fredag 30. oktober 2015

የስልጤ ዞን ወጣቶች የመንግስት ኃይሎችን እየተጋፈጡ ነው * የተጎዱ ተማሪዎች አሉ

ከጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ
ፎቶ ከሳንኩራ ወረዳ በአልም ገበያ ከተማ የተደረገ ተቃዉሞ ነው

ህወሃት መራሹ መንግስት በስልጤ ዞን ተማሪዎችን ከትምርት ቤት፤ የመንግስት ሰራተኞችን ከስራ ገበታ ለማፈናቀል የጀመረዉ ግልጽ ዘመቻ ትኩረት የተሰጠዉ በሚዲያ ብቻ ነዉ። እነዚህ የነገን የብሩህ ተስፋ እሸት የጨበጡ ወጣቶች የራሳችንን አሳተሳሰብና አመለካከት በምንሻዉ መልኩ እንተገብራለን በማለት አንባገነናዊዉን ስርዓት ፊት ለፊት እየተጋፈጡት እየደሙ እየቆሰሉ ነዉ። አቅጣጫ የሚያሳይ፣ አይዞአቹ የሚል ወገንንም ይሻሉ። አንዳንድ ወንድሞችን ለማናገር ሞክሬ ነበር። ጉዳዩ አገራዊ ስለሆነ እንደ ስልጤ ጉዳይ ብቻ መታየት የለበትም በተናጠል የምናደርገዉ ነገር የለም ሲሉ ገልጸዉልኛል። አፋር ሲበደል፥ አፋር ያገር ያለህ ጩኸቴን ስሙኝ ብሎ ኢትዮጵያዊዉን በሙሉ ቢያሰልፍ፤ ሱማሌ፣አማራ፣ኦሮሞ ወዘተ በደልና ጭቆና ሲደርስበት የራሱን የመጀመሪያ የድረሱልኝ ጥሪ እያሰማ ወደ አገራዊ ጉዳይ የመቀየሩ ሒደት ያለና የነበረ ነዉ። ስለዚህ ባገርም ይሁን ባህር ማዶ ያለዉ የስልጤ ማህበረሰብ አቅሙ በሚፈቅደዉና ማድረግ በሚችለዉ መጠን አስቸኳይ ስብሰባዎችን በማድረግ፣መግለጫዎችን በማዉጣት፣ ሰላማዊ ሰልፎችን በማድረግ ከቅበት እስከ ሁልባረግ፤ ከሁልባረግ እስከ ዳሎቻና ጦራ ያለዉን ወገን የመታደግ ሐላፊነት አለበት። ዝምታዉ በቅቶ የተቀናጀ ስራ የሚሰራበት ወሳኝ ወቅት ላይ ነን። ልብ ያለዉ ልብ ይበል። ጅግ ባሎቲ ይከታን! ፎቶ ከሳንኩራ ወረዳ በአልም ገበያ ከተማ የተደረገ ተቃዉሞ ነው። ተማሪዎች እንደተጎዱ መረጃ ደርሶናል። -

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar