fredag 1. august 2014

መኢአድና አንድነት ፓርቲ በመኢአድ ጽ/ቤት መግለጫ ሰጡ

ውህደታችን የተቃውሞ እንቅስቃሴውን ወደ ላቀ ምዕራፍ ያሸጋግረዋል!
***************************************
አንድነትና መኢአድ በዛሬው ዕለት በሰጡት መግለጫ ውህደቱ ነሐሴ 3 እና 4,2006 ዓ.ም እንደሚደረግና ለጉባኤው የሚደረገውም ዝግጅት እንደተጠናቀቀ ነገር ግን ለጠቅላላ ጉባኤ የሚሆን የገንዘብ እጥረት እንደገጠማቸውና ይህን የፋይናንስ እጥረት ለመቅረፍ ተዋሃዱ ሲለን የነበረው ሕዝባችን ያለብንን የፋይናንስ እጥረት ተረድቶ እንዲተባበረን ስንል ጥሪ እናስተላልፋለን ሲሉ ገልጸዋል፡፡ የሁለቱ ፓርቲዎች ፕሬዚደንቶች እንደገለጹት ውህደቱን ለማድረግ በምናደርገው እንቅስቃሴ ብዙ ፈተናዎች እንደገጠሟቸው ጠቅሰው፣የገዢው ፓርቲ ውህደቱን በተለያየ መንገድ ለማደናቀፍ የሚያደርገው ሙከራና የፋይናንስ እጥረት ተግዳሮቶቻቸው እንደነበሩና ይህን ሁሉ አልፈን ውህደቱን በተባለው ጊዜ የምንፈጽም መሆኑን እናረጋግጣለን ብለዋል፡፡
የመግለጫውን ሙሉ ቃል ከዚህ በታች ቀርቧል
#############################
ከሁለቱ ፓርቲዎች የተሰጠ የጋራ መግለጫ።
ከሁለቱ ፓርቲዎች የተሰጠ የጋራ መግለጫ።
ውህደታችን የተቃውሞ እንቅስቃሴውን ወደ ላቀ ምዕራፍ ያሸጋግረዋል!
**********************************************
ከመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ከአንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
***********************************************
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና አንደነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የውህደት ድርድራቸውን አጠናቀው ሰኔ 1 ቀን 2006 ዓ.ም የቅድመ ውህደት መግባቢያ ሰነድ መፈራረማቸው ይታወቃል፡፡ የሁለቱም ፓርቲዎች ከፍተኛ የአመራር ተቋሞች የጋራ የውህደት አመቻችና ጠቅላ ጉባኤ ጠሪ ኮሚቴ በማቋቋም መመሪያ በመስጠት ስራቸውን ጀምረዋል፡፡ የጋራ ኮሚቴው የራሱ ሰብሳቢ፣ ምክትል ሰብሳቢ እና ፀሓፊ በተጨማሪ የሰነድ ዝግጅት፣ የጠቅላላ ጉባኤ ጠሪ ፣ የሕዝብ ግንኝነት፣ የመድረክ ዝግጅት እና መስተንግዶ፣ የህግና ፀጥታ እንዲሁም የፋይናንስ ንዑስ ኮሚቴዎችን በማቋቋም በሳምንት 3 ቀን ስብሰባ በማድረግ መሰረታዊ እና ዋናዋና ስራዎችን በማጠናቀቅ የጉባኤውን ቀን በመጠባበቅ ላይ ይገኛል፡፡
የፓርቲያችን ውህደት የኢትዮጵያ ህዝብ ለረዥም ግዚያት ሲጠይቅና ሲመኘው እንደ ነበር የሚታወቅ ነው፡፡ ይህንኑ ጥያቄ ለመመለስና ገዢውን ፓርቲ የሚፎካከር ፓርቲ ለመመስረት ብቻ ሳይሆን ትግሉ በይዘትም በቅርፅም ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በሚያስችለን ቁመና ላይ ለመገኘት ተግተን በመስራት ላይ እንገኛለን፡፡ የሁለቱም ፓርቲዎች ውህደት ለማደናቀፍ ከፍተኛ ሴራ እንደሚኖር በመገመትም ነቅተን በመጠበቅ ላይ ነን፡፡ በኛ በኩል ሥራዎቻችንን ብናጠናቅቅም ጉባኤያችንን ለማድረግ የገጠመን መሠረታዊ ችግር ወይም እንቅፋት የገንዘብ እጠረት ነው፡፡
አሁን ባላው ሁኔታ ከ1997 ዓም አገር አቀፍ ምርጫ በኂላ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በከፍተኛ ሁኔታ ለማዳከም ተጠንተው የተሰሩ ጉዳዮች ፓርቲዎችን በአዋጅ የፋይናናንስ አቅማቸውን ማዳከም ነው፡፡ ለዚህም የተሻሻለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ማቋቋማያ አዋጅ እና የመንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን አዋጅ መጥቀሱ በቂ ማሳያ ነው፡፡ አሁን ፓርቲዎቻችን ይህንኑ ችግር ለመቅረፍ የባንክ አካውንት በመክፈት ለሕዝቡ ይፋ አድርገናል በዚህም አንፃር አፋጣኝ ድጋፍንም እንጠብቃለን፡፡
ዛሬ በአገራችን ኢትዮጵያ መጭውን የ2ዐዐ7 አገር አቀፍ ምርጫና ውህደታችን ታሳቢ ያደረገ እስር በፓርቲያችን ከፍተኛ አመራር አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ላይ የተካሄደውን እስር ከማውገዛችንም በላይ ለውህደታችን መሰናክል የሆነብን የገንዘብ እጥረት ጉዳይ ከሕዝቡ ጋር በመወጣት ውህደታችን ለመጨረሻ ጊዜ በተቀመጠለት የጊዜ ሠሌዳ እውን ይሆናል፡፡ ውህዱ ፓርቲ የአሸናፊነት መንፈስ ተላብሶ ከፍ ባለ የሞራል ልእልና ትግሉን ይመራል ለዚህም አንጠራጠርም ፡፡
SP 235 ቦሌ ቅርንጫፍ አቢሲኒያ ባንክ
A/C 47 ጠመንጃ ያዥ ቅርንጫፍ አቢሲኒያ ባንክ
ድል የሕዝብ ነው!
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ ( አንድነት)
ሐምሌ 24 ቀን 2ዐዐ6 ዓም
አዲስ አበባ
ምንጭ፡ ፍኖተ ነጻነት

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar