tirsdag 15. juli 2014

በሽብርተኝነት ስም የሚወሰደው እርምጃ ግልጽነት ይኑረው!

በአገር ውስጥ በህጋዊ መንገድ ተመዝግበው የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች ሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም መንግስት በሽብር ጠርጥሮ በቁጥጥር ስር ማዋሉ በሚዲያዎች ተገልጿል፡፡ እነዚህ አመራሮች ከ48 ሰዓታት በላይ ፍርድ ቤት አለመቅረባቸውና የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት በጉዳዩ ላይ ዝርዝር መረጃ አለማቅረባቸው አመራሮቹ የታሰሩት በሚያራምዱት የፖለቲካ አቋም እንዳይሆን ፓርቲያችን ስጋት አድሮበታል፡፡
የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በጉዳዩ ላይ ጥልቅ ውይይት ካደረገ በኋላ የሚከተለውን አቋም ወስዷል፡፡
መንግስት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የተያዙበትን ምክንያት ለህብረተሰቡ ዝርዝር እና ግልጽ መረጃ እንዲሰጥ፤
የታሰሩት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች በህገ-መንግስቱ አንቀጽ 21 መሰረት ለዜጎች የተሰጠው መብት እንዲከበርላቸው፤
በአስቸኳይ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ፤ የፍርድ ሂደታቸውም ተአማኒ፤ ግልጽ እና ፈጣን በሆነ መንገድ እንዲታይ እያሳሰብን
ይህ ሳይሆን ቢቀር ግን የአገሪቱን ህግ አክብረን በሰላማዊ ትግል ከምንንቀሳቀስ ፓርቲዎች ይልቅ ከዚህ በተቃራኒ የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ሀይሎችን የሚያጠናክር፤ ክርክራቸውንም ምክንያታዊ የሚያደርግ እና የዴሞክራሲያዊ ግንባታውን ወደኋላ የሚመልስ በመሆኑ ጉዳዩ እጅግ እንደሚያሳስበን እንገልጻለን፡፡
ስለዚህም መንግስት የጉዳዩን አሳሳቢነት ተገንዝቦ አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጥ ኢዴፓ ያሳስባል፡፡
የኢዴፓ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ
ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar