onsdag 30. oktober 2013

ኢትዮጵያ- የፖሊስ መንግስት ያንሰራፋባት ሀገር (ከፕ/ር አለማየሁ ገብረ ማርያም)


የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ህገመንግስት በህግ ከለላ ጥላ በቁጥጥር ስር የሚውሉ ዜጎችን አስመልክቶ የሚከተሉትን መብቶች ያጎናጽፋል፡፡“በህግ ከለላ ጥላ በቁጥጥር ስር የዋለ ማንኛውም ሰው በህግ አግባብ መብቱ ተጠብቆ ይያዛል፡፡ ማንኛውም ሰው በሀሰት ለመረጃ ጠቀሜታ ተብሎ በማስገደድ እንዲያምን  ወይም የተባለውን እንዲቀበል አይገደድም፡፡ ማንኛውም በማስገደድ የተገኘ መረጃ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡“ ይላል አንቀጽ 19(2)(5)፡፡ እውነታው ሲታይ ግን ይህ የይስሙላ ሙበት የተጻፈበትን ወረቀት ዋጋ ያህል የለዉም፡፡
ባለፈው ሳምንት ሂዩማን ራይትስ ዎች “HRW“ የተባለው ዓለም ዓቀፋዊ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በኢትዮጵያ መንግስት “የፌዴራል ፖሊስ ማዕከላዊ ምርመራ” እየተባለ በሚጠራው የፖሊስ ጣቢያ የሚፈጸሙትን አስደንጋጭና አስከፊ የሰብአዊ መብት ረገጣዎች ዘገባ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው ይህ የፖሊስ ምርመራ ማዕከል በጥርጣሬ የተያዙ ዜጎችን በማሰቃየት ይታወቃል፡፡
እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች ዘገባ “በቁጥጥር ስር ባሉ እስረኞች ላይ በተለይም ያለው መንግስት ይቃወሙኛል በሚላቸው የፖለቲካ እስረኞች ላይ ማዕከላዊ ምርመራ እየተባለ የሚጠራው የምርመራ ተቋም እልህ አስጨራሽ የምርመራ ሂደት በማድረግ እስረኞችን በግድ ወንጀል ሰራን ብለው አንዲአምኑ በማስገድድ፣ እንደሚያሰቃይና ህገወጥ የእስረኞች አያያዝ“ እየፈጸመ እንደሆነ በማረጋገጥ በዘገባው ይፋ አድርጓል፡፡ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ በማያያዝም “ማዕከላዊ ምርመራ እየተባለ የሚጠራው ተቋም ብዙ የተቃዋሚ የፖለቲካ እስረኞች፣ ሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪዎች፣ መንግስት የብሄር ግጭት ተንኳሾች ናቸው በሚላቸውና ሌሎች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ በጅምላ ተይዘው የሚሰቃዩበት የምርመራ ማዕከል” ነው ብሎታል፡፡
ገጣሚው ዊሊያም ኤርነስትን አባባል በመዋስ “ማዕከላዊ የምርመራ ማዕከል”  የሰቆቃ መደብር በለቅሶና በሰቃይ የታጠረ የጭለማ ቤት ነው :: የገዥው መንግስት ተቃዋሚዎች፣ አመጸኞች፣ የሚላቸዉን የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች እና ሌሎች እስረኞች በሙሉ በምርመራ ጊዜ ሰቆቃ ተጠቅሞ አራሳቸዉን አንዲወነጅሉ ያስገደዳቸዋል:: እንዲሁም ብዙዎቹ ማሰቃየትን ጨምሮ የተለያዩ የሰብአዊ መብት ረገጣዎች ይፈጸሙባቸዋል፡፡
እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች አባባል ማዕከላዊ እየተባለ የሚጠራው የምርመራ ተቋም “አስቀያሚው የአካልና የስነ ልቦና ማሰቃያ እንዲሁም አስገድዶ የማሰመኛ ምሽግ” መሆኑን በመጠቆም በማዕከሉ ከሚፈጸሙ የማሰቃየት ወንጀሎች እነዚህ ከብዙ ጥቂቶቹ መሆናቸውን በአጽንኦት ገልጿል፡፡ አኔም በግሌ  ከአስፈሪው ማአከላዊ ምርመራ መዳፍ የተረፉ የቀድሞ እስረኞችን አነጋገሬ አውቃለሁ::
እ.ኤ.አ. በ2011 የአሜሪካ መንግስት መምሪያ በዓመታዊ የሰብአዊ መብት አያያዝ ዘገባው በኢትዮጵያ ያለውን ሁኔታ ለማሳየት የሚከተለውን ማጠቃለያ አስፍሯል፡፡
 ብዙ ተጨባጭ መረጃዎች እንደሚያረጋግጡት እ.ኤ.አ. በ2009 በአዲስ አበባ የሚገኘው ማዕከላዊ እየተባለ የሚጠራው የፖሊስ ምርመራ ማዕከል ፖሊስ ኃይልን በመጠቀም አስረኞችን አስገድዶ ለማሳመን የአካል ማሰቃየት ሰቆቃ ድርጊት ሲፈጽም ነበር፡፡ ይህ ዓይነት የማሰቃየት ዘዴ በአሁኑ ጊዜም በተግባር ላይ እየዋለ ያለ መሆኑን ዜጎች ያላቸውን ሰፊ እምነት አጽንኦት በመስጠት እየገለጹ ነው፡፡ ባለስልጣናቱ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና የዲፕሎማሲው ማህበረሰብ ማዕከላዊ ምርመራን ለመጎብኘት የሚያቀርቡት ጥያቄ አሁንም በመንግስት በኩል አዎንታዊ ምላሽ እንዳላገኘ ይታወቃል፡፡“ በማለት ድርጅቱ ያለውን ሀሳብ ቋጭቷል፡፡
የ15ኛው ክፍለ ዘመን የሰቆቃ ስልት በ21ኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ!
በአዲስ አበባ እምብርት ላይ የሚገኘው ማዕከላዊ እየተባለ የሚጠራው የማሰቃያ ምርመራ ተቋም በመካከለኛው (15ኛው) ዘመን በአውሮፓ የሰብአዊ መብት ረጋጮች በንጹሀን ዜጎች ላይ ይደረግ የነበረውን አስፈሪ፣ አስደንጋጭና ተስፋቢስ የማሰቃየት ስልት ገጽታ መለስ ብለን እንድናስታውስ ያስገድደናል፡፡ እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች መግለጫ “የማዕከላዊ ምርመራ ፖሊሶች በህግ ጥላ ስር የተያዙ የህግ አስረኞችን እነርሱ በሚፈልጉት መልኩ በግድ ለማሳመን፣ መግለጫ እንዲሰጡና ሌሎች መረጃዎችን ለማግኘት ሲሉ በእስረኞች ላይ ማሰቃየትን ጨምሮ የተለያዩ የማስገደጃ  ዘዴዎችን እና ልዩ ልዩ ኢሰብአዊ ድርጊቶቸን ይፈጽማሉ፡፡ እንደ መካከለኛው የአውሮፓ ዘመን መብት ረጋጭ ተቋሞች ሁሉ የኢትዮጵያው የምርመራ ማዕከልም እንደመርማሪዎቹ ፍላጎትና አመችነት ሁኔታ እስረኞችን በአራት ዋና ዋና ክፍሎች መድቧቸዋል፡፡ የማዕከላዊ ምርመራ ማዕከል በተለያዩ የእስረኞች አያያዝና እያንዳንዳቸው ባላቸው ቅጽል ስም የሚታወቁ አራት አይነት የማጎሪያ እስር ቤቶች አሏቸው፡፡ እነርሱም፣ 1ኛ) ጨለማ ቤት፣ ይህ እስር ቤት በጣም አስቸጋሪና ብርሀን የማይገኝበት የማጎሪያ ክፍል ነው፡፡ በዚህ እስር ቤት እስረኞቹ የፀሐይ ብርሀን እና የመጸዳጃ ቤት የማግኘት ዕድላቸው በጣም ጠባብ ሲሆን አንዳንድ ጊዜም ለብቻ የመታሰር ዕጣ ፈንታ ይገጥማቸዋል፣ 2ኛ) ጣውላ ቤት፣ ይህ እስር ቤት በክፍል ውስጥ እንደልብ መዘዋወር የማያስችል ሲሆን ክፍሎቹም በቁንጫ ተባይ የተወረሩ ናቸው፡፡ 3ኛ) ሸራተን፣ በቅርብ ጊዜ ከእስር ቤት የማይለቀቁ ብዙዎቹ እስረኞች ወደዚህ የማጎሪያ ቤት እንዲዛወሩ ይፈልጋሉ፡፡ ይህ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ባለው ሆቴል ስም የተሰየመው እስር ቤት እስረኞቹ የተሻለ የአካል እንቅስቃሴ የማድረግና በህግ አማካሪዎቻቸውና በዘመዶቻቸውም መጎብኘት እንዲችሉ የእስር ቤቱ ኃላፊዎች ፈቃድ የላላበት ነው፡፡ 4ኛ) የተፋፈገው የሴት እስረኞች ማጎሪያ፣ ይህ እስር ቤት በገፍ ሴት እስረኞችን አጭቆ የያዘ ነው፡፡”
ገዥው የኢትዮጵያ አስተዳደር ከተቃዋሚ የፖለቲካ እስረኞች መረጃዎችን፣ መግለጫዎችን እና ተገደው የእምነት ቃል እንዲሰጡ ለማድረግ የተለያዩ የማሰቃያ ዘዴዎችን ይጠቀማል፡፡ ሂዩማን ራይትስ ዎች አንደጠቀሰው: “እስረኞች በተደጋጋሚ በጥፊ ይጠናገራሉ፣ በእርግጫ ይመታሉ፣ በቦክስ ይደለቃሉ፣ በዱላና በጠብመንጃ ሰደፍ ይደበደባሉ፡፡ አንዳንዶች እንደተናገሩት በሚያስጨንቅ ሁኔታ [በመካከለኛው ክፍለ ዘመን ይደረግ እንደነበረው ‘እጅን በገመድ አስሮ ገልብጦ ከጣራ ወደ ታች በማንጠልጠል እንዲወድቁ በማድረግ የማሰቃየት’] ወይም ሁለት እጆችን ወደ ላይ ከእራስ በላይ ከፍ አድርጎ በገመድ አስሮ በማቆም ለበርካታ ሰዓታት በማቆየት በተደጋጋሚ ያሰቃዩ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ አሁንም [በመካከለኛው ዘመን ይደረግ እንደነበረው ሁሉ] በኢትዮጵያ ማዕከላዊ ምርመራ ማዕከልም የእስረኞችን እጆች በካቴና በማስገባት ለበርካታ ጊዜ ታስረው እንደሚቆዩ እንዲያውም አንድ እስረኛ ከአምስት ተከታታይ ወራት በላይ እጁ በካቴና ታስሮ እንደቆየ እና ማቋረጫ በሌለው የቃል ጥያቄ ምርመራ በታሳሪዎቹ ዘንድ ፖሊስ ተደጋጋሚ ዛቻ እንደሚያደርግ ተረጋግጧል፡፡” በጥንት ጊዜ ‘በእስፓኞች ይደረግ እንደነበረው አሰቃቂ የምርመራ ሂደት‘ አንዳንዶቹ እስረኞች ለበርካታ ጊዜ ተገልለው ለብቻቸው እስራታቸውን እንዲገፉ ተበይኖባቸዋል፡፡ በመካከለኛው ክፍለ ዘመን የእስር ቤት ማጎሪያዎች ይደረግ እንደነበረው ሁሉ በዛሬይቱ ኢትዮጵያ እስረኞቹ የፀሐይ ብርሃን የማግኘት መብታቸውን ይከለከላሉ፣ በደካማ የንጽህና አያያዝና በውሱን የህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ይሰቃያሉ፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች በተለይም በመጀመሪያ ለምርመራ  የቀርቡትን ተጠርጣሪዎች ላይ የበለጠ አሰቃቂ ይሆናሉ፡፡”
የእነዚህ ሁሉ የማሰቃየት ተግባራት ዋና ዓላማው በእስረኞች ላይ ታላቅ ጫና በመፍጠር ትክክል ይሁንም አይሁን ለቀረበባቸው የወንጀል ክስ ፈጻሚ መሆናቸውን እንዲያምኑ በማስገደድ መግለጫ፣ የእምነት ቃልና መረጃ እንዲሰጡ ለማድረግ ነው፡፡ እነዚህን በማስገደድ የተሰጡ መግለጫዎችና በግዳጅ የተገኙ የእምነት ቃሎችን አንዳንድ ጊዜ ተወንጃዮቹ ከእስር ቤት ከተለቀቁ በኋላ ወደ ህብረተሰቡ ሲቀላቀሉ ያለውን መንግስት ተገደው እንዲደግፉና ጉዳያቸው በፍርድ ቤቶች በሚታይበት ጊዜም መንግስት እንደ ማስረጃ ለመጠቀም ስለሚፈልጋቸው ነው፡፡
በማዕከላዊ እስር ቤት እስረኞች ለደረሱባቸው የአለአግባብ መታሰርና መንገላታት የሚጠየቅም ሆነ የሚገኝ ካሳ የለም፡፡ ፍርድ ቤቶች ከፖለቲካ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን የማየት ነጻነት የላቸውም፡፡ ፍርድ ቤቶች የማዕካላዊ ምርመራ ፖሊስ በምርመራ ጊዜ በእስረኞች ላይ የማሰቃየትና ህገወጥ ድርጊቶችን ፈጽሟል የሚል ውንጀላ ለፍርድ ቤቶች ቢቀርብ ተገቢውን የማጣራት ሂደት በማከናውን እርምጃ ለመውሰድ አይችሉም፡፡ በሂዩማን ራይትስ ዎች ዘገባ መሰረት የቀድሞ እስረኞች የማዕከላዊ ምርመራን የበቀል እርምጃ በመፍራት በምርመራ ወቅት የደረሱባቸውን በደሎች ለፍርድ ቤቶች ለማቅርብ ስለሚፈሩ ዝምታን እንደሚመርጡ ጠቁሟል፡፡ አንዳንዶቹም ከፍርድ ቤቶች ችሎት በፍጹም ደርሰው እንደማያውቁ ይናገራሉ፡፡
እ.ኤ.አ. በጁላይ 2008 በዓለም በደህንነት ሙያ ታዋቂ የሆኑት እንግሊዛዊው ጡረተኛ ኮሎኔል ሚካኤል ዴዋርስ የኢትዮጵያን የእስር ቤቶች አያያዝ ሁኔታ አጥንተው የመፍትሄ ሀሳቦችን እንዲያቀርቡ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ተዋውለው ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ እስር ቤቶችን ከጎበኙ በኋላ በተጨባጭ የተመለከቱትን የእስር ቤቶችን ሁኔታ እንደሚከተለው አቅርበዋል፡፡ እንደዚህም ይተርኩታል፡፡
“እስረኞቹ ወዳሉበት ግቢ ውስጥ እንድገባ ጥያቄ አቀረብኩ፣ ይህ ግቢ ረዥም የሆነ በአንድ ጎኑ በኩል መጠለያ ሊሆን የሚችል ዳስ ይዟል፣ ግቢው በግንብ አጥር የታጠረ ሲሆን ለአካባቢው ጥበቃ እንዲያመች ሆኖ የተሰራ የጥበቃ ማማና ጥበቃዎች አሉት፡፡ በግቢው ውስጥ ከ70 እስከ 80 የሚሆኑ እስረኞች በተጎሳቆለ ሁኔታ ይታያሉ፡፡ ለሁሉም እስረኞች በምንጣፍ ለመጋደም የሚያስችል በቂ ክፍል የለም፣ መብራት የሚባል ነገር የለም፣ ቦታው በአይነምድርና በሽንት በሚሰነፍጥ ሽታ ታውዷል፣ በግቢው ውስጥ ምንም ዓይነት ውኃም ሆነ የመጸዳጃ ፋሲሊቲ የለም፣ በግቢው ውስጥ ለሴት እስረኞች ተብሎ ትንሽ የሳር ጎጆ ተቀልሳ በቅርብ እርቀት ትታያለች፣ ሆኖም ግን ግቢውን ለማሻሻል ተብሎ በግቢው ውስጥ የተሰራ ምንም ነገር የለም፣ አብዛኞቹ እስረኞች በትናንሽ ወንጀሎች በተለይም በሌብነት ወንጀል እየተያዙ ወደ እስር ቤቱ በተደጋጋሚ የሚመጡ ናቸው፡፡ ጥቂቶቹ ለወራት በዚሁ እስር ቤት የቆዩ ናቸው…፡፡”
ኮሎኔል ዴዋርስ በእስር ቤቱ የተመለከቱትን በሚከተለው መልክ አጠቃለዋል፣ “የእስረኞቹ አያያዝ  በሚያሳፍር ሁኔታ ላይ የሚገኝ ሲሆን ይህም ሁኔታ ፌዴራል ፖሊስን ለሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ትችት እንዲጋለጥ አድርጎታል፣ ማንም ቢሆን እስር ቤቶች እንደ ሂልተን ሆቴል መሆን አለባቸው ብሎ ሀሳብ የሚያቀርብ የለም ነገር ግን ማንም የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በኢትዮጵያ እስር ቤቶች ላይ ተገኝቶ ቅኝት ቢያደርግ እኛ ያደረግነውን ጥረት የሚደግፉ መረጃዎችን ማውጣት ይችላል… የዚህ ሁሉ የመጨረሻ ውጤቱ ሁከት፣ የእስረኞች ፍትህ አልባነትና በዓለም አቀፉ ማህበረሰብና በሰብአዊ መብት ተሟጋች ደርጅቶች መወገዝ ነው፡፡”
እ.ኤ.አ. ኦክቶበር 2013 ሂዩማን ራይትስ ዎች ባቀረበው ዘገባ መሰረት “ባለፉት አስር ዓመታት ሂዩማን ራይትስ ዎች እና ሌሎች ዓለም አቀፋዊና የአገር ውስጥ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ረገጣዎች ማለትም በዘፈቀደ ማሰርና ማጋዝ፣ ህገወጥ የእስረኞች አያያዝ ድርጊት እና ማሰቃየት በተለያዩ ህጋዊና ህጋዊ ባልሆኑ እስር ቤቶች ውስጥ መፈጸማቸውን በተጨባጭ ማስረጃ አረጋግጠው ለህዝብ ይፋ አድርገዋል፡፡”
ማዕከላዊ የምርመራ ማዕከል ቤት: ኢትዮጵያ እስር ቤት መሆኗን ይመሰላል  
ከዚህ በፊት በኢትዮጵያ የእስር ቤቶችን አያያዝ ሁኔታዎች በተመለከተ ገንቢ ትችት ማቅረቤ ይታወሳል፡፡ እ.ኤ.አ. ፌብሯሪ 2012 ባቀረብኩት ትችት የኢትዮጵያ መንግስት በየፖለቲካ እስረኞች ማጎሪያዎች ላይ በዘፈቀደ የሚፈጽማቸውን የሰብአዊ መብት ረገጣዎችና ህገወጥ የእስረኞች አያያዝ ሁኔታ ለማጋለጥ ሞክሪያለሁ፡፡ እ.ኤ.አ. ፌብሯሪ 2013 ኢትዮጵያን “በአፍሪካ የፖሊስ ረጋጭ መንግሥት ተምሳሌትነት በመፈረጅ ጠንካራ ትችት አቅርቢያለሁ፡፡ የክርክር ጭብጤንም እንደሚከተለው አቅርቢያለሁ፡፡
“የሌባ ፖሊስ መንግስት ብቸኛ መለያው — ልዩ መታወቂያው — በማያቋርጥና በየቦታው የሚፈጽማቸው የዘፈቀደ እስሮች፣ ዜጎችን ማደንና ወደ እስር ቤት ማጋዝ ናቸው፡፡ ማንም ሰው በከፍተኛም ሆነ በዝቅተኛ የመንግስት ባለስልጣን ስሜታዊ ትዕዛዝ በቀጥጥር ስር ውሎ የሚታሰር ከሆነ ይኸ የፖሊስ መንግስት መገለጫ ነው፡፡ ከህግ አግባብ ውጭ የዜጎች መብት የሚጣስ ወይም የሚረገጥ ከሆነ ያ በጣም አስቀያሚ የፖሊስ መንግስት መገለጫ ነው፡፡ የህግ የበላይነት ከህግ በላይ በሆነ ፖሊስ አዛዥ የሚተካ ከሆነ ያ የሌባ ፖሊስ መንግስት ተምሳሌት ነው፡፡”
በዚያ ባቀረብኩት ትችት በአዲስ አበባ ከተማ በሙስሊሙ ህብረተሰብ ላይ ከህግ አግባብ ውጭ የፍተሻ ወረቀት ሳይዙ በሌሊት በግልሰቦች ቤት በመሄድ በሚያካሂዱት ህገወጥ ፍተሻ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ በአንዱ ህገወጥ የቤት ፍተሻ ላይ የተደረገው የሚቆጠቁጥ ድርጊት ግን የፌዴራል ፖሊስ ኃላፊዎች በሙስሊም ዜጎች ቤቶች በመግባት የፈጸሙት የገንዘብ፣ የወርቅ ጌጣጌጥ፣ የተንቀሳቃሽ ስልኮች፣ ላፕቶፕ ኮምፒውተሮች፣ የሃይማኖት መጻህፍትና ሌሎች የግል ቁሳቁሶች ላይ የተደረገው ዝርፊያ ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ ከተማ በአንድ ክፍለ ከተማ የፖሊስ አዛዥ ለሆነ ሰው የአሜሪካ ድምፅ የአማርኛው ፕሮግራም ጋዜጠኛ ጠንካራ ጥያቄዎችን በማንሳት ቃለመጠይቅ ሲያቀርብለት እንዲህ የሚል አሳፋሪ ማስፈራሪያ ሰጥቷል፣ “ዋሽንግተንም ሆነ በሰማይ ቤት ብትኖር ደንታዬ አይደለም፣ ከቁብ አልቆጥረውም፣ነገር ግን አዚያው ድረስ መጥቼ አንጠልጥልዬ አመጣሀለሁ፣ ይህን ልታውቅ ይገባል” ብሎ ዛተበት፡፡
እ.ኤ.አ. ጁላይ 2012 ኤርን በርኔት የተባለቸው የሲኤንኤን ጋዜጠኛ ኢትዮጵያን ከጎበኘች በኋላ የሚከተለውን ምስክርነት ሰጥታለች፡፡

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar