onsdag 28. august 2013

አቶ ሐይለማርያም ደሳለኝ ተቃዋሚዎችን በድጋሜ አስጠነቀቁ

መንግስት ባዘጋጀው በሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ላይ ንግግር ያደረጉት አቶ ሐይለማርያም ደሳለኝ ” የአገሪቱ አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የአክራሪዎችንና የአሸባሪዎችን እንቅስቃሴዎች ከመደገፍ ካልተቆጠቡ ህገ መንግስቱ በሚፈቅደው መሰረት እርምጃ እንወስዳለን” ብለዋል።
ማንኛውም ጸረ ሰላም እንቅስቃሴ በሚያደርጉትም ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ የገለጡት አቶ ሐይለማርያም፣ የጥፋት ሀይሎችን ለማምከን የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
አዲሱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያን ፓትሪያርክ አቡነ ማትያስ ጸረ ሰላም እንቅስቃሴዎች ሊወገዙ እንደሚገባ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ፕሬዚዳንት የበላይ ጠባቂ ሼክ ኪያር መሃመድ አማን በበኩላቸው ፣ የመቻቻል ባህሉ ለትውልድ መተላለፍ አለበት ብለዋል።
በጉባኤው ላይ የተለያዩ ባለስልጣናት እና እንግዶች ንግግር አድርገዋል።
መንግስት በቅርቡ በንጹህን ሙስሊሞች ላይ በወሰደው እርምጃ ሊጸጸት ቀርቶ እርምጃው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል እና መንግስት የሀይል አማራጭ ብቸኛው መፍትሄ ነው ብሎ እንደሚያምን ከአቶ ሐይለማርያም ንግግር መረዳት መቻሉን ዘጋቢያችን ገልጿል።
በእስር ላይ ከሚገኙት ድምጻችን ይሰማ አመራሮች ጋር ስለመነጋገር ወይም ችግሩን በሰላም ስለመፍታት ከሀይማኖት አባቶችም አለመነሳቱን አውስቷል።
የስብሰባው አላማ መንግስት ስለወሰደውና ስለሚወስደው የሀይል እርምጃ ከሁለቱም የሀይማኖት መሪዎች ድጋፍ ማግኘትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ከዘጋቢያችን ሪፖርት ለመረዳት ይቻላል።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar