tirsdag 6. august 2013

አንድነት ፓርቲ በባህር ዳር እና አርባ ምንጭ ያካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ በተሳካ ሁኔታ ተካሄደ



 በባህርዳር ስለነበረው ሰልፍ በስፍራው የተገኘው ዘጋቢያችን ሲገልጽ ” ለ ስምንት አመታት የተዘጉ ልሳኖች ተከፈቱ ፤ መከራና ስቃይ ፣ የኑሮ ውድነት ያንገበገባቸው ፤ስራ አጥነት ያማረራቸው ፤ የፍትህ እጦት ያስነባቸው ወገኖች በአደባባይ ተገኝው ድምፃቸውን አሰሙ ብሎአል።
• የታሰሩ የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች ይፈቱ
• መንግስት ህገ-መንግስቱን ያክብር

• መንግስት በኃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን ያቁም!
• መንግስት ለብሄራዊ መግባባት ባስቸኳይ መልስ ይስጥ!
• ውሸት ሰልችቶናል! ይቁም!!
• የጸረ – ሽብር ህጉ ባስቸኳይ ይሰረዝ!
• ዘርን መሰረት ያደረገ ማፈናቀል ባስቸኳይ ይቁም!!
• ሙስና የስርአቱ መገለጫ ነው!!
• የአባይ ጉዳይ የኢትጵያ ሕዝብ ነው!
• ለተከሰተው የኑሮ ውድነት ተጠያቂው መንግስት ነው!!
• የዜጎች ሰብአዊ መብታቸውን የማግኘት መብታቸውይከበር!!
• ዜጎች በሀገራቸው ስራ የማግኘት መብታቸው ይከበር!!
• በአባይ ጉዳይ ወሳኙ የኢትጵያ ሕዝብ እንጂ ግብጾች አይደሉም!!
• የፓርቲ አባልነት በፍላጎት መሆን አለበት!!  የሚሉት መፈክሮች የከተማው ደማቅ የህዝብ ቃሎች ሆነው  አርፍደዋል ብሎአል፡፡
” ያማራው ህዝብ ጨዋ እንጂ ፈሪአይደለም!
ለሱዳን ተቆርሶ የተሰጠው መሬታችን ይመለስ!
የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ባስቸኩዋይ ይፈቱ!
እስክንድር ነጋ ጋዜጠኛ እንጂ አሸባሪ አይደለም።!
የሚሉ መፈክሮችም ተደምጠዋል።የመንግስት አካላት “አረንጓዴ ሽብር ” የሚል ወረቀት እየበተኑ ተመሳስለው በመግባት ሊፈጽሙት ያሰቡት አላማ በከተማው ህዝብ ጥረት አለመሳካቱንም ዘጋቢያችን ገልጿል፡ከባህር ዳር ዙሪያ ወረዳዎች የሚመጣዉን ህዝብ ወደ ሰልፉ እንዳይቀላቀሉ በቀበሌ ካድሪዎች ማሰፈራሪያ እና እንግልት እንዲደርስባቸው ተደርገዋል ፡፡ የባህር ዳር መግቢያዎች በሙሉ በፀጥታ ሀይሎች ተዘግቶ አርፍዷል፡፡ በእለቱ በባህር ዳር ወህኒ ቤቶች በሙሉ የእስረኛ ጥየቃ እንዳይካሄድም ተደርጓል፡፡
ወጣቱ እየተሰደደ ነው በማለት ንግግር ያቀረቡት የፓርቲው ዋና ጸሀፊ አቶ አስራት ጣሴ ነፃነት እስከ ሞት ድርስ መስዋእት ያስከፍላል ብለዋል።
በፓርቲዎች የተቁዋቁዋሙት የንግድ ማእከላት ሲያሻቸው በጉልበት ሲያሻቸው በስርቆት የተቆጣጠሩት ሀብት ሃገርን አደጋ ውስጥ መጣሉንም ዋና ጸሀፊው ገልጸዋል።
“የመንግስት ገዥነት የህዝብ ሎሌነት ሊያበቃ ይገባል” ያሉት አቶ አስራት ፣  የገበሬው ጢሰኝነት ፤ የመሬት ባለቤትነት በህዝብ እንጅ በመንግስት ስር መሆኑ ሊያበቃ ይገባል ሲሉ አክለዋል።
በአርባምንጭም እንዲሁ ፓርቲው ደመቀ ሰላማዊ ሰልፍ አድርጓል። ይህ በእንዲህ እንዳለ
አንድነት “የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት!” በሚል መርህ የጀመረውን ትግል ተከትሎ ከመንግስት  መጠነ-ሰፊ ዘመቻ እንደተከፈተበት ገልጿል።
ፓርቲው ወደ ንቅናቄው ተግባር ከገባ ጊዜ ጀምሮ በርካታ ህዝባዊ ድጋፍ ማግኘቱን እንዲሁም በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ መነቃቃት እና የነፃነት ጥያቄ ድምፅ ከሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች እያስተጋባ መሆኑን ፓርቲው ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።
“በአንፃሩ ገዥው ፓርቲ የህዝቡን የነፃነት ድምፅ ለማፈን የንቅናቄው ተግባር ከተጀመረበት እለት አንስቶ በርካታ መሰናክሎችን እየፈፀመ እንደሚገኝ ጠቁሟል።
<<በጎንደርና በደሴ ያደረግነውን ሰላማዊ ሰልፍ በተደራጀ መንግስታዊ ሽብር ለማደናቀፍ የተሞከረው ሙከራ በህዝቡ ንቁ ተሳትፎ ከሽፎ የህዝቡን የነፃነት ድምፅ ማሰማታችን የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡”ያለው አንድነት፤ ይህ የነፃነት ድምፅ በሌሎች ከተሞች ተቀጣጥሎ እንዳይዘልቅ ገዢው ፓርቲ ነገሮችን  ከሼክ ኑር ኢማም አሟሟት ጋር በማያያዝ ይህ መግለጫ እስከወጣበት ቀን ድረስ በተለያዩ ከተሞች ህዝቡን በማስገደድ አንድነት ፓርቲን እንዲያወግዝ በየቀኑ ሰልፍ በማስወጣት ላይ ይገኛል”ብሏል።
ሐምሌ 28 ቀን 2005 ዓ.ም በጂንካ ፣ ወላይታ ፣ ባህርዳር ፣ አርባምንጭ እና መቀሌ ሰላማዊ ሠልፍ እና ህዝባዊ ስብሰባ እንደሚያደርግ አንድነት ካሳወቀ ጊዜ ጀምሮ የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች በአካባቢው በሚገኙ የአንድነት አባላት ላይ ማዋከብና ከፍተኛ ጫና ፈጥረው መቆየታቸውንም ጠቅሷል።
ሐምሌ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ወላይታ ለቅስቀሳ የገባው የአዲስ አበባ ልዑክ በአካባቢው ባለስልጣኖች  መንግስታዊ ውንብድና ተፈፅሞበታል” ያለው የፓርቲው መግለጫ፤ገዥው ፓርቲ ታርጋ የሌላቸውን ሞተር ሳይክሎች በብዛት በማሰማራት ለቅስቀሳ ከተንቀሳቀሱ አባሎቻችን እጅ- ይዘው የሄዱትን በራሪ የቅስቀሳ ወረቀቶችንና የፀረሽብር ህጉን ለማሰረዝ የተሰባሰቡ ፊርማዎችን ነጥቀዋቸዋል፡፡ብሏል።
እንደ ፓርቲው መግለጫ-የፀጥታ ኃይሎችም ዘራፊዎችን ለማስቆም ፍቃደኛ አልነበሩም፡፡ ሰዎቹ ለቅስቀሳ የተሰማራውን መኪና አራቱንም ጎማ በማተንፈስና ሹፌሩን በመደብደብ ከተማውን ለቆ እንዲወጣ ማስጠንቀቂያ ሰጥተውታል ፡፡ የሰልፉ አስተባባሪዎች በድምፅ ማጉያ መሳሪያም  ቅስቀሳ እንዳያደርጉ ተከልክለዋል፡፡
እንዲሁም የአንድነት ፓርቲ የወላይታ የዞን አመራር አባል የሆነችው  ወ/ሮ ሀድያ መሀመድ ሐምሌ 26 ቀን 2005 ዓ.ም እለት ጀምሮ በግፍ ታስራ ትገኛለች፡፡ በእስር ቤትም የማታምንበትን ሰነድ እንድትፈርም መገደዷ ተመልክቷል።
በመቀሌ ከተማ ከሐምሌ 25 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ቅስቀሳ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ የሰነበተው ልዑክ ምንም ዓይነት የድምፅ ማጉያ መሣሪያ እንዳይጠቀም ከመታገዱም በላይ ለቅስቀሳ ያዘጋጀውን ሞንታርቮ በአደባባይ በፖሊስ ተቀምቷል፡፡
እንዲሁም በቅስቀሳ ላይ የነበሩት የአንድነት ፓርቲ ብ/ም/ቤት አባል አቶ እንግዳ ወ/ፃዲቅ እንዲሁም የትግራይ ዞን የአንድነት ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ክብሮም ብርሃነ እና አቶ አርአያ ፀጋይ በቀዳማይ ወያኔ ፖሊስ ጣቢያ  በዕስር ላይ ይገኛሉ፡፡
<<ይህንን የህገ-መንግስት ጥሰት አንድነት ፓርቲ በፍፁም በዝምታ አይመለከተውም፡፡>>ያለው አንድነት፤<< የጀመርነውን ሠላማዊ ትግል አጠናክረን ፤አንድነት ፓርቲ ሳይገድል እየሞተ ህገ-መንግስቱን የማስከበር ትግሉን አጠንክሮ ዛሬም ወደፊትም ይቀጥላል፡፡”ብሏል።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar