሙስሊሞቹ መስገድ ሲጀምሩ እና ተክቢራ ማድረግ ሲጀምሩ ግን ብዙዎች ያልጠበቁት ነገር ሆነ። የፊሊጶስ ቤተ ክርስቲያን ወደ ውጭ የሚሰማውን ስፒከር ዘግተው፤ የውስጡን ብቻ ለህዝበ ክርስቲያኑ በመክፈት በተመጠነ ድምጽ ቅዳሴያቸውን ማከናወን ጀመሩ። ይህም የሙስሊሞችን ስግደት እና ተክቢራ ላለማስተጓጎል የተደረገ ነገር ነበር።
ፊሊጶስ ቤተ ክርስቲያን ይህን ብቻ አልነበረም ያደረገው። ከሙስሊሙ እና ከመስጊዱ ጋር የሚያገናኘውን ዋናውን የቤተ ክርስቲያን በር በመዝጋት እና በሎሚ ሜዳ በኩል ያለውን የጓሮ በር በመክፈት ህዝበ ክርስቲያኑ የሙስሊሙን ስግደት እና ተክቢራ እንዳያስተጓጉል ትብብር ሲደረግ ታይቷል።
በኢ.ኤም.ኤፍ በኩል ይህ ዘገባ እንዲቀርብ የተፈለገበት ዋናው ምክንያት፤ አሁን ያለው መንግስት በሙስሊሙ እና ክርስቲያኑ መካከል ክፍፍል በመፍጠር እርስ በርስ በጠላትነት እንዲተያዩ ለማድረግ የሚያደርገው ጥረት የማይሰራ መሆኑን ለማሳየት ነው። በማወቅም ሆነ ባለማወቅ አንዳንድ ሙስሊሞች ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በነሱ ላይ ጥላቻ እንዳላቸው አድርገው ልዩነቱን ለማስፋት የሚያደርጉትን ጥረት ለመከላከል ነው። እውነቱ ግን አንድ ነው። ኢትዮጵያውያን ሙስሊም እና ክርስቲያኖች “ሃይማኖት የግል” እንደሆነ ያምናሉ። እርስ በርስም ይከባበራሉ። አሁን ገዢዎች እንደሚሉት ሳይሆን፤ ከዚህ በፊት በነበሩት ታሪኮች ሁለቱም ወገኖች ተባብረው ሲሰሩ ታይተዋል። ቤተ ክርስቲያን ሲሰራ የረዱ ሙስሊሞች እንደነበሩ ሁሉ፤ መስጊድ ሲገነባ የገነቡ ክርስቲያኖችም ነበሩ። በፊሊጶስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የታየው ትብብርም ይህንንኑ መከባበር እና ጨዋነትን የሚያድስ ነው።
ፋሲካ እና ገና ሲመጣ ክርስቲያኖችን “እንኳን አደረሳቹህ” የሚሉ ሙስሊሞች እንዳሉ ሁሉ፤ የረመዳን ጾም አብቅቶ ኢድ ሲመጣ “ኢድ ሙባረክ” በማለት ለሙስሊሞች መልካም ምኞታቸውን የሚገልጹ፤ ብሎም እርስ በርስ የሚገባበዙ ኢትዮጵያውያን በርካቶች ናቸው። ይህንን መከባበር እና ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ለልጆቻችን ልናወርስ ይገባል እንጂ፤ ገዢዎች እንደሚፈልጉት በሃይማኖት ልነከፋፈል አይገባም – የዛሬው መልእክታችን ነው። ቢዘገይም “ኢድ ሙባረክ” ብለናል።

onsdag 30. juli 2014

ኦሮሞ እና እስልምና በ“ሕዳሴ አብዮት” መስመር (ተመስገን ደሳለኝ)

በወርሃ-ግንቦት ላይ ለዘመናት የተንሰራፋውን ሀገራዊ ደዌ ይፈውሳል ብዬ ተስፋ ስለማደርግበት “የሕዳሴ አብዮት” በሶስት ተከታታይ ክፍሎች ለመዳሰስ መሞከሬ ይታወሳል፡፡ በወቅቱ መጪው የ “ሕዳሴ አብዮታችን” መፍትሔ ሊሰጥባቸው ከሚገቡ ጉዳዮች መሀል በዋነኝነት የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪው ማሕበረሰብ እና የእስልምና እምነት ተከታዮች የመብት ጥያቄን በተመለከተ በጥቅሉ ጠቃቅሼው አልፌ ነበር፡፡ ሆኖም ‘ሰፋ ብሎ ቢዳሰስ’ የሚሉ በተለያየ መንገድ የሚቀርቡ ጎትጓች ድምፆች መበራከታቸው የመነሻ ሃሳቡን ፈታ አድርጌ እንዳቀርብ አስገድዶኛል፤ እንግዲህ ይህ ጭብጥም የዛው ተከታይ መሆኑ ይሰመርልኝ፡፡
የኦሮሞ ጥያቄ
በኢትዮጵያችን ከሚገኙ በርካታ ብሔሮች መካከል አብላጫውን ቁጥር የሚይዘው ኦሮምኛ ተናጋሪው ቢሆንም፣ ለዘመናት ይደርሱበት ከነበሩ ሥርዓታዊ በደሎች እና የባሕል ጭፍለቃዎች ዛሬም በምልአት ነፃ እንዳልወጣ በቂ ማሳያዎች አሉ፡፡ በ1960ዎቹ አጋማሽ የአገሪቷ አደባባዮች የዘመኑን መንፈስ በተረዱ ቁጡ ወጣቶች መጥለቅለቁን ተከትሎ፣ ‹በንጉሣዊው አገዛዝ ግብዓተ-መሬት ላይ የመጨረሻዋን ድንጋይ ለማስቀመጥ› በሚል ሰበብ ቤተ-መንግስቱን መቆጣጠር የቻለው ወታደራዊው ደርግ፣ ህልቆ መሳፍርት በሌለው መስዋዕትነት የተገኘውን ወርቃማ ዕድል ከጅማሮው አጨናፍጎታል፡፡ በግልባጩ አብዮቱን ካጋሙት ገፊ-ምክንያቶች ዋንኞቹ ለሆኑት የብሔርና የሕዝባዊ መንግስት ምስረታ ጥያቄዎች፣ መፍትሄ ይስጥ አይስጥ እስኪረጋገጥ ድረስ መታገስ ያልፈለገው ህወሓት፣ ጉዳዩ በደም መፋሰስ ብቻ እንደሚፈታ አውጆ ጫካ ሲገባ አዲሱ መንግስት ገና የ6 ወር ጨቅላ እንደነበረ አይዘነጋም፡፡ ይሁንና ታሪክ በአስከፊ መልኩ ራሱን ሲደግም ያስተዋልነው ወታደራዊውን መንግስት መንፈቅ-ዓመት ያህል እንኳ መታገስ ያልፈቀደው ይህ ቡድን፣ ለጥያቄዎቹ መልስ ሳይሰጥ ከሁለት አስርታት በላይ ያለመንግራገጭ በሥልጣን ለመቆየት ባለመቸገሩ ነው፤ ርግጥ የእኔ ትውልድም የእድሜውን እኩሌታ በትግስት መጠበቁ የአደባባይ እውነታ ቢሆንም፣ ተጨማሪ የቻይነት ዓመታት ይኖራሉ ብዬ ግን አላስብም፤ አብዮቱን ምኩንያዊ የሚያደርገውም ይህ ነው፡፡ …እነሆም ከአራት አስርታት በላይ ሲንከባለሉ የቆዩት የኦሮሞ ጥያቄዎች በ“ሕዳሴ አብዮት” ይፈቱ ዘንዳ፣ ሊተኩርባቸው የሚገቡ አንኳር አጀንዳዎችን በሁለት አውድ ከፍለን እንመለከታለን፡፡
ኢህአዴግ-መራሹ መንግስት ጥያቄዎቹን ከወረቀት ድንጋጌ (ከአፋዊነት) እና ከፕሮፓጋንዳ ሽንገላ ባለፈ፣ እውነተኛ መፍትሔ በሚያስገኝ መልኩ እልባት ሊያበጅላቸው አልፈቀደም፤ ባለፉት ሃያ ሶስት ዓመታት ‹‹አነበርኩት›› የሚለው ቋንቋ ተኮር ፌዴራሊዝም የይስሙላ ስለመሆኑ ለመገንዘብ፣ ዛሬም ከደርዝን በላይ የፖለቲካ ድርጅቶች የራስ አስተዳደር ጥያቄን አንግበው በትግል መድረክ መገኘታቸውን ማየቱ በቂ ነው፡፡ የክልሉ ‹‹ገዥ›› እንደሆነ የሚነገርለት ኦህዴድም ቢሆን፣ የህወሓቱ የአማርኛ ክንፍ እንደሆነው ብአዴን ሁሉ፣ የኦሮምኛ ክንፍ ከመሆን አለማለፉን፣ የብሔሩ ልሂቃንን ጨምሮ የፌደራል ሥርዓቱን አወቃቀር ያጠኑ በርካታ ምሁራን ማስረጃ እያጣቀሱ ያጋለጡት እውነታ ነው፡፡ ሕዝቡም በየጊዜውና በየአጋጣሚው የሚያነሳው ጥያቄ አሁንም ተግ አለማለቱ የልሂቃኑ ማስረጃ መሬት መርገጡን ያስረዳል፡፡ በቅርቡ አፈ-ጉባኤ አባዱላ ገመዳ ስለሕጋዊነቱ በድፍረት የደሰኮረለት የማስተር ፕላኑ ጥያቄ በኃይል መጨፍለቅም በገዥው በኩል ሕገ-መንግስቱ አፈር ለብሶ እንዳበቃለት ተናግሮ አልፏል፡፡በተጓዳኝ የክልሉ ነዋሪ በተፈጥሮ ሀብቱ ተጠቃሚ እንዳይሆንና ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል እንዳይኖር ከመደረጉ ባሻገር፤ ከሕዝቡ ቁጥር ብዛት አኳያ ኦሮምኛ በሁለተኛ ብሔራዊ የሥራ ቋንቋነት እንዲያገለግል ኦህዴድ ተፅእኖ የሚፈጥር አልሆነም፤ ሌላው ቀርቶ ጥያቄውን በሰላማዊ መንገድ ያነሱ ፖለቲከኞች ‹‹ኦነግ›› ተብለው የምድር ፍዳቸውን ሲቀበሉ የታደጋቸው የለም፡፡ የዚህ እኩይ ድርጊት ተጠያቂም ጉልበተኛው ህወሓት ብቻ ነው ማለት ገራገርነት ይመስለኛል፤ የገዛ ወገኑን አሳልፎ የሰጠው ኦህዴድም ጭምር የድርሻውን መውሰዱ አይቀሬ ነውና፡፡ ይህም ሆኖ ከአንዳንድ ምልክቶች በመነሳት ጥያቄዎቹ መልስ እስካላገኙ ድረስ፣ የቱንም ያህል የእስር ቤት ደጃፎች ከዚህም በላይ ቢጨናነቁ፣ የቱንም ያህል የእስረኞቹ ሰቆቃ እያደር ቢበረታ ከእንግዲህ በኦሮሚያ ምድር በፍርሃት ዝም-ጭጭ ብሎ የሚተኛ ሊኖር እንደማይችል ዛሬ ላይ ቆሞ መናገሩ ‹‹ሟርተኛ›› አያስብልም፡፡
የኦሮምኛ ተናጋሪውን ያደረ ቅራኔ በመፍታት የአንድነት ዘብ ለማድረግ፣ የሀገሪቱ ታሪክ እና ባሕል በዳግም ብያኔ መታደሱ ግድ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የክልሉ ማሕበረሰብ በዘመናዊው መንግስት ምስረታም ሆነ ከባእድ ወረራ መታደጉ ላይ ታላቅ አበርክቶ ቢኖረውም፣ በሀገሪቷ ታሪክ ውስጥ ሚናው ደብዝዞ መገለፁ ጎምዛዛ እውነት ነው፤ የቋንቋው ተናጋሪ ያልሆነው አብዛኛው ኢትዮጵያዊም ይህንን አምኖ ሊያርመው ቀርቶ፣ እውቅና ሊሰጠው እንኳ አለመፍቀዱ፣ ጉዳዩን ወደሰሞነኛው ‹‹ውጡ ከሀገራችን›› አይነቱ አስደንጋጭ ኩነት ገፍቶታል፡፡ ከዚህ በተቃራኒው በጥቂት የብሔሩ ልሂቃን የሚንፀባረቀው (ሀገርን ለፍርሰት ሊያጋልጥ የሚችለው) ሸውራራ የታሪክ አረዳድን እና የቅኝ አገዛዝ ትርክትን ማጥራት ሌላው ወሳኝ የቤት ሥራ ሆኗል፤ ምክንያቱም ከጥያቄው ጋር ተያይዘው የሚነሱ የተቃውሞ ድምፆች ማጠንጠኛ ‹ባሳለፍነው መቶ ዓመት ለቅኝ አገዛዝ ተዳርገናል፣ ሥርዓታዊ በሆነ መዋቅር የሥልጣን ባይተዋር ሆነን ቆይተናል፣ ከሌላው ሕዝብም በተለየ መልኩ ከሰብአዊ ፍጡር በታች ተቆጠረን ተረግጠናል…› የሚል መንፈስ እንዲይዝ እየተለጠጠ ነው፡፡ ይህ የታሪክ ትንተና ስሁት መሆኑን የምንረዳው በየትኛውም መንግስታዊ ሥልጣን ጊዜ (ሀገሪቱ በጦር መሪዎችም ሆነ በነገሥታቱ ጠንካራ መዳፍ ስር በተያዘችበት ዘመን) በግንባር ቀደምትነት በመንበሩ ላይ ይፈራረቁ ከነበሩት አማርኛና ትግርኛ ተናጋሪዎች የማይተናነስ እኩል ሚና እንደነበራቸው የቋንቋው ተናጋሪ ምሁራን በማስረጃ አስደግፈው ባዘጋጇቸው ድርሳኖቻቸው ያተቱትን ስናስተውል ነው፡፡
ለማሳያም ‹‹የጎንደር ዘመን›› ተብሎ ከሚጠቀሰው (እ.ኤ.አ ከ1636-1769 ዓ.ም ድረስ የዘለቀው) ማዕከላዊ መንግስት ውድቀት በኋላ የተተካውና ‹‹ዘመነ መሳፍንት›› እየተባለ የሚጠራው አገራዊ የአስተዳደር ዘይቤ ጠንሳሽና ተግባሪ የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች እንደነበሩ ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በወቅቱ የመንግስቱ መቀመጫ ከሰሜን ጎንደር ወደ ደብረታቦር የተዘዋወረ ሲሆን፣ የግዛት ወሰኑ ደግሞ ጎንደርን፣ ወሎን፣ ጎጃምን፣ ከፊል ሸዋንና ትግራይን የሚያካትት እንደነበር መዛግብቱ ያወሳሉ፡፡ በዘመኑ ሥልጣኑን የጠቀለሉትና ‹‹የጁ (ወራ-ሼክ) ስርወ-መንግስት›› በሚል ስም የሚጠሩት የአሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች እንደነበሩ የብሔሩ ምሁራን ነግረውናል፡፡ እያገባደድነው ባለው በዚህ ዓመት ‹‹የውገና ድርሰቶችና የታሪክ እውነቶች›› በሚል ርዕስ ዳጎስ ያለ ጥራዝ ያሳተሙት ታቦር ዋሚ ‹‹በኢትዮጵያ ታሪክ ዘገባዎች አላግባብ ዘመነ መሳፍንት ሲባል የቆየው የየጁ ዘመንና ታሪካዊ ሚና›› በሚለው ንዑስ ርዕስ ሥር በርካታ መጽሐፍትና የጥናት ጽሑፎችን በመጥቀስ ሥልጣኑ በኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች እጅ እንደነበረ በስፋት አብራርተዋል፡፡ ታቦር በትርክታቸው ‹‹የጁ ከሰሜን ኢትዮጵያ የኦሮሞ ነገዶች አንዱ እንደሆነና ቀስ በቀስም ይህ ስም የጎሳው ብቻ ሳይሆን ሕዝቡ የሰፈረበት አካባቢ ጭምር መጠሪያ እንደሆነ በርካታ ጸሐፍት ይመሰክራሉ›› (ገፅ 287) ሲሉ በአባሪ ማስረጃዎች አስደግፈው አቅርበዋል፡፡ ሥርወ-መንግስቱ በሥልጣን ላይ የቆየበት ጊዜያትንም ‹‹ከጎንደር ዘመነ-መንግስት ማብቂያ እስከ አፄ ቴዎድሮስ መነሳት ድረስ የነበሩትን ዓመታት ሁሉ ያካትታል›› (ገፅ 293) በማለት ገልፀውታል፤ ይህንን በአሃዝ እናስቀምጠው ብንል ደግሞ ወደ 86 ዓመት ገደማ ልንቆጥር እንገደዳለን፡፡
በተመሳሳይ መልኩ ‹‹የኦሮሞ ታሪክ›› የተሰኘው መጽሐፍ ጸሐፊ እሸቱ ኢረና ዲባባም መከራከሪያውን እንዲህ ሲሉ ያጠናክሩታል፡- ‹‹ጎንደር የሃበሻ መንግስት (አቢሲኒያ) ማዕከል በነበረችበት ወቅት የኦሮሞ ህዝብ በአካባቢው ሰፍሮ ይኖር እንደነበረና ወሳኝ ሚና ለረጅም ጊዜ ነበረው፤ እ.ኤ.አ. ከ1853-1854 በጎንደር በእስር ላይ የነበረው ጀርመናዊ ሰዓሊ በሰራቸው ምስሎች ኦሮሞ በወቅቱ በአካባቢው ገዢ እንደነበር እርሱም ከአካባቢው ኦሮሞ ሴት እንዳገባ፤ ምስልዋንም ሰርቶ እነዚህ የስዕል ስራዎቹ እ.ኤ.አ. በ1868 ዓ.ም በለንደን ከተማ በመጽሐፍ መልክ ታትሞ ወጥቶ ይገኛል፡፡ በአካባቢው ሰፍረው ይኖሩ ከነበሩት የኦሮሞ ጎሳዎች ውስጥ የቦረና ኦሮሞ አንዱ መሆኑን ኤች ሙሬይ በ1830ዎቹ ባሳተመው ጽሑፍ ውስጥ ከጠቀሰ በኋላ ኦሮሞ እንደ ሕዝብ በደንቢያ በጎጃም፣ በዳሞትና በአንጎት አካባቢዎች ሰፍሮ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡›› (ገፅ 83-84)
ራሱ የክልሉ መንግስትም፣ በባሕልና ቱሪዝም ቢሮው በኩል ‹‹የኦሮሞ ታሪክ እስከ አስራ ስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን›› በሚል ርዕስ ባሳተመው መጽሐፍ ‹‹…‹ወራ-ሼክ› የሚለው የቤተሰቡ መጠሪያ በየጁ ኦሮሞዎች ዘንድ ታላቅ ዝና ከማግኘቱም በላይ በአጠቃላይ የየጁ ኦሮሞዎች ቀደምት መንግስት መነሻ ወይም አባት ተደርጎ እስከመቆጠር ደረሰ ይባላል›› (ገፅ 281) ሲል ገልጿል፡፡
በግልባጩ የአፄ ምኒሊክ ፈረስ ሐረርና አርሲ መርገጡን ‹‹የቅኝ-ግዛት ወረራ›› አድርገው የሚያቀርቡ ዘመነኛ ‹‹ፖለቲከኞች››፣ ይህ አይነቱን ጥሬ ሀቅ ለመቀበል ቀርቶ ለመስማት አይፈቅዱም፡፡ የጠቀስኳቸው ድርሳናትም የሚነግሩን ኦሮሞ ከሌላው ብሔር ጋር ትንቅንቅ ገጥሞ በለስ ቀንቶት ድል ባደረገ ቁጥር መንግስታዊ ሥልጣን መጠቅለሉን ብቻ አይደለም፤ በሀገሪቱ ታሪክ ጭቆና እንጂ ቅኝ አገዛዝ የሚባል ነገር አለመኖሩንም ጭምር ነው፡፡ ከኤርትራ እስከ ሞያሌ፤ ከጋምቤላ እስከ ሶማሌ በተዘረጋው ሰፊ የኢትዮጵያ ግዛት ላይ በተደጋጋሚ ከተቃጡ የባዕዳን ወረራዎች በቀር፣ ቅኝ-ገዢም ሆነ ቅኝ-ተገዢዎች ስለመኖራቸው የሚያትት አንድም የታሪክ መረጃ ተፈልጎ ታጥቷል፡፡ መቼም ‹‹ድሮ ነፃ ሀገር ነበረን›› በሚል ዛሬ ላይ የመገንጠልን ጥያቄ ሲያነሱ፤ አሊያም አንድ ብሔርን በነፍጠኛነትና በወራሪነት ሲኮንኑ የምናደምጣቸው ጠርዘኛ ልሂቃን ‹የኦሮሚያ የግዛት ወሰን ጎንደርን እና ትግራይን ያጠቃልል ነበር› ስለማለታቸው ሰምተን አናውቅም፡፡ መቀመጫውን ደብረታቦር ላይ አድርጎ ከትግራይ እስከ ሸዋ ያስተዳድር የነበረ ሥርወ-መንግስት፣ የበለጠ ጉልበተኛ ተነስቶበት፣ በተራው ከመንበሩ በኃይል ሲገለበጥ ቅኝ-አገዛዝና ኢ-ሰብአዊ ብሎ ለመኮነን መሞከሩ ውሃ የሚያነሳ ሙግት ሊሆን አይችልም፡፡ እዚህ ጋ ሊዘነጋ የማይገባው ጉዳይ፣ በተለይም ከአፄ ምኒሊክ መንገሥ ወዲህ የኦሮሞ ማሕበረሰብ ቋንቋውን ጨምሮ የባሕል እሴቶቹ ተውጠው፣ የአገሪቱ ወካይ እንዳይሆኑ መጨፍለቃቸውን ነው፤ እንደምሳሌም የገዳ ሥርዓት ምንም እንኳ ሁሉንም የቋንቋው ተናጋሪ ያቀፈ ባይሆንም (የ‹‹ጊቤ ግዛት›› ተብለው የሚታወቁት፡- ጅማ፣ ሊሙ፣ ጎማ፣ ጉማ እና ጌራ ከገዳ ይልቅ በንጉሣዊ ሥርዓት ሲተዳደሩ፤ ወለጋና ኢሊባቡርን የመሳሰሉ አካባቢዎችም በ‹‹ሞቲ›› ይመሩ ስለነበር) የአክሱም ሐውልትን ወይም የጎንደር ግንብን ያህል በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ቦታ አለማግኘቱ አይካድም፡፡ እንዲሁም በሌላ ቋንቋ ተናጋሪው ዘንድ ‹‹ጣኦት ማምለክ›› ተደርጎ የሚቆጠረው የኢሬቻ ክብረ-በዓል አረዳድ ስሁት ስለመሆኑ ቢረፍድም የመስከሩ ጠቀሜታ የጎላ ነው፡፡ ይህ የምስጋና ሥነ-ስርዓት በአገሪቱ ታሪክ ተገቢውን የክብር ስፍራ ሳያገኝ መገፋቱን በማመን፣ ሚዛንን ማስተካከል ግድ ይላል፡፡ በጥቅሉ ምግቡ፣ አለባበሱ፣ ሙዚቃውና መሰል እሴቶቹ በትልቁ የታሪካችን ገፅ በበቂ ደረጃ አለመወከላቸውን ዛሬም ለማድበስበስ መሞከሩ መፍትሔውን ከማራቅ፤ አሊያም ልዩነትን ከማስፋት ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም፡፡ መቼም በዛሬይቱ ኢትዮጵያ፣ የመገንጠል ጥያቄ ያነሱ ቡድኖች መኖራቸው ደብቀን የምናስቀረው ሚስጥር አይደለም፤ ከኦሮሚያ እስኪ ኦጋዴን፤ ከጋምቤላ እስከ ቤንሻንጉል ድረስ ይህን ለማስፈፀም የሚተጉ የታጠቁ ኃይሎች ተፈጥረዋልና፡፡ በርግጥ እነዚህ ኃይሎች የቆሙበት መሰረት ማሕበረሰቡን የሚወክል ነው ወይስ የራሳቸውን የሥልጣን ጥማት ብቻ የሚያረካ? የሚለው ገና ያልጠራ፣ አሁንም አጥጋቢ መልስ ያላገኘ ጥያቄ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ፖለቲካዊው ፍላጎት ማሕበራዊ ውሉን የዋጠው ይመስላል፡፡ ኤርትራን ያጣንበት ምክንያትም ከዚህ ብዙም እንደማይርቅ ጥርጥር የለውም፡፡ አሁንም የዚህን ጥያቄ ውል ከሳትን ሌላ የምናጣው ክፍለ-አካል መኖሩ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህም ነው በ‹‹ሕዳሴው አብዮት›› እንደ አዲስ በምትገነባው ኢትዮጵያችን ጥያቄዎቹ በቀዳሚነት ምላሽ ሊያገኙ ይገባል ብዬ የምከራከረው፡፡ በለውጡም፣ እነዚህ ጎታች የፖለቲካ አቋሞች እና አቀንቃኞቹ ዘላቂ መፍትሔ አግኝተው የአንድነት ዘመን አብሳሪ እንደሚሆኑ አልጠራጠርም፡፡
በተቀረ በኦሮሞ ላይ አንድ ብሔር በተለየ መልኩ በደል አድርሷል፣ ዘግናኝ ጭፍጨፋ ፈፅሟል… መሰል ትርክቶች ጭራና ቀንድ ተሰክቶባቸው ግብረ-ሂትለርና ፋሽስታዊ ድርጊቶች ተመስለው የሚቀርቡበት አውድ ከተራ ጊዜያዊ የፖለቲካ ፕሮፓጋንዳነት ያለፈ፣ በዕውን ለመፈፀማቸው ምንም አይነት የታሪክ ሰነድ አልተገኘም፡፡ ከጥቂት ሳምንት ቀደም ብሎ በዚህ ርዕሰ-ጉዳይ ዙሪያ ከታሪክ ምሁሩ ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ጋር ስንወያይ ‹‹ወደ አኖሌ (አርሲ) ከዘመተው የአፄ ምኒሊክ ሠራዊት መካከል አብላጫው ኦሮሞ ነው›› ሲሉ መግለፃቸውም፣ ከዶ/ሩ የትምህርት ደረጃ፣ ከረዥም ዓመት የሥራ ልምዳቸው እና ከቋንቋው ተናጋሪ አብራክ የተገኙ ከመሆናቸው አኳያ ችግሩን ወደ አንድ ብሔር ማላከኩ ስህተት ለመሆኑ ሁሉንም የሚያስማማ ይመስለኛል፡፡ ታቦር ዋሚም ከላይ በጠቀስኩት መጽሐፍ (ከገፅ 275-278) ከአማራው ነገስታቶች ጋር ጋብቻ የፈፀሙ ኦሮሞ ንጉስና ንግስት በማለት በስዕላዊ መግለጫ አስደግፈው ያቀረቡት የቋንቋው ተናጋሪ ንጉሦችና ነገስታት ስም ዝርዝር እንደተጨማሪ ማስረጃ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ጸሐፊው ለማሳያነት ከጠቀሷቸው ውስጥ የአፄ ቴዎድሮስ-እቴጌ ተዋበች፣ የአፄ ምኒሊክ-ጣይቱ ብጡል፣ የንግስት ዘውዲቱ-ወሌ ብጡል፣ የአፄ ኃይለስላሴ-እቴጌ መነን፣ የምኒልክን እህት ያገቡት-ንጉስ ሚካኤል… የኦሮሞ ብሔረሰብ አባላት እንደነበሩ አትተዋል፡፡ ከዚሁ ጋርም አያይዘው በተለያየ ጊዜ በሀገሪቷ የተከሰቱት የኃይል ግጭቶች አሰላለፍ በብሔር ከመቧደን ይልቅ፣ በሥልጣንና በጥቅመኝነት ላይ የተመሰረቱ እንደነበረ ፈራ-ተባ እያሉም ቢሆን እንዲህ ሲሉ ገልፀውታል፡-
‹‹በጣም የሚገርመው ከሣህለ ሥላሴ ጊዜ ጀምሮ እስከ አፄ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት ድረስ በኦሮሞው ላይ ሲካሄዱ ለነበሩት ዘመቻዎች ሁሉ ግንባር ቀደም ተዋናዮቹ በተለያዩ ምክንያቶች ከነገሥታቶቹ ጋር ጊዜያዊና ዘላቂ ዝምድና የፈጠሩ እራሳቸው ኦሮሞዎች መሆናቸው ነው፡፡ …(ራስ ጎበና) እኚህ የኦሮሞ መስፍን የታወቁ ፈረሰኛ፣ ጀግና፣ ተዋጊና ወታደራዊ ስትራቴጂስት ከመሆናቸው በላይ በኦሮሞ የውጊያ ስልትና በኦሮሞ ሥነ-ልቡና ላይ የጠለቀ እውቀት ነበራቸው፡፡ ይህንን ብቃት ሙሉ በሙሉ ለምኒሊክ አገልግሎት አውለውታል፡፡ ከሁሉም በፊት ምኒልክ ሳይሆኑ የኦሮሞን ግዛት ያሸነፉት ራስ ጎበና ነበሩ፡፡›› (ገፅ 499-500 እና 503)፡፡
ይህን መሰሉ የኃይል ትንቅንቅ ከአርሲና ባሌ በፊት ቤጌምድርና ትግራይ ውስጥ በተከሰተበት ወቅት ኦሮምኛ ተናጋሪው በአሸናፊነት በመውጣቱ ለ86 ዓመት ያህል ሥልጣን ይዞ መቆየቱን ከላይ አይተናል፡፡ መቼም የጁዎች፣ ጎንደሮችን ድል አድርገው ሥርወ-መንግስታቸውን ደብረ ታቦር ላይ የመሰረቱት በምርጫ ካርድ (ያለነፍጥ) ነበር ካልተባለ በቀር፣ አንዱን ወገን ለይቶ በሂትለርነት መኮነኑ ፍትሃዊ ካለመሆኑም ባለፈ፤ የሚጠቅመው ከመከራ ነፃ እንዲወጣ የምንዋትትለትን ሕዝብ ሳይሆን፣ የአገዛዙን ዕድሜ ለማራዘም ነው፡፡ በተጨማሪም በራሱ በቋንቋው ተናጋሪዎች ብቻ ከተዘጋጁ ድርሳናት የጠቀስኳቸው እነዚህ ሁነቶች፣ በማስረጃ ያልተደገፈውን (አፈ-ታሪኩን) የአኖሌ ጡት ቆረጣ ትርክት ተአማኒነት ያሳጡታል፡፡ ከዚህ ባለፈ የተሸነፈ ሠራዊትን እጅ-እግር መቁረጥ ምኒሊክም ሆኑ ከእርሳቸው በፊት የነበሩ ገዥዎች ይፈፅሙት የነበረ ጭካኔ መሆኑ አይስተባበልም፤ እንዲያውም በአንድ ወቅት አፄ ቴዎድሮስ፣ በሸዋ ላይ ሾመውት የነበረው የምኒሊክ አጎት አቤቶ ሠይፈ ‹‹ሸፍቶብኛል›› በሚል አንኮበር ድረስ መጥተው ወግተው ድል ካደረጉት በኋላ ሠራዊቱ በሙሉ አንድ እጅና አንድ እግሩ እንዲቆረጥ ማድረጋቸውን ተከትሎ፡-
“አፄ ቴዎድሮስ እጅግ ተዋረዱ
የሸዋን ሰው ሁሉ እጅ ነስተው ሄዱ”
ተብሎ መገጠሙ የጉዳዩን እውነታነት ለማሳየት በቂ ነው፡፡
(የእስልምና እምነት እና የኦሮምኛ ተናጋሪው ማሕበረሰብ ጥያቄዎች፣ በ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› የሚኖራቸውን የመፍትሔ ሃሳብ በተመለከተ ሳምንት እመለስበታለሁ)

mandag 28. juli 2014

የኢድ አልፈጥር በዓል በመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ተከበሮዋለ።

1 ሺህ 435ኛው የኢድ አልፈጥር በመላው የእስልምና ተከታዮች ዘንድ እየተከበረ ነው። በአዲስ አበባ ስታዲየም የነበረው
ክብረበአል በሰላም የተጠናቀቀ ሲሆን፣ ድምጻችን ይሰማ ምንም አይነት ተቃውሞ እንዳይካሄድ ባዘዘው መሰረት፣ በአዲስ አበባ ስታዲዮም ተቃውሞ ሳይካሄድ ቀርቷል።
የኢህአዴግ የጸጥታ ሃይሎች ሰሞኑን በወሰዱት ጠንካራ እርምጃ በርካታ ሙስሊሞች የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፣ ቁጥራቸው በውል ያልተወቀ ሙስሊም ዜጎች
በእስር ቤት እየማቀቁ ይገኛሉ።
በኢድ አል ፈጥር ላይ ተቃውሞ ከተነሳ የኢህአዴግ ደህንነቶች እርምጃ ለመውሰድ ተዘጋጅተው እንደነበር መዘገቡ ይታወሳል።
ልቁማን የኢትዮጵያ ቤልጂየም  የሙስሊም ማህበር ( ልብማ) ለኢሳት በላከው መግለጫ መንግስት ባለፈው አርብ በሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ የወሰደውን
እርምጃ አውግዟል።
ማህበሩ በመግለጫው ህዝበ ሙስሊሙ ላነሳቸው የመብት ጥያቄዎች የመንግስት ምላሽ ግድያ፣ ድብደባ፣ እስራትና ንቀት መሆኑን አስታውሷል። የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ
አባላትን ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ መታሰራቸውን፣ ብዙ ንጹህ ሙስሊሞች መገደላቸውን፣ አንዳንዶች አገር ጥለው መሰደዳቸውን እንዲሁም ሌሎች አካል ጉዳተኞች ቆነው
መቀመጣቸውን ጠቅሷል።
የሙስሊሙ ማህበረሰብ ትግሉን ከመቀጠል ውጭ ሌላ አማራጭ እንደሌለው ልብማ ጠቅሶ፣ ድምጻችን ይስማ በኢትዮ-ቴልኮ ላይ የጣለውን የአንድ ቀን ማእቀብም በማድነቅ ተመሳሳይ
አርምጃዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቋል። በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ከሙስሊሞች ጎን እንዲቆሙ፣ መላው የኢትየጵያ ህዝብም በሚወሰዱት እርምጃዎች ተባባሪ እንዲሆን ማህበሩ ጥሪ አቅርቧል።

ተላላኪው ማን ነው? ታማኝ በየነ ጥያቄውን በማስረጃ ይተነትናል

ተላላኪው ማን ነው? ታማኝ በየነ ጥያቄውን በማስረጃ ይተነትናል።
ታማኝ በየነ ከሲሳይ አጌባ ጋር ያደረገውን ውይይት ይመልከቱ::

ሕወሓት አቶ አንዳርጋቸውን በቲቪ ስታቀርብ ራሷን በራሷ ያጋለጠችባቸው 4 ቅጥፈቶች

ስንታየሁ ከሚኒሶታ
እንደተጠበቀው በሕወሓት መንግስት በሚመራው የኢትዮጵያ ፖሊስ ፕሮግራም ላይ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲቀርቡ ተደርጓል። የአቶ አንዳርጋቸው በቲቪ መቅረብ ከዚህ ቀደም በአንዷለም አራጌ፣ በብርቱካን ሚደቅሳ፣ በደበበ እሸቱ፣ በአቡበከር አህመድ ላይ የተለመደ በመሆኑ ብዙም አስገራሚ አልሆነም። ሆኖም ግን ቪድዮውን ልብ ብሎ ለተመለከተው ወያኔ እንዳሰበው ትርፍ ሳይሆን የበለጠ ኪሳራ እንዳገኘበት ለመረዳት ችያለሁ። ለዚህም ነው ወያኔ አቶ አንዳርጋቸውን በቲቪ ስታቀርብ የረሳቻቸው 4 ቅጥፈቶች ስል ለዚህ አስተያየቴ ር ዕስ የሰጠሁት።
ወያኔ አቶ አንዳርጋቸውን በቲቪ ስታቀርብ ራሷን በራሷ ያጋለጠችባቸው 4 ቅጥፈቶች1ኛ. ቪድዮው በጣም ኤዲት እንደተደረገ ያስታውቃል
ሕወሓት ያዘጋጀው የቪድዮ ካሜራ ማንና አቀናባሪው ደንጋጣ እንደሆነ ቪድዮው ያስታውቅበታል። በጣም ተቆራርጦ መቀጣጠሉ ከማስታወቁም በላይ ቢያንስ ከዚህ የተሻለ ኤዲቲንግ ሥራ መሥራት ይችል የነበረ ቢሆንም ይህን ባለማድረጉ ለፕሮፓጋንዳ ሥራ የተዘጋጀውን ቪድዮ ኪሳራ ላይ ጥሎታል። ቪድዮ አቀናባሪው ሆን ብሎ ሕዝብ መቆራረጡን እንዲያውቅ ያደረገ ከሆነ ልናደንቀው የሚገባ ሲሆን፤ ሆኖም ግን ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ከሆነ ይህ ቪድዮ ቅንብሩ አይመጥንም።
2ኛ. ቪድዮው በተደጋጋሚ የተቀረጸ መሆኑ ያስታውቃል።
ቪድዮውን ልብ ብላችሁ ከተመለከታችሁት በተለያየ ጊዜ የተቀረጸ መሆኑ ያስታውቃል። ይህም የሚፈልጉትን ለማግኘት ብዙ ማይል እንደተጓዙ ያሳያል። ምንም እንኳ ተመሳሳይ ቀን የተቀረጸ ለማስመሰል አንድ ዓይነት ቱታ ቢያስለብሱትም 3 የተለያዩ የውስጥ ቲሸርቶች ይታያሉ። አንዱ ነጭ፣ ሌላኛው ሰማያዊና 3ኛው ቀይ ቲሸርቶች። በሌላ በኩል ቪድዮው ሊያልቅ ሲል የምታዩት ቱታ ደግሞ የተለየ ነው።
3ኛ. ውሃዋ የለችም።
እንግዲህ ወያኔ ሌላው የረሳችው አቶ አንዳርጋቸውን በጥሩ ሁኔታ እንዳሉ ለስመሰልና ንጹህና የተገዛ ውሃ አጠገባቸው አስቀምጣ ነበር። ቪድዮው ግን በተለያየ ጊዜ የተቀረጸ ለመሆኑ የሚያስታውቀው በሌላኛው የቪድዮ ክፍል ውስጥ ውሃዋ የለችም።
4ኛ. ቶርች የሚደረግ ሰው እንዳለ ይሰማል
ይሄ ትልቁ ወያኔን ራሱን በራሱ ያጋለጠበት ክፍል ነው። ቪድዮው ተጀምሮ ከ1 ደቂቃ በኋላ ያለውን ስትመለከቱት አንዳርጋቸው በሚናገርበት ወቅት ከጀርባው የድብደባና የሲቃ ድምጽ ይሰማል። ይህም ምን ያህን በወያኔ እስር ቤቶች የሚደረጉትን ቶርቸሮች የሚያሳይ ነው። ይህ ለወያኔ ትልቁ ኪሳራ ሊባል የሚችል ደካማው የፕሮፓጋንዳ ቪድዮው ሊባል ይችላል። ራሱን በራሱ ቶርቸር አድራጊ መሆኑን መስክሯልና ይህንን የሚመለከታቸው አካላት ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተከራካሪ ድርጅቶች ማሳየት ይኖርባቸዋል፤ አንዳርጋቸውም እንዲህ ያለው ቶርቸር እንደደረሰበት ማሳያ ሊሆነን ይችላል እላለሁ።
ቪድዮውን ተመልከቱትና ፍረዱ። በመጨረሻም ለወያኔ የማስተላልፈው መል ዕክት አለኝ – እንደሁልጊዜው ለዛሬውም አልተሳካም!

fredag 25. juli 2014

ሠማያዊ ፓርቲና ሕገ መንግሥት


የፓርቲዉ መሪዎች ዛሬ ለጋዘጠኞች በሠጡት መግለጫ እንዳሉት ማሻሻዉ በቋንቋ ላይ የተመሠረተ የክፍለ ሐገር አከላላል እንዲቀር፤ መሬት በግል እንዲያዝና ብሕራዊ ቋንቋ እንዲኖር የሚጠይቁ ሐሳቦች ተካተዉበታል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚ የፖለቲካ ማሕበር ሠማያዊ ፓርቲ አሁን የሚሠራበት የሐገሪቱ ሕገ-መንግሥት ሊያካትታቸዉ ይገባል ያላቸዉን የማሻሻያ ሐሳቦች በይፋ አስታወቀ።የፓርቲዉ መሪዎች ዛሬ ለጋዘጠኞች በሠጡት መግለጫ እንዳሉት ማሻሻዉ በቋንቋ ላይ የተመሠረተ የክፍለ ሐገር አከላላል እንዲቀር፤ መሬት በግል እንዲያዝና ብሕራዊ ቋንቋ እንዲኖር የሚጠይቁ ሐሳቦች ተካተዉበታል።ሠማያዊ ፓርቲ «የዜጎች ቃል ኪዳን ለዲሚክራሲያዊት ኢትዮጵያ» ያለዉን የማሻሻያ ሰነድ ለሕዝብ ዉይይት እንደሚያቀርብም ባለሥልጣናቱ አስታዉቀዋል።

torsdag 24. juli 2014

የፖሊስ ሃላፊዎች ጥያቄዎችን አነሱ

በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ስር በየደረጃው የሚገኙ የፖሊስ ሃላፊዎች ካለፈው አንድ ወር ጀምሮ በሰንዳፋ እና በኮልፌ ፖሊስ ማሰልጠኛዎች
ከደህንነት ጋር በተያያዘ ስልጠና እየተሰጣቸው ሲሆን፣ የሰልጠና ተሳታፊዎች የሚያነሱዋቸውን  ጥያቄዎችን አሰልጣኞች መመለስ አለመቻላቸውን በስልጠናው ላይ የሚሳተፉ ፖሊሶች ለኢሳት ገልጸዋል።
ፖሊሶቹ ” መንግስትበተለይከሙስሊምሃይማኖትተከታዮችየሚነሳውንዲሞክራሲያዊየሆነጥያቄለምንአይመልስም?  ለምን በፖሊስተቋምላይየስራጫናእንዲበዛ ይደረጋል?ህዝቡበፖሊስላይያለውጥላቻ
ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል፣እኛህብረተሰቡን በተገቢውመንገድማገልገልእንፈልጋለንና አስተዳዳራዊ ሁኔታዎች ይለወጡ” የሚሉ ጥያቄዎች ቀርበዋል። አሰልጣኞቹ የሚቀርቡት ጥያቄዎች ከአቅማቸው በላይ
መሆኑንና የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣኖች የሚመልሱዋቸው እንደሆነ እየገለጹ ነው። በሚሰጠው መልስ ደስተኛ ያልሆኑት ፖሊሶች፣ ትክክለኛውን መልስ የሚሰጠው አካል ይመጣል ብለው ቢጠባበቁም
እስካሁን ድረስ አርኪ መልስ የሚሰጥ ባለስልጣን አላገኙም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከፌደራልጉዳዮችናኢህአዴግጽ/ቤትበተላለፈትዕዛዝመሰረትበአዲስአበባበሁሉምክ/ከተማዎችናበ116 ወረዳዎችየሚኖሩሙስሊምኢትዮጵያውያንንለማደንእንቅስቃሴ
እንዲጀመር ትእዛዝ መሰጠቱ ታውቋል።ትእዛዙየተሰጠውለሁሉምከፌደራልእስከወረዳድረስለሚሰሩየኢሀአዴግአባላትሲሆንየጽ/ቤትሃላፊዎችበየጽ/ቤታቸውየሚገኙአባላትንበመጥራት
ስለወጣው ትእዛዝ ገልጸውላቸዋል፡፡  የቀበሌመታወቂያየሌለውሙስሊምታፍሶእንዲታሰርናወደመጣበትአካባቢእንዲሸኝይደረጋል፡፡
ይህንንልዩተልዕኮየሚመሩትበየክ/ከተማውናበየወረዳውየሚሰሩበጥቅምየተሳሰሩሙስሊሞችናቸው ሲሉ ምንጮች አክለዋል፡፡  ባለፉት 3 ቀናት የተለያዩ የደህንነት አባላት በሚያውቁዋቸው
ሙስሊሞች ዘንድ በመደወል ለማስፈራራት መሞከራቸውን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።
ባለፈው አርብ ኢህአዴግ የጸጥታ ሃይሎች በረመዳን ጾም ላይ በሚገኙት ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ የወሰዱት እርምጃ ጥቁር ሽብር ተብሎ መሰየሙ ይታወቃል። ኢህአዴግ የጸጥታ ሃይሎች በቀሰቀሱት
ግጭት በርካታ ሙስሊሞች ተደብድበው ሆስፒታል የገቡ ሲሆን፣ በብዙ መቶወች የሚቆጠሩት ደግሞ ታስረው ከፍተኛ የሆነ ስቃይ ከደረሰባቸው በሁዋላ ብዙዎቹ ተለቀዋል፡፡ በተለይ በሴቶች  ላይ የተወሰደው
እርምጃ አስከፊ እንደነበር የሚወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ።

የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በአቶ አንዳርጋቸው ዙሪያ የሰጠው መልስ የእንግሊዝ የፓርላማ አባላትን አስገረመ

በእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ እና የጋራ ብልጽግና መስሪያ ቤት ዋና ጸሃፊ የሆኑት ማርክ ሲሞንድ  የግንቦት7 ዋና ጸሃፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣
ከእንግሊዝ መንግስት የኮንሱላር ምክር የሚያገኙበት ሁኔታ እንዲመቻች የሚጠይቅ ደብዳቤ ለንደን ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ ጽፈዋል። ለንደን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ በሰጠው መልስ፣
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በኢትዮጵያ ፓርላማ አሸባሪ የተባለ ድርጅት መሪ መሆናቸውን ገልጾ፣ አሸባሪ ለመሆናቸው ማሳያ ይሆን ዘንድ ግንቦት7 በቅርቡ ያወጣውን መግለጫ በእንግሊዝኛ ተርጉሞ አያይዞ
አቅርቧል። ግንቦት7 አቶ አንዳርጋቸውን ለማስፈታት በኢትዮጵያ ፣ በየመን እና በእንግሊዝ መንግስታት ላይ ኢትዮጵያውያን መውሰድ ስላለባቸው እርምጃዎች የሚዘረዝር መግለጫ ማውጣቱ ይታወቃል።
በመላው አለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በእንግሊዝ ኢምባሲ ፊት ለፊት በመሄድ ተቃውሞ እንዲያሰሙ፣ ተከታታይ ደብዳቤዎችን እንዲጽፉ የሚጠይቀውን መግለጫ፣ ግንቦት7 አሸባሪ ድርጅት ለመሆኑ
ማሳያ ነው በማለት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የጻፈው ደብዳቤ የፓርላማ አባላቱንና የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሰራተኞችን እንዳስገረማቸው ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ የአቶ አንዳርጋቸው
ቤተሰቦች ገልጸዋል።
የአቶ አንዳርጋቸውን ጉዳይ በቅርብ የሚከታተሉት ሁለቱ የፓርላማ አባላት  ጀርሚ ኮርቢን እና ኤምሊ ቶርንቤሪ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በሰጠው መልስ ከተገረሙት መካከል ሲሆን፣
ባለስልጣኖቹ የእንግሊዝ መንግስት በሂደት ስለሚወስደው እርምጃ እንዲብራራላቸው ደብዳቤ ጽፈዋል። የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ዋና ጸሃፊ፣ አገራቸው በተከታታይ ስለምትወስደው እርምጃ ዝርዝር
መርሃ ግብር እያዘጋጁ መሆኑን ለፓርላማ አባላቱ ገልጿል።
ኢሳት ባለስልጣኖቹ የተጻጻፉዋቸው ደብዳቤዎች ቅጅ የደረሰው ሲሆን፣ ከደብዳቤዎች ለመረዳት እንደሚቻለው፣ መንግስት በአቶ አንዳርጋቸው ላይ የሚያቀርበው የሽብርተኝነት ክስ  ግንቦት 7 መንግስትን
በሃይል አወርዳለሁ ብሎ ማወጁ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ አሁንም የመነጋጋሪያ አጀንዳ እንደሆነ ቀጥሎአል። በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚኖሩ ዜጎች ስልኮችን ለኢሳት በመደወል ለአቶ አንዳርጋቸው ያላቸውን
አክብሮትና መካሄድ ስላለበት ትግል አስተያየቶችን ይሰጣሉ።

onsdag 23. juli 2014

የታሰሩት ሙስሊሞች ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ እየተዘዋወሩ ነው

በጁምዓው ተቃውሞ የተያዙ ንፁሀን ሙስሊሞች ወደ ቂሊንጦ ማረሜያ እየተዘዋወሩ ነው። በማረሜያ ቤቱም ከፍተኛ የሆነ የቦታ እጥረት ተከስቷል።
(ሃይደር አሊ እንደዘገበው)
ጁምዓ በ11/11/2006 በህዝበ ሙስሊሙ ላይ በአንዋር መስጂድ የመንግስት ሀይሎች በወሰዱት ኢ-ሰብዓዊነት የተሞላበት እርምጃ ታስረው ከነበሩ ሙስሊሞች አብዛኛዎቹ ጁምዓ ሌሊቱን ተደብድበውና የተወሰኑት በገንዘብ ዋስ እየተለቀቁ ሲሆን በዕለቱ ተይዘው ከነበረው ሰላማዊ ሙስሊሞች ውስጥ የተወሰኑት ተመርጠው ወደ ቂሊንጦ ማረሜያ ቤት እየተዘዋወሩ እንደሆነና ለእነዚሁ ንፁሀን ወንድምና እህቶቻችን የሚሆን በቂ ቦታ ማረሜያ ቤቱ ስለሌለው የቦታ እጥረት መከሰቱ ታውቋል።
ወደ ቂሊንጦ ማረሜያ ቤት ከተዘዋወሩት ንፁሀን እህትና ወንድሞቻችን መሀከል 40 የሚሆኑት ዞን 2 ውስጥ የገቡ ሲሆን በዞኑ ውስጥ ለገቡት በቂ ቦታ ባለመኖሩ በዞኑ ውስጥ ለአንድ ታራሚ በተዘጋጀው ቦታ ለሁለት እየተኙም ቦታው ሊበቃ ባለመቻሉ መሬት ላይም ጭምር ለመተኛት እየተገደዱና በማረሜያ ቤቱ ውስጥ ያሉ ታራሚዎችን ጨምሮ ለከፍተኛ እንግለት እየተዳረጉ እንደሆነ ታውቋል።
ወደ ዞን ሶስትና አንድ የገቡት ታራሚዎች ቁጥር ለጊዜው ያልታወቀ ሲሆን በዞን ሶስትም ውስጥ ለታራሚ የተዘጋጀው ቦታ ባለመብቃቱ በአንድ መኝታ ላይ ለሁለት እየተኙ እንደሆነ የታወቀ ሲሆን በዞኑ ያሉ ታራሚዎችም ለእንግልት እየተዳረጉ እንደሆነ ታውቋል።
ንፁሀንን ያለ ጥፋታቸው አስሮ ማንገላታቱ ይቁም!

ተስፋለም ወልደየስ፦ “ሚዛን” በሳተበት አገር “ሚዛን” ባለ ብዕሩን የተቀማ ጋዜጠኛ

አሁን በ እስር ላይ ከሚገኙት የዞን ዘጠኝ ጦማርያን እና ጋዜጠኞች መካከል አንዱ ተስፋለም ወልደየስ ነው። ዘሪሁን ተስፋዬ ስለተስፋለም ምስክርነቱን እንዲህ በማለት ይገልጸዋል።
(ከዘሪሁን ተስፋዬ)
ሌሊቱ ሊጋመስ ግማሽ ያህል ሰዓት ቀርቶታል። ወትሮም ዓርብ ምሽት ውክቢያ የማያጣው የአዲስ ነገር ቢሮ በግርግር ተሞልቷል። ጋዜጠኛ ወዲህ ወዲያ ይራወጣል። ቀሪው ኮምፒውተር ላይ አፍጥጦ ዘወትር ለሕትመት ዘግይቶ ለሚገባው ጋዜጣ ጽሑፉን ይተይባል። ጋዜጠኛ ተስፋለምም አንዲት ጥጉን ይዞ ይጫጭራል። ዜናዎች ኤዲት ያደርጋል። እኔም ለመጀመሪያ ጊዜ ይዤ የመጣሁትን ዜና ኤዲት እንዲያደረግ ሰጥቼው፤ ወደጀመርኩት የኢኮኖሚ ጽሑፍ ተመለስኩ። ነገር ግን አፍታም ሳይቆይ በንዴት እየቀዘፈ “አሁን በዚህ ሌሊት ይህ ዜና ተብሎ ይሠራል… ” ተስፋለም ይህን ይህል ግልጽ ነው። ለሞያው የሚቆረቆር። አንዳች ስህተት መስሎ የሚሰማውን ፊት ለፊት ከመናገር የማይቆጠብ።
ያን ሌሊት በብዙ ጭቅጭቅና ንትርክ ዜናው ተሰርቶ ወጣ። አጋጣሚው ግን ልዩነታችን በጋዜጠኝነት ፍልስፍና ላይ እንደሆነ ቁልጭ አድርጎ ያሳየ ነበር። እሱ “ሚዛናዊ” ብሎ የሚሟገትለት ጋዜጠኝነት በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሥራዓት አንዳች የማያራምድ ይልቁንም ጋዜጠኝነትን አሽመድምዶ ልሳን የሚሸብብ መኾኑ ሊያግባባን አልቻለም። እኔ “balanced journalism is a zero-sum game in Ethiopia” ብዬ እሞግተዋለሁ፤ እሱ በየትኛውም የመንግሥት ሥራዓት ቢሆን የጋዜጠኝነት ሕግጋት የማይጣሱ ደንቦች ናቸው ይላል። ይህንንም በሥራው ያሳያል።
Tesfalem woldeyes
Tesfalem woldeyes
ጋዜጠኝነትን ሕይወቱ ያደረገው ተስፋለም፤ በምንም መልኩ ቢሆን ሞያው በትምህርት ቤት ያገኛቸውን የጋዜጠኝነት መርሖዎች እንዲቃረን አይፈልግም። ዜናዎች ሲያዘጋጅ “ሚዛናዊነት” የሚለው መርሕ አለመጣሱን ሲያረጋግጥ ብቻ ነው ወሬው የሕትመት ብርሃን የሚያየው። ይህ ግን በአንዳንድ ባልደረቦቻችን ላይ ጥርጣሬ አልጫረም ማለት አይቻልም። እሱ “ሚዛናዊ” ብሎ የሚጠራው ጋዜጠኝነት፣ ለዘብ የሚል በተለይም አንዳንድ ጠንካራ የሚባሉ ዜናዎችን (በአዲስ ነገር በወቅቱ ዕይታ) አግላይ ነው የሚል ክርክር ይስነሳ ነበር። የዜናዎቹ ‘ሚዛን’ ለመጠበቅ ሲባል ለዘብተኛ መኾናቸው “ተስፍሽ ለመንግሥት ተቆርቋሪነት ያሳያል” የሚል አንድምታ ያለው ጥርጣሬ ማሳደሩ አልቀረም።
ይሁንና በሚያዘጋጃቸው ዜናዎች ተዓማኒነት፣ ጥራት እና ቋንቋ አጠቃቃም ሁሉም የሚያደንቀው ነበር። በተለይ ማህበራዊ ገጾች ላይ የሚወጡ ጽሁፎችን እሱ ሳያይቸው እንዲወጡ የሚፈልግ ጋዜጠኛ አልነበረም። የመተረክ ችሎታው፤ የቋንቋ አጠቃቀሙ እና ዝርዝር ጉዳዮችን የማካተት ብቃቱ ልዩ ነው። ተግባቢነቱና ሁለ ገብነቱም የሞያ መርሕ ልዩነት ቢኖርም በሁሉም ዘንድ በፍቅር እንዲፈለግ አድርጎታል። የማይደክም ነው። የእንቅልፍ ሰዓቱ እጅግ በጣም አነስተኛ መሆኑ እንደ ሰው ቆሞ መሄዱ ሁሌም የሚገርመኝ ነው።
Tesfalem Woldeyes
Tesfalem Woldeyes
ዙረት ይወዳል። በአንድ ሥፍራ መቀመጥ የጋዜጠኛ ተግባር አይደለም ባይ ነው። በመጓዝ ጋዜጠኛ በእውቀት ይበለጽጋል የሚል ዕምነት አለው። ወደ ተለያዩ አገሮች በሚጓዝበት ወቅት ብዙ ጋዜጠኞች የማይሳካላቸውን የጉዞ ማስታዎሻዎችን ማዘጋጀት ላይ የላቀ ብልጫ እንዳለው አሳይቷል። በአንድ ጉዞ ብቻ ለወራት የሚበቃ ታሪክ ይዞ ይመለሳል።
የተስፋለም “ሚዛናዊነት” መርሕ ቢያንስ ቢያንስ ሚዛን የሳቱ አስተዳዳሪዎቻችንን ብትር እንዳይቀምስ ከለላ ይሆነዋል የሚል ዕምነት ነበረኝ። ግምቴ ግን አልሰራም። ሁሌም ጠላት ከጉያው ሥር ካልፈለቀቀ ያስተዳደረ የማይመስለው መንግሥት ተስፋለምን በጠላትነት ፈረጀው። ማዕከላዊ እስር ቤትን ለዜና ሥራ እና እሥረኛ ወዳጆቹን ለመጠየቅ ብቻ የሚሄድበት ጋዜጠኛ፤ አሁን ማደሪያው ኖኗል። እጅግ ልብ የሚሰብር ኢ-ፍትሓዊነት ነው። በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ውስጥ ይሄን ያህል ለሞያ ታማኝ መሆን የሚያስከፍለው ዋጋ እስር እና እንግልት መሆኑ አሳዛኝ ነው።
የተስፋለም እስር ኢ-ፍትሓዊነት ብቻ አይደለም ጸጸት የሚፈጥረው። ብዙዎቻችን የሥራ ባልደረቦቹ ይህንን እውነታውን ሳንረዳ መቅረታችን ነው። ስለዚህች አገር ተስፋ ነበረው። አዎንታዊ ጉዳዮችን ይበልጥ መፃፍ መንግሥትን ከአውሬነት ወደ ሰለጠነ ሰውነት ይገራዋል የሚል ዕምነት ነበረው። እምነቱ ግን ተስፍሽን ዕራሱን አስከፈለው። ሚዛን የሳተኝ አገር ሕሊና ቢሶች አስተዳዳሪዎች ተሸክማ ተስፋለምን ለአውሊያዋ መገበሪያ አደረገችው። ብዕሩን ነጥቃ ከሚወደው ሞያ ለጊዜውም ቢሆን ለየችው።
ተስፋለምን ከሞያ ባሻገርም እንደ ቅርብ ወንድም እናፍቀዋለሁ። ከነልዩነታችን የጥበብ ፍቅር ያስማማናል። ሁለታችንም ዙረት መውደዳችን በተለያየ አጋጣሚ የተለያዩ ሥራዎች እንድንሰራ አድርጎናል። ከሁሉ ግን ዑጋንዳ ለሥራ ለዓመት በቆየበት ጊዜ የመጀመሪያውን በምስራቅ አፍሪካ የሚሰራጭና በአማርኛ የሚታተም “ሐበሻዊ ቃና” የሚል በስደተኞች ላይ የሚያተኩር ጋዜጣ መጀመሩ ይበልጥ እንደወደው አድርጎኛል- ለሞያውም ጥልቅ ፍቅር እንዳለው መስክሮልኛልና።
ተስፍሽን ባልደረቦቹ በወጉ አልተረዳነውም። ፍቅርና አክብሮታችን ግን ሁሌም ነበር። አሁንም ይበልጥ እንድናከብረው ለሚዛናዊነትም የከፈለውን መስዋዕትነት እንድናስበው ሆኖል። ተስፍሽ ሁሌም የምታከብራት ሚዛናዊነት ከግፈኞች አሳሪዎችህ ነጻ በምትወጣ አገራችን ነፍስ ዘርታ እንደምትላወስ አትጠራጠር።

tirsdag 22. juli 2014

ወያኔ በሰሜን ጎንደር የዐማራ ሕዝብ ላይ የፈጸመው የዘር ማጽዳት እና የዘር ማጥፋት ወንጀል – ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት

ዘረኛው የትግሬ-ወያኔ ቡድን በሰሜን ጎንደር የዐማራ ሕዝብ ላይ የፈጸመው የዘር ማጽዳት እና የዘር ማጥፋት ወንጀል
የትግሬ-ወያኔ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት አቅዶ ሲነሳ፣ የግቡ መረማመጃ ያደረገው የኢትዮጵያዊነት መገለጫ የሆኑ ተቋሞችን፣ ኃይማኖቶችን፣ ዕሴቶችን እና በተለይም «ዐማራ» የተሰኘውን ነገድ ተወላጆች ነጥሎ ማጥፋት የሚል ሥልት በመከተል እንደሆነ ይታወቃል። በዚህም መሠረት የጥፋቱ ቅድሚያ ዒላማ ያደረገው ለትግራይ ሕዝብ በችግሩ ጊዜ ደራሽ እና የተራበ አንጀታቸውን ዳሳሽ በሆነው የወልቃይት፣ የጠገዴ፣ የጠለምትና የሠቲት ወረዳዎች ሕዝብ ላይ ነው። ወያኔ በእነዚህ የትግሬ አዋሣኝ ወረዳዎች ሕዝብ ላይ የጥፋት ክንዱን የዘረጋው በሦስት መሠረታዊ ምክንያቶች ነው።
የመጀመሪያውና ታላቁ ምክንያት የእነዚህ ወረዳዎች ሕዝብ ዐማራ በመሆኑ እና የትግራይ አዋሳኝ ስለሆነ የትግራይን ታሪክ ክፉውንም ሆነ ደጉን ጠንቅቆ የሚያውቅ በመሆኑ ነው። በዚህም ምክንያት የዚያ አካባቢ ሕዝብ የትግሬ-ወያኔ ለተነሳለት ፀረ-ኢትዮጵያ እና ፀረ-ዐማራ እንቅስቃሴ የማይተኛ እንደሆነ ስለሚረዳ ይህን ሕዝብ ብቻውን አቁሞ ማጥፋት ለወደፊቱ ግሥጋሴው ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርላቸው በማመን የችግር ጊዜ ደራሻቸውን ሕዝብ ያለርኅራኄ ጨፍጭፈውታል።
ሁለተኛው ምክንያት «ታላቋን ትግራይ» ለመመሥረት ባላቸው ዕቅድ ለውጭ ግንኙነታቸው መውጫ መግቢያ እንዲሆናቸው ከሱዳን ጋር የሚዋሰኑትን እነዚህን ወረዳዎች ወደ ትግራይ ማጠቃለል ስለነበረባቸው ነው። ሆኖም የአካባቢው ሕዝብ «ነገዳችን ዐማራ፣ ጠቅላይ ግዛታችን ጎንደር ነው።» እያለ እንዳያስቸግራቸው በቅድሚያ ነባር ነዋሪውን ጎንደሬ አጥፍቶ በሠፋሪ ትግሬ ማስያዝ ለዓላማቸው ሥምረት ያገለግላል ብለው በማመናቸው ነው።
ሦስተኛው ምክንያት የሠቲት፣ የወልቃይት፣ የጠገዴ፤ እና የጠለምት ወረዳዎች ለሠፋፊ የእርሻ በተለይም ለጥጥ፣ ለሰሊጥ፣ ለማሽላ፤ ለዱር ሙጫ፣ ወዘተርፈ ምርት የሚያመች የለም እና ሠፊ መሬት ባለቤት በመሆኑ ነው። ስለዚህ የእነዚህ የሚያጓጉ የተፈጥሮ ኃብቶች ተጠቃሚ ለመሆን ተቀናቃኙን የጥንት ነዋሪውን ሕዝብ የግድ ማጥፋት አለብን ብለው በማመናቸው ነው።
ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) በዐማራ ነገድ አባሎች ላይ የተቀነባበረ የዘር ማጽዳት ወንጀል መፈጸም የጀመረው ድርጅቱ ገና «ተጋድሎ ሓርነት ሕዝቢ ትግራይ (ተሓሕት)» ተብሎ ይጠራበት ከነበረበረበት የጨቅላነቱ ዘመን ጀምሮ እንደሆነ የድርጅቱ ታሪክ ያስረዳል። በተለይም የትግራይ አዋሣኝ በሆኑት የሰሜን ጎንደር ታሪካዊ አካሎች በነበሩት ወረዳዎች ነዋሪ የሆኑ ዐማራዎችን ለማጥፋት ተሓሕት-ሕወሓት ፕሮግራም ነድፎ መንቀሳቀስ የጀመረው ከ፲፱፻፷፯ ዓ.ም. ጀምሮ እንደሆነ የድርጅቱ ነባር አባሎች ያስረዳሉ። የሰሜን ጎንደር ለም እና ድንግል ወረዳዎች የሚባሉት፦ ወልቃይት፣ ሠቲት፣ ላይ እና ታች አርማጭሆ፣ ጠገዴ እና ጠለምት ናቸው። በሕወሓት ታሪክ ውስጥ «የዲማ ኮንፈረንስ» በመባል የሚታወቀው እና ከ፻፶ (አንድ መቶ ሃምሣ) ያላነሱ አባላቱ ተካፋይ በሆኑበት በየካቲት ወር ፲፱፻፷፰ ዓ.ም. «ጸደቀ» የተባለው ፕሮግራም ወልቃይትን፣ ሠቲት፣ ጠገዴን እና ጠለምትን ከዐማራ በማጽዳት ወረዳዎቹን ወደ ትግራይ መጠቃለል እንዳለባቸው ያስገነዝባል።
ይህ ፕሮግራም ዐማራውን ከማውገዝ አልፎ፣ በትግሬ ደመኛ ጠላትነት በመፈረጅ በግልፅ ቋንቋ «የትግላችን ዓላማ ፀረ-የዐማራ ብሔራዊ ጭቆና ነው» ይላል። ከዚህ በተጨማሪም ፕሮግራሙ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት፣ ብሔራዊ ጥቅም እና የሕዝቧን አንድነት በእጅጉ የሚጎዳ ብቻ ሳይሆን፣ አገሪቱ እንደአገር እንዳትቀጥል የሚያደርግ ዓላማ ያለው መሆኑ በፕሮግራሙ መሠረት ባለፉት ፳፫(ሃያ ሦሥት) ዓመታት በመፈጸም ላይ ያሉት ተግባሮች ሁነኛ እማኖኞችና ነቃሾች ናቸው።
በ፲፱፻፷፰ ዓ.ም. የጸደቀውን የድርጅቱን ፕሮግራም ተግባራዊ ለማድረግ አርከበ ዕቁባይ «ወደ ታላቋ ትግራይ ረፐብሊክ ሊካተቱ ይገባል» የተባሉትን ከጎንደር ወልቃይትን፣ ጠገዴን፣ ጠለምትን፣ ሠቲት፤ እንዲሁም ከወሎ ክፍለሀገር ደግሞ ራያና ቆቦን፣ አላማጣን፣ ወልድያን፣ ጨምሮ እስከ አሸንጌ ኃይቅ ድረስ ያሉትን ሥፍራዎች የሚያካትት ካርታ አዘጋጀ (ተያያዥ ካርታዎችን ከ፩-፬ ይመልከቱ)። በዚህ ሁኔታ ከኢትዮጵያ ተገንጥላ የምትመሠረተው «የትግራይ ረፐብሊክ» ከሱዳን ጋር የሚያገናኛት የመሬት አካል እንድታገኝ ሆነ። በዚህም መሠረት በ፲፱፻፷፱ ዓ.ም. ተሓሕት-ሕውሓት ያለ የሌለ ኃይሉን ከጎንደር ክፍለ ሀገር ነጥቆ ወደ ትግራይ ባካለላቸው ጥንተ-ነዋሪ የዐማራ ሕዝብ ላይ የጥፋት ክንዱን አነሳ።
ከሁሉ አስቀድሞ መታወቅ ያለበት ጉዳይ የትግሬ-ወያኔ ዐማራን ማጥፋት የጀመረው ኢትዮጵያዊነትን በሁለንተናዊ መልኩ ከትግራይ ሕዝብ አዕምሮ እንዲጠፋ ካደረገ እና የዓላማው ተቃዋሚ የሆኑ የራሱን ነገድ አባሎች ከትግራይ ምድር ካጸዳ በኋላ ነው። ይህ በዚህ እንዳለ በ፲፱፻፷፱ ዓ.ም. የተሓሕት-ሕወሓት አመራር አባላት የሆኑት ስብሐት ነጋ፣ አረጋዊ በርሄ፣ ዐባይ ፀሐዬ፣ ሥዩም መሥፍን፣ ስዬ አብርሃ እና አውአሎም ወልዱ «በትግራይ ክፍለሀገር ውስጥ የሚኖሩ ዐማሮች፣ ኦሮሞዎች እና የሌሎችም የኢትዮጵያ ነገዶች ተወላጆች ከትግራይ መሬት ለቀው ይውጡ፤ ትግራይ የትግሬዎች ብቻ ናት!» ብለው ሲወስኑ በወቅቱ ይህን ውሣኔ ተቃውመው የቆሙት ግደይ ዘርዓፅዮን እና ዶክተር አታክልቲ ቀጸላ ብቻ እንደነበሩ ስለሁኔታው የሚያውቁት አቶ ገብረመድህን አርአያ በተለያዩ አጋጣሚዎች አሣውቀዋል። ያ ውሳኔ ተግባራዊ ሆኖ፣ ዛሬ ትግሬዎች ትግራይን በብቸኝነት፣ ቀሪዋን ኢትዮጵያ ደግሞ በገዥነት ተቆጣጥረው ይገኛሉ።

mandag 21. juli 2014

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ያሉበት ቦታ እስካሁን ይፋ አልሆነም

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ያሉበትን ቦታ ለማወቅ ጥረት እየተደረገ ቢሆንም፣ እስካሁን ድረስ ትክክለኛ ቦታውን ለማወቅ አልተቻለም። ይሁን
እንጅ በማእከላዊም ሆነ በቃሊ እስር ቤት አለመኖራቸውን ምንጮች ገልጸዋል።
የገዥው ፓርቲ ሰዎች በአቶ አንዳርጋቸው ላይ የፕሮፓጋንዳ ስራ ለመስራት የተለያዩ ሰዎችን እያነጋገሩ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል።
ኤርትራ ውስጥ ነበርን ያሉ እና በአቶ  አንዳርጋቸው ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ የሚያካሂዱ ” አዳዲስ ሰልጣኞች ” እየተዘጋጁ ሲሆን፣ ከከመንግስት የመገናኛ ብዙሃን ምንጮች የተገኘው መረጃ
እንደሚያሳየው ደግሞ አጠቃላይ የቴሌቪዥን ፕሮግራሙ ከመንግስት ጋዜጠኞች እውቅና ውጭ በደህንነት ሰዎች ብቻ የሚዘጋጅ ይሆናል።
አቶ አንዳርጋቸው ያሉበትን ሁኔታ ለመከታተል ወደ ኢትዮጵያ ተጉዘው የነበሩት የአቶ አንዳርጋቸው ታላቅ እህት በ24 ሰአት ውስጥ አገር ጥለው እንዲወጡ መታዘዛቸው ይታወቃል።

በአብርሃ ደስታ ቤተሰብ ላይ እየደረሰ ያለው ግፍ ከልክ አልፏል

ብዙዎች እንደሚያውቁት አብርሃ ደስታ በትግራይ የሚገኘው የአረና ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ነው። አረና ፓርቲ የህወሃት ተፎካካሪ ፓርቲ በመሆኑ፤ ወያኔዎች በአባላቱ ላይ ግፍ እና በደል ሲያደርሱ ቆይተዋል። አብርሃ ደስታም ትግራይ ሆኖ በዚያ የሚደረገውን ስር አት አልበኝነት በማጋለጡ፤ የትግራይን ህዝብ እንደካደ ተደርጎ ከድብደባ ጀምሮ የእስር እንግልት ደርሶበታል።  አሁንም ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ መኖሩ ይነገራል እንጂ፤ ህዝብ እንዲያየውም ሆነ እንዲጠይቀው አልተፈቀደም። ፍርድ ቤት ያቀረቡትም ሰውነቱ በጣም ደክሞ እና ተጎሳቅሉ ከእኩለ ለሊት በኋላ ነው።
Abraha Desta
Abraha Desta

ይህ በአብርሃ ደስታ ላይ የሚደርሰው ስቃይ እና መከራ እንዳለ ሆኖ፤ እሱ ከታሰረ ጀምሮ ደግሞ በቤተሰቡ ላይ ከፍ ያለ ግፍ እየተፈጸመ መሆኑን ከትግራይ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል። እንዲህ ይነበባል።
• የአብርሀ ታናሽ እህትና የጤና ባለሙያ (የጤና መኮንን/ HO) የሆነችው ተኽለ ደስታ የኢህአዴግ አባልም ሁና የአብርሀ እህት ስለሆነች ብቻ ከስራ ተባራለች፣ ቢሮ እንዳትገባም በዘበኞች ተከልክላለች፣ መልቀቂያም ከልክለዋታል፤ ቀጣዩ ውሳኔም ቁጭ ብላ እንድትጠባበቅም ተነግሯታል፡፡
• ሁለቱ አዲስ ምሩቃን ወንድሞቹ ኣረጋዊ ደስታና ገ/ገርግስ ደስታ በከፍተኛ ብልጫ ሰቅለው የተመረቁ ቢሆንም ዩኒቨርሲቲው እነሱን ላለመቅጠርና ከነሱ ያነሰ ነጥብ ያላቸውን መቅጠሩ ተሰምቷል፤ አዋሳ ዩኒቨርሲቲም ተወዳድረው እንዳለፉ ሲነገራቸው ቆይቶ ሌሎች ከነሱ በታች የነበሩ ሲጠሩ እነሱ እስካሁን አልተጠሩም፡፡
• እናቱ ሙሉ ኣለማየሁ “አንቺ የዐረናው እናት፣ እንቺ የከሀዲው እናት ይህ የህ.ወ.ሐ.ት ምድር ነው- ወዴትም ውጪልን” ድረስ የሚደርሱ ከፍተኛ በደሎች፣ ለቃላት የከበዱ ግፎች እየተፈፀሙባት ነው፤
• ሌሎች ዘመድ አዝማዶቹም በተዋረድ በከፍተኛ ጭንቅ ውስጥ ገብተዋል፣ ነገ በነሱ ላይም ምን እንደሚመጣ ስጋት ገብቷቸዋል፤

• ጀግናን መውለድ እዳው ብዙ ነው፤ በተለይም ደግሞ እዚህ በጭቆናዋ ምድር- በትግራይ! — ይላል የዘገባው መጨረሻ።

ጅምላ ጨራሽ ተውሳክ (Biological Weapons) በድብቅ ወደ ትግራይ ተወሰደ

በመሰረቱ ጅምላ ጨራሽ ተውሳክ ወይም ባዮሎጂካል መርዝ በሰው ልጅ ላይ መጠቀም በተባበሩት መንግስታት የተከለከለ ነው። ሆኖም ይህንን የሰውን ልጅ በጅምላ የሚጨርስ ተውሳክ በህወሃት ጄነራሎች የሚመራው የኢትዮጵያ መከላከያ ሚንስትር በድብቅ ወደ አገር ውስጥ አስገብቶ ነበር። “ለምን እና በማን ላይ ግድያውን ለመፈጸም ነው?” የሚለው ጥያቄ እንዳለ ሆኖ፤ የተባበሩት መንግስታት የጸጥታ ክፍልም ቢሆን እንደዚህ አይነት ጥቆማ ቢደርሰው እርምጃ ለመውሰድ ይችላልና ኢትዮጵያውያን አክቲቪስቶችን ይህንን ጉዳይ ልብ ሊሉት ይገባል። እናም ዛሬ የደረሰን ዘገባ እንዳመለከተው ከሆነ፤የዛሬ ዓመት በድብቅ ተጭነው ወደ አገር ቤት ውስጥ የገቡትን አንትራክስ ስፓርስ (anthrax spores )፥ ብሩሲሎሲስ (brucellosis)፣ እና ቦቱሊስም (botulism) የሚባሉ ጅምላ ጨራሽ ባዮሎጂካል መርዞች ታሽገው ከተቀመጡበት ደብረዘይት መከላከያ ኮሌጅ ላቦራቶሪ ውስጥ ወደ መቀሌ ዛሬ ሌሊት በኮንቴነር ተጭነው እንደተወሰዱ ለማወቅ ተችሏል።
ጥቆማውን ያቀረበው እና አባ ኮስትር በሚል ስም መጠራት የመረጠው ግለሰብ ከሙያውም አንጻር ይህንን ጥቆማ መሰረት በማድረግ ለግንዛቤ እንዲሆን ከዚህ በታች ያለውን የግንዛቤ ጽሁፍ አዘጋጅቶ አቅርቧል።
biological_warfare
ሥነህይወታዊ በሽታ አምጭ(Biological Ethiologic Agents ) ተዉሳክን እንደ ጦር መሳርያ (Biological Weapons )የሰዉ ልጅ መጠቀም የጀመረዉ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ 400 አ.አ የጦር ቀስትን በሞቱ እንስሳ ፈሳሽ ደምና የደም ተዋጾች መዘፍዘፍና ባላንጣን በመዉጋት ፤የኩሬ መጠጥ ዉሀን በመበከል እንደተጀመረ ከጤና ነክ መረጃወች መረዳት ይቻላል።የምራባዊያን ታሪካዊ ድርሳናትም ይህንኑ ያረጋግጣሉ።
የቅርቦችን ክንዉን ሰናስታዉስ በአንደኛዉ የአለም ጦርነት ጀርመን አንትራክስ (Anthrax)የተባለዉን በባክቴርያ በሶስት መንገዶች የሚዛመት ራሱን አካባቢዉ ሁኔታጋር በቀላሉ ሊቋቋም የሚችል(Spore former) እና በአፈር ላይ እስከ ፵ አመታት በላይ መቆየት የሚችል በተለይም ሳር የሚግጡ የቤት እንሰሳን የሚያጥቃ እና ከነሱ ጋር በሚደረግ ንክኪ ማለትም ቆዳቸዉ ሲነካ :-
1. በብነት መልክ በአየር(Aerosols )
2. ሰዉነታችን ላይ ቀላል ጭረት ካለ በንክኪ (Cutaneous) እንዲሁም
3. ሰጋቸዉንበመመገብ (Gastrointestinal) ወደ ሰወች የሚተላለፍ ሲሆን በተመሳሳይም ይህንኑ አንትራክስ በሁለተኛዉ የአለም ጦርነት በጃፓን በሚስጥር በእስረኞች ላይ ተሞክሮ እስከ ሶስት ሺህ የሚሆኑ ሰወች ሰለባ ሆነወል።አሜሪካም ጀርመን በሁለተኛዉ የአለም ጦርነት ባዮሎጂካል መሳሪያን የምትጠቀም ከሆነ ምላሽ የሚሆናትን ለህክምናም ሆነ ለመከላከል አዳጋች የሆነዉን ለስጋ ዉጤቶች መመረዝ መንስኤ የሆነዉን ቦቱሊዝም የሚያመጣ (clostridium botulinum bacteria)የተሰኘ ባክቴሪያ ማዘጋጀትዋ ይታወሳል።በተጨማሪም ኤራቅ፤ ብሪታንያ፤ራሽያ ቬትናም የመሳሰሉ ሀገሮች የባዮሎጂካል ጦር መሳርያን የሚጠቀሙ ሲሆን በዉጤታማነቱም ሆነ በአቅርቦት ከኒውክሌር የተሻለና እጅግ ርካሽ መሆኑንም የተለያዩ የዘርፉ ምርምሮች ያመላክታሉ።
በዚህም መሰረት አንድ ግራም ባዮሎጂካል ቶክሲን (ቦቶሊዝም)አስር ሚሊዮን ያህል ሰዎችን በአንዴ ይገላል።ለምሳሌ ይሄዉ በላቦራቶሪ የተጣራ የቦቶሊዝም ቶክሲን የሰዉን ልጅ መተንፈሻ ና ነርቭ በማጥቃት ከሚታወቀዉ ሳሪን ኬሚካል ጦር መሳርያ(sarin chemical weapon ) ይልቅ ሶስት ሚሊዮን ጊዜ እጅግ ሲበዛ መርዛማ(potent) ነዉ።ቦቱሊዝም ሳሪን ኬሚካል ከሚሸፍነዉ የቆዳ ስፋት አንጻርም አንድ ግራም ቦቱሊዝም የሚባለዉን አደገኛ ገዳይ ቶክሲን አስራ ስድስት እጥፍ ማለትም ሶስት ሺህ ሰባት መቶ ያህል(3700) ስኩየር ካሬ ሜትር ቦታ ይሽፍናል።
ሌላ ጊዜ በሰፊዉ የምመለስበት ሆኖ ለጥፋት የተዘጋጀዉ አፍሪካዊ ናዚ ወያኔ እነዚህን በተባበሩት መንግስታት ጠቅላላ ጉባኤ የተከለከሉ የባዮሎጂካል የጦር መሳሪያወች(Biological Weapons) አከማችቶ መገኘቱ እንደምታ ሊጤን ፤ ሊታወቅ ና መረጃዉ ተጣርቶ አለም አቅፍ ትኩርት ሊሰጠዉና ወንጀለኛዉ ትግራይ መራሹ የወንበዴ ቡድን እጅከፈጅ (Redhanded) ተይዘዉ ለፍርደ እንዲቀርቡ ሁላችንም የድርሻችንን እንወጣ።

søndag 20. juli 2014

ልዕልት ሂሩት በ84 አመታቸው አረፉ

የልዕልት ተናኘወርቅ ኃይለስላሴ እና የራስ ደስታ ዳምጠው ልጅ የነበሩት ሂሩት ደስታ ዳምጠው ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል። የቤጌምድር አስተዳዳሪ የነበሩት ባለቤታቸው ጄነራል ነጋ ተገኝ የዛሬ አስር አመት በሞት የተለዩ ሲሆን፤ ልዕልት ሂሩት በደርግ ዘመን ከሌሎች ንጉሣዊ ቤተሰቦች ጋር ለ14 አመታት ከታሰሩ በኋላ እንደኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1980 ከእስር መፈታታቸው የሚታወስ ነው። ከ እስር ከተፈቱ በኋላ ነዋሪነታቸውን በለንደን አድርገው ይኖሩ የነበሩት ልዕልት ሂሩት ምንም ልጅ አልነበራቸውም።
ቀዳማዊ ኃይለስላሴ እ.አ.አ አሜሪካን ሲጎበኙ የልጅ ልጃቸው ልዕልት ሂሩትም አብረው መጥተው ነበር። ከጃኩሊን ኬኔዲ ጎን ቆመው የሚታዩት እኚሁ ልዕልት ሂሩት ናቸው።
ቀዳማዊ ኃይለስላሴ እ.አ.አ አሜሪካን ሲጎበኙ የልጅ ልጃቸው ልዕልት ሂሩትም አብረው መጥተው ነበር። ከጃኩሊን ኬኔዲ ጎን ቆመው የሚታዩት እኚሁ ልዕልት ሂሩት ናቸው።
በደርግ ዘመን ከተረሸኑት 60ዎቹ ሰዎች መካከል የልዕልት ሂሩት ወንድም እና የባህር ኃይል አዛዥ የነበረው እስክንድር ደስታ አንዱ እንደነበር ይታወሳል። የልዕልት ሂሩት የቀብር ስነ ስርአት ባለፈው ሳምንት በቅድስት ስላሴ ቤተ ክርስቲያን፤ በተለይ ለንጉሣውያን ቤተሰቦች በተዘጋጀው ከቤተ ክርስቲያኑ ምድር ቤት በክብር አርፏል።

ለክቡር አምባሳደር ጥሩነህ ዜና… የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር (ግርማ ሠይፉ ማሩ – የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል)

ሐምሌ 11 ቀን 2006
ለክቡር አምባሳደር ጥሩነህ ዜና
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር
አዲስ አበባ
ጉዳዩ፡ በጥርጣሪ በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎችን ሰብዓዊ መብት አያያዝ ይመለከታል
ክቡር ኮሚሽነር ከሐምሌ አንድ ቀን ጀምሮ በ “ወንጀል” ተጠርጥረዋል በሚል የፓርቲያችን አንድነት ለፍትህና ዲሞክራሲ (አንድነት) የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው እና የድርጅት ጉዳይ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም አቶ አብርሃ ደሰታ ከአረና ፓርቲ እና አቶ የሺዋስ አሰፋ ከሰማያዊ ፓርቲ በፖሊስ ቁጥጥር ስር አንደሚገኙ ሰምተዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይሁን አንጂ ይህን ማመልከቻ እሰከምፅፍበት ሰዓት ድረስ ግልፅ ባልሆነ ሁኔታ ታሳሪዎች ከህግ አማካሪ እና ቤተሰብ ጋር በህግ በተፈቀደው ስርዓት መሰረት ሊገናኙ አልቻሉም፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ ማንም በሌለበት እና ከህግ አማካሪዎች ጋር ሳይገናኙ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ተጠይቆባቸው ወደ ማእከላዊ ሄደዋል የሚል ዜና ቢወጣም አሁንም በትክክለኛ ሁኔታ ፍርድ ቤት ስለመቅረባቸው መረጃ የሚሰጥ አካል አላገኘንም፡፡ አንድ እድ ሰዎች ከምሸቱ በአንድ ሰዓት ፍርድ ቤት ቀርበዋል የሚሉም አሉ፡፡
በዚህ የተነሳም ተሳሪዎች በድብቅ ፍርድ ቤት ቀርበዋል የሚባልበት ሁኔታ እና ይልቁንም ከህግ አማከሪያቸው እንዲሁም ከቤተሰብ ጋር እንዳይገናኙ የተደረገበት ሁኔታ ለከፍተኛ ጥርጣሬ የሚያሳድር ነው፡፡ የእነዚህ ታሳሪዎች በጥርጣሬ የታያዙበትን ወንጅል እንዲያምኑ በኢትዮጵያ ህገ መንግሰትም ሆነ በህገ መንግሰት ተቀባይነት ባገኙ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት ምንም ዓይነት የሀይል እርምጃ እና ህገወጥ የሆነ ምርመራ ማካሄድ አይቻለም፡፡ ሰለሆነም ክቡር ኮሚሽነር በህግ መንግሰት የተፈቀደ ሰብዓዊ መብታቸውን የተነፈጉ እነዚህ ታሳሪዎች ያሉበትን ሁኔታ መስሪያ ቤቶ ክትትል እንዲያደርግ እና ለቤተሰቦች እንዲያሳውቅ አደራ ጭምር እየጠየቅሁ፡፡ የፖሊስ አካላትም ይህን ህገወጥ ክልከላቸውን እንዲያቆሙና ለህግ ተገዢ እንዲሆን እንዲያሳሰቡልን እንጠይቃለን፡፡ በአፋጣኝ ታሳሪዎችን ሁኔታ ማወቅ በታሳሪዎች ላይ ሊደርስ ከሚችል አካላዊም ሆነ ሌላ ማንኛውም ጉዳት ለመታደግ ስለሚረዳ፣ ሀገርም ከዚህ የምትጠቀመው አንድም ነገር ስለማይኖር ክቡርነትዎ አሰፈላጊውን ትኩረት ስጥተው ኃላፊነቶን እንደሚወጡ ተሰፋ አለኝ፡፡
ከማክበር ከሠላምታ ጋር
ግርማ ሠይፉ ማሩ
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል

ዱላ የሃይማኖት እና የዜግነት መብትን፣ ሰብአዊ ክብርንም ከማጣት በላይ አያሳምመንም! (ነስረዲን ኡስማን)

በፖሊስ ፈጥኖ ደራሽ ካምፕ በሰብአዊ ፍጥረት ላይ ወንጀል ተፈጽሟል፡፡
“በአላህ እና በተበዳይ መካከል ግርዶሽ የለም!”
ጁምአ ሐምሌ 11፣ ለቅዳሜ ሐምሌ 12 አጥቢያ፣ ኮልፌ በሚገኘው የፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ ግቢ ውስጥ ሌሊቱን ሙሉ በሺህዎች በሚቆጠሩ ሰብአዊ ፍጡራን ላይ ከባድ ወንጀል ተፈጽሟል፡፡ …
በነፍስ ወከፍ ወፋፍራም ዱላ የያዙ በመቶዎች የሚቆጠሩ ፖሊሶች መንትያ ሰልፍ ሠርተው ፊት ለፊት እየተያዩ ቆመዋል፡፡ በረድፍ በቆሙት ፖሊሶች መካከል ያለው ርቀት 3 ሜትር አይሆንም፡፡ በሁለቱ ረድፎች መካከል ያለው ርቀትም ከዚያ አይበልጥም፡፡ ከአንዋር መስጂድ ቅጥረ ግቢ በበርካታ የጭነት መኪና ታጭቀው የተወሰዱት የአዲስ አበባ ነዋሪ ሙስሊሞች ወፋፍራም ዱላ ይዘው ግራ እና ቀኝ በረድፍ በቆሙት ፖሊሶች መሃል ለመሃል በእንብርክክ እንዲሄዱ ታዘዙ፡፡ በእንብርክክ የሚሄዱበት መሬት ሆን ተብሎ ለቅጣት የተዘጋጀ ይመስላል፡፡ ጠጠራማ፣ አሸዋማ፣ ድንጋያማ፣ ኮረታማ እና ጭቃማ ነው፡፡ ፖሊሶቹ የሠሩት መንትያ ረድፍ ከ300 ሜትር ይበልጣል፡፡ በዚያ መሬት ላይ ይህን ያህል ርቀት በእንብርክክ መሄድ በራሱ ከባድ ቅጣት ነው፡፡ ዋናው ቅጣት ግን ይህ አልነበረም፡፡ ወፋፍራም ዱላ ይዘው በመንታ ረድፍ የቆሙት ፖሊሶች በሙሉ የእንብርክክ በሚሄደው በእያንዳንዱ ሙስሊም ላይ ዱላቸውን ያሣርፉበታል፡፡ ወገቡን፣ ጭንቅላቱን፣ አንገቱን፣ ሽንጡን፣ እግሩን … በቃ ያገኙት ቦታ ላይ ይመቱታል፡፡ ተደብዳቢው አናቱ ላይ ተመትቶ ራሱን ከሳተ ጎትተው ከረድፋቸው ውጪ አውጥተው ጥለውት ፈጥነው ቦታቸው ላይ ይመለሳሉ፡፡ አንድም ልጅ ዱላችሁን ሳይቀምስ እንዳያልፍ የተባሉ ይመስላሉ፡፡ ጁምአ ዕለት ሐምሌ 11 ቀን በፆም የዋሉ በሺህዎች የሚቆጠሩ ወንድሞች በዚህ መልኩ ከ300 ሜትር በላይ የእንብርክክ እየሄዱ ከግራና ከቀኝ በዱላ ተቀጥቅጠዋል፡፡ ይህ በሰብአዊ ፍጡራን ላይ የተፈፀመ ወንጀል (Crime against humanity) አይደለምን?! …
አገራችን ኢትዮጵያ ይህን መሰል ኢ ሰብአዊ ወንጀል በዜጎች ላይ እንዲፈፀም ትዕዛዝ ለመስጠት እና ይህን ትዕዛዝ ያለአንዳች ሰብአዊ ርኅራኄ ለመፈፀም የሚፈቅዱ በሰው አምሳል የተፈጠሩ ውሾች ያሉባት አገር መሆኗን ማወቅ በጣም ያሳምማል፡፡
ላለፉት ሁለት ተኩል ዓመታት እንደ ዜጋም፣ እንደ ሃይማኖት ማኅበረሰብም ስለ ሕገ መንግሥታዊ መብቶቻችን መከበር በሰላማዊ መንገድ ስንጮህ፣ የሕወሓት/ኢሕአዴግ መንግሥት ለዚህ የህዝቦች የጋራ ጩኸት ተገቢ ምላሽ ከመሥጠት ይልቅ እኒህን መሰል ፍፁም ከሰብአዊነት የወጡ ወንጀሎችን መፈፀምን መርጧል፡፡ የሃይማኖት ነፃነትና የዜግነት መብቶቻችን እንዲከበሩ በጠየቅን የጅምላ ድብደባ ወንጀል ሲፈፀምብን ይህ የመጀመርያ አይደለም፡፡ የሕወሓት/ኢሕአዴግ መንግሥት ይህን መሰል ኢ ሰብአዊ የድብደባ ወንጀሎችን በመፈፀም ምን እንደሚያተርፍ ባይገባንም፣ በእኛ በኩል ዱላ እና ጥይት በሃይማኖታችን ምክንያት የተፈፀሙብንን እና ዛሬም እየተፈፀሙብን ያሉ ግልጽ የሃይማኖት ነፃነትና የዜግነት መብት ረገጣዎችን አሜን ብለን እንድንቀበል ሊያደርጉን እንደማይችሉ በአጽንኦት ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን፡፡
ከዚህ ቀደም በተለያዩ ጊዜያት የተፈፀሙብን የጭካኔ ድብደባዎች የሃይማኖት ነፃነትና የዜግነት መብት ጥሰቶችን በመቃወም ከምናደርገው ትግል እንድናፈገፍግ አላደረጉንም፡፡ መንግሥት እስካሁን ከወሰዳቸው በርካታ ሕገ ወጥ እርምጃዎች በኋላ፣ ዛሬም እንደ ሕዝብ ድምፃችንን ለማሰማት ስንሰበሰብ የዱላ አማራጭን መከተሉ እንደ መንግሥት ሊያፍርበት የሚገባ ድንቁርና ወለድ እርምጃ መሆኑን አስረግጠን ልንነግረው እንሻለን፡፡ ለዜጎች ሕጋዊ እና ትክክለኛ የመብት ጥያቄ፣ ዱላ እና ጥይት በምንም ዓይነት መፍትኄ አያመጡም፡፡ ዱላ እጃችሁ ላይ ስላለ ዜጎችን በመደብደብ፣ ጠመንጃ እጃችሁ ላይ ስላለ ዜጎችን በመግደል ከመገበዝ፣ እንደ መንግሥት የህዝብን ድምጽ ብትሰሙ መልካም ነው፡፡ ያ ካልሆነ ግን፣ ሌላው ቢቀር፣ ቢያንስ እኛ ሰላማዊ ትግላችንን በጽናት ከመቀጠል የማናፈገፍግበትን ምክንያት ብታውቁት መልካም ይመስለናል፡፡ አንድ መንግሥት በሚያስተዳድረው ሕዝብ ላይ በደልን ማብዛቱ ለውድቀት ይዳርገው እንደሁ እንጂ፣ ከቶም አሸናፊ አያደርገውም፡፡ እንደምን ይህን ሐቅ ማየት እንደተሳናችሁ ባይገባንም፣ በአንጎለ ቢስ ፖሊሶች እንዲህ እያስቀጠቀጣችሁንም ትግላችንን በጽናት የምንቀጥልበትን ምክንያት እንንገራችሁ፡፡
ትግላችንን በጽናት የምንቀጥለው ውሾቻችሁ ያለ ርኅራኄ ያሳረፉብን በመቶዎች የሚቆጠሩ በትሮች ስላልጎዱን፣ በአካላችን ላይ ጉዳት ስላልደረሰብን አይደለም፡፡ የአንድ ቤተሰብ አባላት የሆኑ ሁለት እና ሦስት ወንድማማቾችን ጨምሮ በብዙ ሺህዎች የምንቆጠር ሙስሊም ዜጎች በጨካኞች በትር እንደ እባብ ተቀጥቅጠናል፡፡ ህይወታቸው በአስጊ ሁኔታ ላይ የሚገኝ ወንድሞችም ጥቂት አይደሉም፡፡ እናም ዱላው አላሳመመንም፤ አካላችን አልተጎዳም አንልም፡፡ ነገር ግን፣ ምንም ዓይነት ጭካኔ የተመላበት ሕገ ወጥ ድብደባ፣ ብሎም እሥርና ግድያ፣ በገዛ አገራችን ሙስሊም በመሆናችን ብቻ እየተፈፀሙብን ካሉት የዜግነት መብት እና የሃይማኖታዊ ነፃነት ረገጣዎች በላይ አያሳምሙንም፡፡
የዚህች አገር ዜጎች እንደመሆናችን፣ መብቶቻችን እና ሃይማኖታዊ ማንነታችን ተከብሮ፣ በዜግነታችን ኮርተን፣ በሰላም ወጥተን በሰላም መግባት የምንሻ ሕዝቦች ነን፡፡ ካለፉት ሦስት ዓመታት ገደማ ወዲህ ግን፣ መንግሥት ግልጽ ፀረ-ሙስሊም ፖሊሲ በመከተል በርካታ የዜግነት መብቶቻችንን እየገፈፈን እንደሚገኝ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ እነዚህ የመብት ገፈፋዎች በተለያዩ ዘርፎች (በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ) የሚገለፁ ሲሆን፣ ከትናንት በስቲያ ድምፃችንን ልናሰማባቸው ከነበሩ በደሎች አንዱ በሆነው የትምህርት ዘርፍ የሚፈፀምብንን በደል ለአብነት ያህል እናንሳ፡፡
ከስድሳ ዓመት በማይበልጠው የኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ታሪክ፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ በሃይማኖታዊ እምነቱ/ቷ እና ተግባራቱ/ቷ ምክንያት ከትምህርት ገበታ ለመፈናቀል ሲዳረጉ የታየው ባለፉት ሁለት ዓመታት ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸው ከዛሬ ነገ ተመርቀው ወደሥራ ዓለም በመግባት እኛንም ሆነ አገራቸውን ያገለግላሉ ብለው በተስፋ ሲጠብቋቸው የነበሩ ወደ አንድ ሺህ የሚጠጉ ሙስሊም የዩኒቨርሲቲ እና የኮሌጅ ተማሪዎች በሃይማኖታቸው ምክንያት ከትምህርት ለመፈናቀል ተዳርገዋል፡፡ በተጨማሪም ከተለያዩ የአገራችን ዩኒቨርሲቲዎች እምነታቸውን በቀናዒነት ለመተግበር የሚተጉ ሙስሊም ተማሪዎች ተለቅመው ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተወርውረዋል፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ከትምህርት መስተጓጎላቸው ሳያንስ፣ በ“አሸባሪነት” የሐሰት ክስ ተመሥርቶባቸው በትምህርት ሊያሳልፉት የሚገባ ወርቃማ ጊዜያቸው እና ዕድሜያቸው ከወህኒ ቤት ፍርድ ቤት በመመላለስ እንዲባክን ተደርጓል፤ እየተደረገም ነው፡፡
በማይምነት፣ በድህነት እና በኋላቀርነት በምትታወቀው አገራችን፣ በቀደምት ዘመናት ሙስሊሙ ኅብረተሰብ ከዘመናዊ ትምህርት በስልታዊ መንገድ ሲገፋ ኖሯል፡፡ በአጠቃላይ በአገራችን ሠፍኖ በኖረው ኋላቀር አስተሳሰብ ሳቢያ በተለይ ሴቶቻችን የዚህ መገፋት ድርብ ሰለባ ሆነው እንደኖሩም ይታወቃል፡፡ ይህ ሁኔታ በሂደት እየተሻሻለ መጥቶ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አካባቢ ጥቂት ሙስሊም ሴቶችን ማየት የተቻለበት ዘመን ላይ ከተደረሰ በኋላ፣ በስንት ድካም ለዚህ ደረጃ የደረሡ ሙስሊም ሴቶችን “ይህን ልበሱ፣ ይህን አትልበሱ” በሚል ተልካሻ ምክንያት ከትምህርት ገበታ ማፈናቀል “ለሴቶች መማር ትልቅ ትኩረት እሰጣለሁ” በሚል መንግሥት ሲፈፀም ማየት በእጅጉ የሚያሳዝንና የሚያሳምምም ነው፡፡
“በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሶላት መስገድ እና ሃይማኖታችሁ በሚያዝዘው መሠረት መልበስ አትችሉም” በሚል የመማር መብትን መነፈግ፣ ከፖሊስ ዱላም፣ ከእስርም፣ ከግድያም በላይ ያሳምመናል፡፡ ይህ የዜግነት መብታችን እና ክብራችንን የሚነካ፣ በፍፁም ከመንግሥት የማይጠበቅ አሳፋሪ ተግባር ነው፡፡ ይህን መቼም ቢሆን ልንቀበለው አንችልም፡፡ ስለዚህም ነው፣ የቱንም ያህል ኢ ሰብአዊ በሆነ መልኩ በዱላ ብንቀጠቀጥም፣ ለራሳችን ክብር ያለን ዜጎች ነንና፣ በከፍተኛ 2ኛ ደረጃም ሆነ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሃይማኖት ነፃነታችን እና መብታችን፣ ብሎም የዜግነት ክብራችንን ለማስጠበቅ የምናካሂደውን ሰላማዊ ትግል እንቀጥላለን የምንለው፡፡
እነዚህን ከመንግሥት የተሳሳተ ፖሊሲ የመነጩ የተሳሳቱ እርምጃዎች ሕጋዊ እና ሰላማዊ በሆነ መንገድ መቃወም፣ ለሕግ ተገዢ የሆኑ ዜጎች ሊያደርጉት የሚችሉትና የሚገባቸው አነስተኛ ነገር ነው፡፡ በአንጻሩ መንግሥት ይህን ሰላማዊ ተቃውሞ ኃይልን በመጠቀምና በእነዚህ ዜጎች ላይ ሕገ ወጥ እርምጃ በመውሰድ ለማስቆም መሞከሩ እጅግ ኃላፊነት የጎደለው፣ የወረደ አካሄድ ነው፡፡ ዜጎች ለመንግሥት ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ መንግሥት “እኔ ጉልበት ስላለኝ የፈለግሁትን ባደርግ ልትቃወሙኝ መብት የላችሁም” በሚል ዜጎቹን በጅምላ በፖሊስ ዱላ የሚያስደበድብ ከሆነ፣ ከተደብዳቢዎቹ ዜጎች ይልቅ ክብር እና ሞገሱን የሚያጣው መንግሥት ነው፡፡
የሕወሓት/ኢሕአዴግ መንግሥት ኃይል እና ጉልበቱን በመመካት፣ በዜጎች ላይ የሚፈጽመው ቅጥ ያጣ ግፍ እና በደል ዋጋ የማያስከፍለው ከመሰለው በጣም ተሳስቷል፡፡ የታዘዙትን ‹አረረ መረረ› ሳይሉ የሚፈጽሙ አንጎለ ቢስ ፖሊሶች እና ወታደሮች አሰማርቶ ሰላማዊ ዜጎችን እንደ እባብ ማስቀጥቀጥ በምንም መለኪያ አገርን የመምራትና ሕዝብን የማሥተዳደር ጥበብ አይደለም፡፡ አንድ መንግሥት ለሕግ ተገዢ ከመሆን የበለጠ ከዜጎች የሚፈልገው ነገር ይኖራል ብለን አናምንም፡፡ በዚህም መንፈስ የአገርን ሰላምና የህዝብን ፀጥታ ሳናውክ፣ የዜጎችን መብትም ሳንነካ፣ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በእምነታችንና በሃይማኖታችን ምክንያት እየተፈፀሙብን ያሉትን በደሎች በሰላማዊ መንገድ እየተቃወምን እነሆ ለሁለት ዓመት ከመንፈቅ ዘልቀናል፡፡ የዚህች አገር ሕዝቦች፣ የዚህችም አገር ዜጎች ነን፡፡ እንደ ሕዝብ እና እንደ ዜጋ “ድምፃችን ይሰማ” እያልን ስንጮህ፣ በመንግሥት ልንሰማ ይገባናል፡፡ ይህን ማድረግ የመንግሥትነት ወግ ነው፡፡ በተቃራኒው፣ የጋራ ጥያቄዎቻቸውን በጋራ ለማሰማት የተሰባሰቡ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎችን ከቤተ አምልኳቸው ሰብስቦ በፖሊስ ካምፕ ውስጥ እንደ እባብ መቀጥቀጥ፣ በሰብአዊ ፍጥረታት ላይ ግልጽ ወንጀል መፈፀም ከመሆኑም ባሻገር፣ እጅግ በጣም ወራዳ የድንቁርና ተግባር ነው፡፡ ይህ ወራዳ የድንቁርና ተግባር “እውን በዚህ አገር መንግሥት ከነግርማ ሞገሱ አለን?” አሰኝቶናል፡፡
እርግጥ ነው፣ መንግሥት የኢትዮጵያ ራዲዮና ቴሌቪዥን ብቸኛ የመረጃ ምንጫቸው ከሆኑ ዜጎች መካከል የተወሰኑ ወገኖቻችንን በፕሮፖጋንዳ ያታልል ይሆናል፡፡ ነገር ግን በገጠርም ሆነ በከተማ ያለው አብዛኛው ሕዝብ ለተራዘሙ ጊዜያት በመታለል ይኖራል ብሎ ማሰብ፣ ያለጥርጥር ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ሕዝበ ሙስሊሙ አንድነቱን ጠብቆ፣ በመንግሥት ኃይሎች የሚፈፀሙበትን ሕገ ወጥ በደሎች ለሐቅና ለሰብአዊ ክብር የሚከፈል ተገቢ መስዋዕትነት መሆኑን ተገንዝቦ ትግሉን በጽናት ይቀጥላል፡፡ ሰላማዊ ትግሉ እስከቀጠለ ድረስ ደግሞ ጊዜ በገፋ ቁጥር እውነቱ ደምቆ እየወጣ ሐሰት መኮሰሷ የማይቀር ነው፡፡ ያኔ የግፍ በትር ያሳረፋችሁባቸው ዜጎች በከፈሉት መስዋዕትነት ኮርተው ቀና ሲሉ፣ እናንተ ግን ታፍራላችሁ፡፡
አንድ በጣም የምወዳቸው አንደበተ ርቱዕ ሸኽ አንድ ዕለት የተናገሯትን ድንቅ ንግግር ለጽሑፌ መደምደሚያ ላደርጋት እወዳለሁ፡፡ “በአላህ እና በተበዳይ መካከል ግርዶሽ የለም!!”

lørdag 19. juli 2014

ወይንሸት ሞላ ክፉኛ ተደብድባ ዝግ ችሎት ቀረበች!

በትላንትናው እለት አንዋር መስጊድ ህዝበ ሙስሊሙ ሲደበደብ ወይንሸት ሞላ በስፍራው ነበረች። አንድ ከዚህ በፊት የሚያውቃት የደህንነት አባል በቀጥታ ወደሷ መጥቶ ይደበድባት ጀመር። በወቅቱ በስፍራው የነበረው በፍቃዱ ጌታቸው ስለሁኔታው እንዲህ በማለት ጽፎ ነበር።
በወቅቱ የሰማያዊ ፓርቲ የሰማያዊ ፓርቲ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል የሆነችው ወጣት ወይንሸት ሞላ አብራኝ ነበረች፡፡ አንዋር መስጊድ በወንዶች መግቢያ ፊት ለፊት ካለው ህንጻ ላይ ሆነን ሁነቱን ስንከታተል ከአሁን ቀደም የሚያውቃትና ከህንጻ ላይ ሆኖ ሲቀርጽ የነበር ደህንነት ብቻዋን ነጥሎ እየደበደበ ወሰዳት፡፡  ‹‹ለምን ተወስዳታለህ!›› ብዬ በጠየኩበት ወቅት ከእነዛ ከመንገድ ተለቃቅመው ለድብደባ የተሰማሩት ወጣቶች መካከል አንዱ ሽጉጥ አወጣብኝ፡፡ ለመሳሪያ ልምድ የሌለው በመሆኑ ካርታው እግሩ ስር ወደቀበት፡፡ ወይንሸትን ይዘውም ወደ ውጭ ከነፉ!
ወይንሸት ሞላ
ወይንሸት ሞላ
ዛሬ ፍርድ ቤት ይዘዋት ቀርበዋል። ሁኔታውን የተከታተለው ዮናታን ተስፋዬ የታዘበውን እንዲህ በማለት ነው ያቀረበው። “እጇቿ ክፉኛ ተጎድተዋል፡፡ ጣቷ አብጧል፡፡ ፊቷ ገርጥቷል፡፡ የግራ እጇ በፋሻ ተጠቅልሎ አንገቷ ላይ እንደታሰረ በአንድ ፖሊስ እርዳታ ወደ ፍርድ ቤቱ ግቢ ገብታለች፡፡” ብሎ ነበር። ጥቂት ቆይቶ ባስተላለፈው መልእክት ደግሞ “ወይንሸት ጭንቅላቷን በቀኝ በኩል ተፈንክታለች፡፡ ተሰፍቶ ይታያል፤ ቀኝ እጇ መሰበሩ ተረጋግጧል፡፡ ሰውነቷ በጣም መጎዳቱ ያስታውቃል፡፡ ከፍርድ ቤት መልሰው አዲስ አበባ ፖሊስ ከሚሽን ወስደዋታል፡፡ ማንም እንዲያያት አልተፈቀደም የፍርድ ሂደቱንም ማንም መከታተል አልቻለም፡፡ ስንቅ ማቀበልም ተከልክሏል፡፡” በማለት ሁኔታውን አስረድቷል።
አሁን በደረሰን ዘገባ መሰረት በዝግ ችሎት የቀረበችው ወይንሸት ሞላ 14 ቀን ተጨማሪ ምርመራ ተጠይቆባት፤ 14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባታል፡፡ የፍርድ ቤቱን ሂደት ማንም ሰው እንዲከታተል አልተፈቀደም የህግ ሰውም እንዳያናግራት ተከልክሏል፡፡  አሁን ከማዕከላዊ አጠገብ በሚገኘው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እስር ቤት ነች፡፡ የፖሊስ ጣቢያው ኃላፊዎች ማንም ሰው ሊያያት እንደማይችልና ስንቅም ሆነ ልብስ ላልተወሰነ ቀናት እንዳይመጣ በማለት መልሰውናል፡፡
አሁን ያለው ሁኔታ ይህን ይመስላል። ትንሽ ቆይተው እሷንም አሸባሪ ብለው መክሰሳቸው የማይቀር ነው። ሌላ የሽብር ክስ ከመስማታችን በፊት፤ ትክክለኛውን ነገር ከወዲሁ እንዲረዱት፤ ወይንሸት ሞላ ወደ አንዋር መስጊድ ከመሄዷ በፊት አግኝቷት የነበረው ዮናታን ቀደም ብሎ የዘገበውን እናስነብብዎ። እንዲህ በማለት ጽፎ ነበር።
ወይኒ ትናንት ጠዋት ላይ ቢሮ ቁጭ ብዬ ከላፕቶፕ ላይ እንደተደፋሁ መግባቷንም ሳላስተውል . . .
“እዚህ አፍንጫችን ስር ይህን የመሰለ ሰላማዊ ትግል ሲካሄድ ቢያንስ ሄደን አንታዘብም!? እዚህች መርካቶ አጠገብ ተቀምጠን ዘመን እየተጋራን – ታሪክ እየተጋራን . . .” ስትል ቀና ብዬ አየኋት።  . . . ምንም ማለት አልደፈርኩም. . . ለብዙ ጊዜ አንዋር መስጂድ እሄድ ነበር (በተለይ ባለፈው ዓመት)  የግልና የፖለቲካ ስራ ጊዜ አይሰጥም እንጂ አሁንም ብገኝ ምኞቴ ነው ፤ ሰው በጨካኞች ተከቦ ለመብቱ በፅናት ፍፁም ሰላማዊ ሆኖ ሲጮህ መመልከት በራሱ ትልቅ መነቃቃት እና ተስፋ ይሰጣል፡፡
ወይኒን ተረዳኋት ግን ሰጋሁ፡፡ ምክንያቱም ወይኒ ቀጥተኛ ሰው ነች . . . የሰው ጥቃት አትወድም . . . ሰው ሲበደል እያየች ዝም የሚል አፍ አልፈጠረባትም . . . ትናገራለች በጣም ተቆጥታ ትናገራለች . . . እንኳን በቆመጥ ሲደበደቡ እያየች በክፉ ሲታዩም ይተናነቃታል . . . ከእንባዋ እየተናነቀች ምራቋን ውጣ ትናገራለች . . . ወይኒ እንዲህ ነች . . . ምናልባትም ይህ ተቆርቆሪ ስብዕናዋ ይሆናል ሰማያዊ ፓርቲ ከትማ ያገናኘን፡፡ እናም ሰጋሁ፡፡
እንጃ ቀልቤ የሆነ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል አስቀድሞ አሳወቀኝ መሰል . . .  “ምንም እኮ አዲስ ነገር አይፈጠርም I’ve been there, you know, it’s all the same every Friday” ከልቤ አልነበረም …
“መርካቶ ጉዳይ አለኝ በዛው ሙስሊም ወገኖቼን አየት አየት አድርጌ እመለሳለሁ” ከነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ሽፈራዉ ጋር እንደምትሄድ ነግራን ሄደች። ጌች ተደብድቦ ሲመለስ እሷ በዛው ቀረች . . . የፈራሁት ሆነ የህወሓት ካድሬዎች እንደሚጠሏት አውቃለሁ፤ ግን ፅናቷ ያፅናናኛል፡፡
ጎንደር አብረን ታስረን የማይረሳ ትዝታ ቀርፃብኝ ነበር . . . የሳዑዲ መንግስትን ተቃውመን አደባባይ ስንወጣ ሶስት ጨካኝ ፌደራሎች ብቻዋን ደብድበዋት ኢያስፔድ ታቅፎ ከወደቀችበት ነጥቆ አስጥሏት ሮጦ ከጨካኞች ሲያመልጥ እንኳን በደከመ ሰውነቷ ወደ ተቃውሞው ለመመለስ ፍላጎት ነበራት . . . ማርች 9 የሴቶች ሩጫ ጊዜ ከጣይቱ ልጆች ጋር ከፊት ሆና እየመራች የህወሓት ደህንነቶች አይን ውስጥ መግባቷ በምርመራ ወቅት ለረጅም ሰዓት ያቆዩአት ነበር . . .
የሆነ ሆኖ የወይንእሸት ሞላ ዛሬ በእጃቸው ድጋሚ ገብታለች . . . በመጥፎ ሁናቴም ተደብድባ ተጎድታለች፡፡ ደስተኛ እንደሆነች ግን ውስጤ ይነግረኛል . . . እሷ ነፃ ነች የውስጧን ጥያቄ መልሳ ሰላም አግኝታለች፡፡
በርካታ ሙስሊም ወገኖቻችንም ይህ ሰላምና እርካታ በመከራና በእስር ውስጥ ሆነው እንደሚሰማቸው አምናለሁ፡፡ ለእውነት በፍቅርና በይቅርታ የቆሙ አይወድቁም ነብዩም መሲሁም ያስተማሩን ይህን ነው!!! በርቱ!” በማለት ነበር የትላንቱን ውሎ የገለጸው። ዛሬ ደግሞ ሌላ ቀ ነው፤ ወይንሸት ክፉኛ ተጎድታ ጉዳይዋ በዝግ ችሎት ታየ። መልሰውም ወሰዷት። እኛም መጨረሻዋን ሰላም ያድርገው፤ በማለት እንሰናበታለን።

fredag 18. juli 2014

የዛሬ ዕለት፣ በተወሰነ ደረጃ ሰኔ 1 1997 ዓ.ም መሰለኝ (ጋዜጠኛ ኤልያስ ገብሩ)

የተከበረው የፖሊስ ሙያ ሳይንስ ያገኙትን መደብደብ ነው እንዴ!)
========
ዛሬ ረፋድ ላይ ከቤቴ ስወጣ፣ የምወደውን የዮጋ ስፖርት ሰርቼ እና አምላኬን አመስግኜ ነበር፡፡ ደስ የሚል ጥሩ ስሜትም ነበረኝ፡፡ ታላቁ አንዋር መስኪድ ከደረስኩ በኋላ የተፈጠረውን አሳዛኝ፣ ሰቅጣጭና ዘግናኝ ሁኔታ ከተመለከትኩኝ በኋላ ግን እስከአሁኗ ደቂቃ ድረስ እጅግ ተከፋሁ፤ ብዙ ነገሮች በአዕምሮዬ ተመላሰለሁ፡፡ ከምንም በላይ የሀገሬ አብዛኛው ህዝብ የተጎሳቀለ ሕይወት እና ይህቺ ሃብታም ሆና በብዙ ችግሮች የሚማቅቁ ዜጎችን የያዘች ሀገሬ አሳዘነችኝ፡፡ 
ኤልያስ ገብሩ
ኤልያስ ገብሩ

በጣም ሰላማዊ የሆነ ኃይማኖታዊ ሥርዓት በደቂቃዎች ውስጥ ወዳልታሰበ ብጥብጥ እና ረብሻ ውስጥ ሲገባ በዓይኔ ብሌን ስመለከት እንዴት አልከፋ?! በፖሊስ ፊት የተገኙ ዜጎች በሚያሳቅቅ መልኩ የዱላ በትር ሲያርፍባቸው መመልከት እንዴት አያም?! ፖሊስ ሮጦ የደረሰበትን ሰው አናት አናቱን በዱላ ከመታው በኋላ የምስኪን ወገኖቼ ደም ሲፈስ አይቼ እንዴት የዘወትር ፈገግታዬ እና ሳቄን ላምጣው?
ይህቺን ጽሑፍ እየጻፍኩ እንኳ ልቤ በሀዘን ተሞልቶ አይኖቼ ዕንባ አርግዘዋል – የወገኖቻችን ጭንቅላት ተበርቅሶ ደማቸው እንደውሃ ሲፈስ ስመለከት ሞት ምን ያህል ቅርባችን መሆኑንም ተረዳሁ፡፡ (በሕይወቱ ሙሉ፣ በአጋጣሚ፣ ለሰከንድ እንኳን ደም ተንጠባጥቦ መንገድ ላይ ስመለከት ውስጤ በጣም ስለሚረበሽ ወዲያው ፊቴን አዞራለሁ)
ከምንም በላይ የገረመኝና አንባብያንን ዛሬ መጠየቅ የዳዳኝ የፖሊሳዊ ሳይንስ ሥነ-ምግባር በኢትዮጵያ ምን እንደሆነ ሰዎች እንዲያስረዱኝ ነው፡፡ በሆነ አጋጣሚ ተቃውሞ በተነሳ ቁጥር ምላሹ እንደእባብ አናት አናቱን መደብደም የፖሊስ ሳይንስ ሕግ ነው?
እሺ፣ ነገሮችን ለማረጋጋት ተብሎ ፖሊስ መጠነኛ እርምጃ የመውሰድ አጋጣሚ ተፈጠረበት እንበል (እንበል ነው ያልኩት)፣ ከሰዎች የሰውነት አካላት መካከል በዋነኝነት ተመርጦ መመታት ያለበት አናታቸው ነውን? በዚህ አጋጣሚ ሳይንሱን የሚተነትንልኝ ኢትዮያዊ ፖሊስ ባገኝ ደስ ባለኝ፡፡ ወይም ስለሳይንሱ የሚውቅ ሰው ይንገረኝ፡፡
ሰዎች አናታቸው ተመትቶ ደማቸው ሲፈስስ ተመለከትኩ እንጂ እኔም ብሆን እድሜ በእጄ ያዛኳት ላፕቴፕ እንደተዓምር መከላከያዬ ሆነችኝ እንጂ በዚህ ሰዓት አናቴ ተፈንክቶ አልጋ ላይ ነበርኩ፡፡ ሁኔታውን ባሰብኩት ቁጥር ይዘገንነኛል – የጋዜጠኝነት ሕይወት ከሞት ጋር የሚያላትም ግዴታ እንዳለበት በጽኑ ባምንም!
ከቀናቶች በፊት አልጀዚራ ቴሌቭዥን በዓለም ላይ በተለያዩ ጊዜያት ከሙያቸው ጋር በተገኛኘ የተገደሉ እና አካላቸው ተጎድቶ በቤታቸው የተቀመጡ ወንድ እና ሴት ጋዜጠኞችን ቃለ-ምልልስ እያደረገ፣ የሞቱትን ደግሞ በፎቶግራፍ እያስደገፈ በማሳየት ሰፊ ዘጋቢ ፊልም ሰርቶ ያቀረበውን ከሁለት ጓደኞቼ ጋር በቤት ተመልክተናል፡፡ የዛሬው የአንዋር መስኪድ አሰዛኝ ሁነት ታዳሚ መሆኔ በፈተና የተሞላ ሙያዬን ይበልጥ እንድወደው እና እስከመጨረሻው ድረስ በዕናት እንድቆምለት ብርታት ሰጥቶኛል – በኢትዮጵያ ከሙያቸው ጋር በተያያዘ የሞት ጽዋን የተጎኘጩ እና የተለያዩ ዋጋዎችን የከፈሉ እና በመክፈል ላይ ያሉ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገራት ተበትነው የሚገኙ ጋዜጠኞችን ለአፍታም ሳልዘነጋ!
እንደዛሬው አይነት መሰል ሁኔታ ሰኔ 01 1997 ዓ.ም በዚህቺው በመዲናችን አዲስ አበባ ተመልክተናል፡፡ ያኔ ግን ዱላ ሳይሆን ጥይት ነበር፡፡
ኦ አምላኬ፣ መቼ ይሆን በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገራት ያሉ የወገኖቼ እንግልት እና መከራ የሚያከትመው?!
በመጨረሻ መንግሥታችን ሆይ፣ ‹‹ከሁለት ዓመታት በላይ ያቆጠረውን የሙስሊሙ ማኅበረሰብን የመብት ሰላማዊ ጥያቄ አድምጥ! በጠረጴዛ ዙሪያም ተቀምጣችሁ ተወያዩና ሰላማዊ መፍትሄ ስጥ!›› የሚለው እንደኢትዮያዊ ዜጋ ምክሬ ነው፡፡