mandag 31. mars 2014

በሀረር ከተማ በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ከፍተኛ ድበደባ እየተካሄደባቸው ነው

የእስር ቤት ምንጮች እንደገለጹት በሀረር ከደረሰው ተደጋጋሚ ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ተቃውሞቸውን አሰምተዋል በሚል የታሰሩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በፌደራል ደህንነት መርማሪዎች ከፍተኛ ድብደባ እየተካሄደባቸው ነው:፡
ፖሊስ ጋራጅ ውስጥ የታሰሩት ወጣቶች ከምግብ ተከልክለው ከዘመድ እንዳይገናኙ ተደርገው ” እመኑ” በሚል ከፍተኛ ድብደባ እየተፈጸመባቸው ነው። ታከሉ ሙላቱ፣ ታገሰ ሙላቱና አዳነ የሚባሉ የጫማ ንግድ ድርጅት ባለቤቶች ከፍተኛ ድበደባ ተፈጽሞባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበር የእስር ቤት ምንጮች ገልጸዋል። በተለይ ታከለ ሙላቱ የተባለው ነጋዴ  ወደ ጀጉላ ሆስፒታል ቢወሰድም፣ ከሆስፒታል በሁዋላ የት እንደተወሰደ አልታወቅም።
በጥይት ተደብድበው የሞቱ ሰዎች መኖራቸውንም ምንጮች አክለው ገልጸዋል። ተወከል የሚባል ወጣት ደረቱ አካባቢ በጥይት ተመትቶ በህክምና ላይ ነው።
ገንዘብ አላቸው የሚባሉ ነጋዴዎችን ደግሞ ” ተጠርጣሪዎች ናችሁ” በሚል እየታሰሩ ፣ ፖሊሶች ጉቦ እየተቀበሉ እየለቀቁዋቸው መሆኑን ምንጮች አክለው ገልጸዋል።
መስተዳድሩ በቅርቡ በሃረር የደረሰውን  የእሳት አደጋ መነሻ በተመለከተ የተለያዩና የተምታቱ መግለጫዎችን እየሰጠ ነው።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar