onsdag 30. april 2014

አንድነት – የአንድነት መግለጫ የዞን ዘጠኝ እስረኞችን በተመለከተ


1zone9
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
———————————————————–
የኢህአዴግ መንግስት በሚቃወሙትና በሚተቹት ላይ እየወሰደ ያለውን አፈና እና እስር የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲታገለው ጥሪ እናቀርባለን!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ(አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
ፓርቲያችን አንድነት አበክሮ በተደጋጋሚ እንደገለፀው ኢህአዴግ ያነበረው አምባገን እና ክፉ ስርዓት ዜጎች በተለያየ ጊዜ የሚያነሱትን የሰብዓዊ መብት፣ የዴሞክራሲና የፍትህ ጥያቄ የሚቀለብሰው ወታደራዊ አቅሙን በመጠቀም ነው፡፡ በዚህ ህገ-ወጥ አካሄዱም ስርዓቱን ይቀናቀናሉ የሚላቸውን ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች፣ ታዋቂ ሰዎችና በግለሰብ ደረጃ ተቃውሞ የሚያሰሙ ዜጎችን የተለያየ ስም እየሰጠ ወደ እስር ቤት አውርዷል፡፡ እያወረደም ይገኛል፡፡ በርካታ ዜጎች የአስከፊው ስርዓት ሰለባ ሆነዋል፣ እየሆኑም ነው፡፡ ሀገራችን በመነጋገርና በመደማመጥ ችግራችንን የምንፈታባት እንዳትሆን ሆን ተብሎ ለዘላለም መንገስ በሚፈልጉ ባለጊዜዎች የፊጥኝ ታስራ፤ ዜጎቿ እንደቀደመው ስርኣት ሁሉ በእስር እየተሰቃዩ ይገኛሉ፡፡
እንደዜጋም በታላቋ ሀገራችን በሰቆቃ እንድንኖር ተፈርዶብናል፡፡ ኢህአዴግ ዛሬም ከመንገድ አፍሶ መውሰዱን ቀጥሏል፡፡ ማሰቃየቱንና ማንከራተቱን ገፍቶበታል፡፡ ከጊዜና ሁኔታዎች እንደመማር ዛሬም ለስርዓቱ አደጋ ናቸው የተባሉ ወጣቶች ሰበብ እየተፈጠረ ወደ ማሰቃያ ስፍራ እየተጋዙ ነው፡፡ የገዥው ፓርቲ አፈ-ቀላጤ በሆኑ ሚዲያዎች የታሰሩት ክስና ወደፊት የሚታሰሩት እነማን እንደሆኑ እየተነገረ ይገኛል፡፡ ወጣት አመራሮቻችንና አባላትን የማሸማቀቅ ስራ እየተሰራም ነው-ስራ ከሆነ፡፡
የኢህአዴግ መንግስት ሰሞኑንም በግል ተነሳሽነታቸው ለሀገራቸው አስተዋፅኦ ለማድረግ ወስነው በብዕራቸው የሰብኣዊ መብት እንዲከበርና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲረጋገጥ በሚወተውቱ የነበሩ የዞን ዘጠኝ አባላትና ጋዜጠኞች ላይ የወሰደው የእስር ርምጃ የሚያመለክተው በቀጣዩ አመት የሚካሄደውን ምርጫ አስመልክቶ የተወሰደ የማሸማቀቅና የወጣቶችን ጥያቄ ለመቀልበስ የሚፈልገው የአምባገነኑ ስርዓት ተግባር ነው፡፡
ፓርቲያችን ሚያዝያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም አመሻሽ ላይ ዞን 9 በተሰኘ ድረ ገጽ (ብሎግ) ላይ በሳል ፖለቲካዊና ማህበራዊ ትችቶችን በማቅረብ ከሚታወቁትን ወጣት ጋዜጠኞች ማህሌት ፋንታሁን፣ በፍቃዱ ሀይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ ዘላለም አጥናፍ ብርሀን፣ አቤል ዋበላ እንዲሁም ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ፣ ጋዜጠኛ አስማመው ኃ/ጊዎርጊስ እና ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት የሚሸረሽር እንደሆነ እናምናለን፡፡ አፈናው ግን ሌሎችን በሺዎች የሚቆጠሩ ብሎገሮችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችን እንደሚፈጥር አንጠራጠርም፡፡
የኢህአዴግ መንግስት የከፈተው የእስር ርምጃ በአስቸኳይ እንዲያቆምና የታሰሩትም ታሰሩ ከተባለበት ሰዓትና ደቂቃ ጀምሮ የሚገኙበትን አጠቃላይ ሁኔታ እንዲጣራ፤ መንግስት ያሰረበትን ተጨባጭ ማስረጃ ካለ ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ፤ ያ ካልሆነ ግን እስረኞቹን በአስቸኳይ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቅ እናሳስባለን፡፡ ፓርቲያችን ዘላቂው መፍትሄ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመፍጠር የሚደረገውን ትግል አፋፍሞ መቀጠልና በሰላማዊ ትግል አምባገነኑን ስርኣት ማስወገድ ብቻ እንደሆነ ያምናል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!!

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar